ቤተክርስቲያን ማለት የክርስቲያኖች መኖሪያ፡ የእግዚአብሔር ቤት ነው፡፡ቤት ማለት መኖሪያ ማለት እንደሆነ ሁሉ ቤተክርስቲያን ማለት የክርስቲያኖች ቤት/መኖሪያ የእግዚአብሔር ቤት ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ “ቤተ-ልሔም” የሚለው ቤተ ህብስት፣ የህብስት ቤት፣ የእንጀራ ቤት ማለት እንደሆነ ማለት ነው፡፡ “…እግዚአብሔርን አንዲት ነገር ለመንኩት እርሷንም እሻለሁ…በሕይወቴ ዘመን ሁሉ በእግዚአብሔር ቤት እኖር ዘንድ…እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኘውንም አይ ዘንድ…መቅደሱንም እመለከት ዘንድ…(መዝሙር 27፡4)” ቤተክርስቲያን ማለት አምልኮተ እግዚአብሔር የምንፈጽምበት ሕንፃ ቤተክርስቲያንንና በውስጡ ያሉትን ንዋየ ቅድሳት፣ የሚፈፀሙትን ምሠጢራትና ያለውን አገልግሎት ጨምሮ ነው፡፡
እዚህ ላይ ህንፃ ቤተክርስቲያን ስንል አገልግሎቱንም ጭምር የሚያመለክት መሆኑ ሊሰመርበት ይገባል፡፡ ይህም የክርስቲያኖች መሰብሰቢያ መገናኛ፤ ክርስቲያኖች በአንድነት ተሰብስበው የሚጸልዩበት ሥጋ ወደሙ የሚቀበሉበት የሚሰግዱበት ከእግዚአብሔር ጋር የሚገናኙበት የጸሎት ቤት ማለት ነው፡፡ ኢሳ. 56÷7 ኤር.7÷10-11 ማቴ.21÷13 ማር. 11÷17 ሉቃ. 19÷46 በሌላም ስፍራ «እኔ ግን በምሕረትህ ብዛት ወደቤትህ እገባለሁ፥ አንተን በመፍራት በቤተ መቅደስህ እሰግዳለሁ።» እንዲል መዝ 5፡7 እንዲሁም «አሁንም በዚህ ስፍራ ለሚጸለይ ጸሎት ዓይኖቼ ይገለጣሉ፥ ጆሮዎቼም ያደምጣሉ። አሁንም ስሜ ለዘላለም በዚያ ይኖር ዘንድ ይህን ቤት መርጫለሁ፤ ቀድሻለሁም፤ ዓይኖቼና ልቤም ዘወትር በዚያ ይሆናሉ።» ብሏል። 2ኛ ዜና 7፥15(ኢሳ. 56፡7፤ ኤር. 6፡10-16፤ ማቴ. 21፡13፤ ማር. 11፡17፤ ሉቃ. 19፡46 ) ጌታም “ቤቴ የጸሎት ቤት ትባላለች` በማለት የቤተመቅደስን አስፈላጊነት ነግሮናል፡፡ “ቤቴ” ወዳላት ቤተመቅደስ በመሄድ ክርስቶስን ዛረም እናመልካልን፡፡ እዚህ ላይ “ቤቴ” ሲል ባለቤትነቱ የእርሱ መሆኑን ያረጋግጣል፡፡ ሐዋርያትም ወደ ቤተመቅደስ አዘውትረው ይሄዱ እንደነበር መጽሐፍ ይናገራል (ሐዋ 3፡1) የጸሎት ቤት ናትና፡፡
I happen this learn
LikeLike