ቤተክርስቲያን ኲላዊት ናት፡፡
ቤተክርስቲያን ኲላዊት ናት ሲባል የሁሉ (አለም አቀፋዊት- Universal) እና ከሁሉ በላይ ናት ማለት ነው፡፡ ይህም በጸሎተ ሃይማኖት “እንተ ላዕለ ኩሉ” በሚለው ይታወቃል፡፡ ቤተክርስቲያን የሁሉ እንደሆነች ሁሉ ደግሞ ከሁሉ በላይ ናት፡፡ በደመ ክርስቶስ የተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የዚህ ወገን ናት የዚህ ወገን አይደለችም የማትባል በዘር፣ በቋንቋ፣ በጎጥና በቀለም እንዲሁም በቦታ የማትከፋፈል የሁሉና በሁሉ ያለች ናት፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን የሁሉም መሆንዋን እንዲህ ሲል ገልጾታል“አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና” ገላቲያን 3 ፥ 28፡፡
ቤተክርስቲያን የሁሉ ናት (አለም አቀፋዊት ናት) ስንል በአምስት ደረጃ ከፍለን ልናየው እንችላለን፡፡
በመልክአ ምድር (Geography)፡- ቤተክርስቲያን የዚህ ሀገር ወይም የዚህ አካባቢ ናት አይባልም፡፡ በክርስቶስ ያመነ የተጠመቀ ሁሉ (ከማንኛውም የዓለም ክፍል ቢመጣ) የሚገባባትና የሚኖርባት ቤት ናት እንጂ፡፡
በሰው ፀባይ (Personal attributes):- ቤተክርስቲያን የዚህ ዘር፣ የዚህ ቋንቋ ተናጋሪ፣ የዚህ ጾታ ወይም የዚህ እድሜ ክልል ናት አይባልም፡፡ የሁሉም ናት እንጂ፡፡ በቤተክርስቲያን ሰው እምነቱ እንጂ ሰብአዊ ማንነቱ አይጠየቅም፡፡
በጊዜ/በዘመን (Time horizon)፡- ቤተክርስቲያን ከሐዋርያት ዘመን ጀምሮ ለነበረው ትውልድ፣ አሁንም ላለው ትውልድ፣ ወደፊትም ለሚኖረው ትውልድ ናት፡፡ ቤተክርስቲያን የሁሉም ናት ሲባል የሁሉም ትውልድ ናት ማለትም ነው፡፡
በማዕረጋት (Hierarchical):- ቤተክርስቲያን የፓትያርኩም፡ የጳጳሳቱም፡ የቀሳውስቱም፡ የዲያቆናቱም፡ የምዕመናኑም ናት፡፡ ሁሉም በቤተክርስቲያን የየራሳቸው ድርሻ አላቸው፡፡
በሰማይና ምድር (Earth and Heaven)፡- ቤተክርስቲያን በአካለ ሥጋና በአካለ ነፍስ ያሉት አንድነት ስለሆነች የሁለቱም ናት፡፡ ቤተክርስቲያን የክርስቶስ ስለሆነች የክርስቶስ ለሆነ ሁሉ ናት፡፡
ቤተክርስቲያን የሁሉም ናት ሲባል በቃ የሁሉ ናት ተብሎ የሚያበቃ አይደለም፡፡ የሁሉም ናት ማለት ሁሉም በቤተክርስቲያን የየራሱ የአገልግሎት ድርሻ አለው ማለት ነው፡፡ ፈተና ቢያጋጥማትም የሚመለከተው ሁሉንም ነው ማለት ነው፡፡