በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን
እመቤታችን ቅዱስት ድንግል ማርያም የመልአኩን የቅዱስ ገብርኤልን ብሥራት ከሰማች በኋላ፣ የአብ ቃል ወልድ በማኅፀኗ አድሮ፣ ወደ ተራራማው ኤፍሬም አገርም ሄዳ በቅድስት ኤልሳቤጥ ከተመሰገነች በኋላ የጸለየችው ጸሎት፣ ያቀረበችው ምስጋና፣ የዘመረችው የምስጋና መዝሙር ጸሎተ እግዝእትነ ማርያም (የእመቤታችን የማርያም ጸሎት/Magnificat – St Mary’s Song of Praise) ይባላል። ይህም ቅዱስ ሉቃስ በወንጌሉ ያሰፈረው ነው (ሉቃ 1:46-55)። ይህ ጸሎት የወልደ እግዚአብሔር ሰው የመሆኑ አዋጅ፣ የሐዲስ ኪዳንን መጀመር ያበሠረ ትንቢታዊ መዝሙር፣ በአዲሲቷ ሔዋን መታዘዝ የመጀመሪያዋ ሔዋን አለመታዘዝ የፈረሰበት፣ እመቤታችን የእውነተኛ ትህትና ፍጽምት ምሳሌ መሆኗ የተገለጠበት፣ እውነተኛዋ ቤተ ክርስቲያን በቅድስት ድንግል ማርያም በኩል ያሰማችው የደስታ ድምፅ፣ የእግዚአብሔር ምሕረትና የነገረ ድኅነት ዜና ነው። ይህ ታላቅ ጸሎት ትህትና፣ እምነት፣ ትፍስሕት፣ ምስጋና፣ መታዘዝ፣ ተስፋ እና ፍቅር በአንድነት የተገለጡበት ነው። ስለዚህም በዘወትር ጸሎታችን እንድንጸልየው ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሠርታልናለች። በዚህች የአስተምህሮ ትምህርታዊ ጽሑፍ የዚህን ጸሎት (ምስጋና) ይዘት በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት አስተምህሮ መሠረት በዝርዝር እንዳስሳለን።

ታዐብዮ ነፍስየ ለእግዚአብሔር/ነፍሴ እግዚአብሔርን ታላቅ ታደርገዋለች
“ጻድቅና ቅድስት የሆነች ነፍስ በምን ትገለጣለች?” ቢሉ እግዚአብሔርን በማክበር ነው። ለዚህም ቅድስት ድንግል ማርያም እውነተኛ ምሳሌ ናት። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በቤተ መቅደስ እግዚአብሔርን ስታመሰግን ያደገች የብፅዓት ልጅ ናት። በቤተ መቅደስ የአባቷን የቅዱስ ዳዊትን መዝሙር የሌሎችንም ቅዱሳንን ጸሎት ስትጸልይ ያደገች ቅድስት ናት። ስለዚህም ጸሎቷን እንደነዚህ ቅዱሳን ነፍሴ (My Soul) እግዚአብሔርን ታከብረዋለች በማለት ጀመረች። ጸጋን የተመላች ቅድስት ድንግል ማርያም ‘ነፍሴ’ ስትል በሙሉ መሰጠት በፍፁም ልቧ፣ ሕሊናዋና ፈቃዷ የምታመሰግን መሆኑን ያመለክታል። ይህም ለክርስቲያኖች ጸሎት ሁሉ አርአያ የሆነ ጸሎት ነው። እመቤታችን የአምላክ እናት ለመሆን የተመረጠች ሆና ሳለ እንደ አባቷ ቅዱስ ዳዊት (መዝ 103:1)፣ እንደ ቅዱሳን ነቢያት (ኢሳ 61:10)፣ እንደ እመ ሳሙኤል (1ኛ ሳሙ 2:1-10) ሐና ‘ነፍሴ እግዚአብሔርን ታላቅ ታደርገዋለች’ አለች። ይህ ፍፁም ትህትናዋን የሚያመለክት ነው። እርሷ የትህትና አርአያ ናትና። በምሥጢራዊ ትርጉም ግን እግዚአብሔርን ታላቅ ታደርገዋለች ማለቷ የማይታየው፣ የማይዳሰሰው አምላክ የእርስዋን ነፍስና ሥጋ ተዋሕዶ የሚታይና የሚዳሰስ መሆኑን የሚያጠይቅ ነው።
ወትትሐሠይ መንፈስየ በአምላኪየ ወመድኃንየ/መንፈሴም በመድኃኒቴ በእግዚአብሔር ደስ ይላታል
ለሰው ልጅ ሁሉ ከክርስቶስ መወለድ የበለጠ ደስታ የለውም። እመቤታችንም ስለዚህ ደስታ ነው ምስጋናን ያቀረበችው። የእመቤታችን ምስጋና በነፍስም በመንፈስም በሥጋም የቀረበ ስለሆነ ምሉዕ ምስጋና ነው። ሰው የነፍስ፣ የመንፈስና የሥጋ ውሕደት ነውና (1ኛ ተሰ 5:23)። መንፈስ ቅዱስ መልቶባታልና ‘መንፈሴ ደስ ይላታል’ (ሐሴት ታደርጋለች) አለች። በማኅፀኗ ያደረው ወልደ እግዚአብሔር ፈጣሪዋ ነውና መንፈሴም (My Spirit) በአምላኬ በእግዚአብሔር ሐሴት ታደርጋለች አለች። በመድኃኒቴ ማለቷ ከእርስዋ የተወለደው ለዓለሙ ሁሉ መድኃኒት መሆኑን የሚያጠይቅ ነው። እርስዋንም ጠብቋታልና መድኃኒቴ አለችው። ይህም ትህትናዋን የሚያሳይ ነው። እርሷ ከተለዩ የተለየች ብትሆንም ራስዋን ዝቅ አድርጋ መድኃኒቴ አለችው። ለአምላክ እናትነት መመረጧ የእግዚአብሔር ድንቅ ሥራ አድርጋ መድኃኒቴ አለችው። አንድም እስራኤል ዘነፍስን ሁሉ ወክላ መድኃኒቴ አለችው። እርሱ የዓለም መድኃኒት (መድኃኔ ዓለም) ነውና።
እስመ ርእየ ሕማማ ለአመቱ/የባርያይቱን መዋረድ (ትህትና) አይቷልና
እመቤታችን የባርያውን ትህትና ተመልክቷልና ማለቷ ሌላው የትህትናዋ መገለጫ ነው። እመቤታችን ለአምላክ እናትነት የተመረጠች ስትሆን ራሷን ዝቅ አድርጋ የባርያውን ትህትና አለች። ይህም አስቀድማ ለመልአኩ ለቅዱስ ገብርኤል እነሆኝ የጌታ ባሪያ እንደ ቃልህ ይደረግልኝ (ሉቃ 1:38) ያለችው ነው። የእኔን የባርያውን ትህትና ተመልክቷልና መንፈሴ በእርሱ ሐሴት ታደርጋለች ማለቷ ነው። እርስዋ እናት ስትሆን በትህትና ራስዋን ባሪያ አለች። በምስጢራዊ ትርጉሙ ግን የመጀመሪያዋን ሔዋን ውርደት (ውድቀት) የሚመለከት ነው። የቀዳማዊት ሔዋንን ውርደት ተመልክቷልና፤ ተመልክቶም የማዳኑን ሥራ ጀምሯልና ማለት ነው። ቅዱስ ኤፍሬም በሐሙስ ውዳሴ ማርያም “ሔዋን ዕፀ በለስ በልታ ባደረገችው ዓመፅ በባሕርያችን ያደረ የቀድሞው እርግማን በእርስዋ የጠፋልን አምላክን የወለደች ድንግል ማርያም የሁላችን መመኪያ ናት። ስለ ሔዋን የገነት ደጅ ተዘጋ ዳግመኛም ስለ ድንግል ማርያም ተከፈተልን” እንዳለው መዋረዳችንን ተመልክቶ መድኃኒትን እንደላከልን የሚያጠይቅ ነው። የእመቤታችን ደስታ (ወትትኃሠይ ያለችው) ከዚህ የተነሳ ነው። ይህ የሰው ልጅ ሁሉ ደስታ ነውና።
ናሁ እምይእዜሰ ያስተበፅዑኒ ኩሉ ትዉልድ/እነሆም፥ ከዛሬ ጀምሮ ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉኛል
አስቀድሞ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል፣ ከዚያም ቅድስት ኤልሳቤጥ እመቤታችንን አንቺ ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ ብለው አመስግነዋታል። ከዚያ ጀምሮ እስከ ዘለዓለም ድረስ እንደምትመሰገን ስትገልጽ ከዛሬ ጀምሮ አለች። ይህም ከዚያች ቀን ጀምሮ እስከ ዘላለም ድረስ ማለት ነው። ትውልድ ሁሉ ማለቷ የሰው ልጅ ሁሉ (ትውልደ ሴም፣ ትውልደ ያፌት፣ ትውልደ ካም)፣ እስከ ዓላም ፍፃሜ ድረስ የሚነሳው ትውልድ ማለቷ ነው። “ብፁዕ” ማለት የተባረከ፣ የተመሰገነ፣ ለብቃት የደረሰ ማለት ሲሆን ብፅዕት ማለትም የተባረከች፣ የተመሰገነች፣ ቅድስት ማለት ነው። ይህ ለእመቤታችን የሚገባ ነው። ስለዚህ እኛም ስለንጽሕናዋ፣ ስለቅድስናዋ፣ የፈጣሪያችን እናት ስለመሆንዋ፣ ምክንያተ ድኂን ስለሆነችን እንደ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልና እንደ ቅድስት ኤልሳቤጥ ቡርክት አንቲ እምአንስት (ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ) እያልን እናመሰግናታለን። ብፅዕት ይሉኛል ማለትም በውዳሴ፣ በቅዳሴ፣ በዝማሬ፣ በቅኔና በመሳሰሉት ያመሰግኑኛል ማለት ነው። እንደ ቅዱስ አትናቴዎስ፣ እንደ ቄርሎስ፣ እንደ ቅዱስ ኤፍሬም፣ እንደ አባ ሕርያቆስ፣ እንደ ቅዱስ ያሬድ፣ እንደ አባ ጊዮርጊስም በሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን ሆነን ብፅዕት ስንላት እንኖራለን። ስምሽን ለልጅ ልጅ ያሳስባሉ እንደተባለው ምስጋናዋን ለትውልድና ትውልድ እናሳስባለን።
“ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉኛል” የሚለው አገላለፅ “እንዴት ከትሕትና ጋር ይስማማል?” ቢሉ አዎን ይህም የእመቤታችን ትሕትና አንዱ መገለጫ ነው። እርሷ ቅድስተ ቅዱሳን መሆኗ የታወቀ ነው። ነገር ግን ይህ አገላለፅም ቢሆን በታላቅ ትሕትና የተናገረችበት ነው። እመቤታችን “ትውልድ ሁሉ (እነርሱ) ብፅዕት ይሉኛል፤ በእኔ ታላቅ ነገርን አድርጓልና” ያለችው እግዚአብሔር ሰውን ለማዳን ያደረገውን እፁብ ድንቅ የሆነ የማዳኑን ሥራ (ከእርሷ ሰው መሆኑን፣ እርሷንም ወላዲተ አምላክ ማድረጉን) የተናገረችበት ነው። አንድም በትንቢት ለወደፊት የሚሆነውን እውነት የተናገረችበት ነው። አንድም በትሕትና የሚቀርብ ጸሎት እግዚአብሔር ያደረገውን መቀበልንና ሥራውንም መመስከርን ያካትታልና ለእናትነት የመረጣትን እግዚአብሔርን ያመሰገነችበት ነው። አንድም በሦስተኛ አካል (እነርሱ ተብለው በሚጠሩት ትውልድ ሁሉ) ብፅዕት ይሉኛል (እንደሚሉ በሚገልጽ የትሕትና ቃል) ነው ያለችው። ይህም እውነታን (reality) የሚገልፅ ነው። ትውልድ ብፅዕት የሚሏት ለራሳቸው ምክንያተ ድኂን ስለሆነችላቸው እንጂ ብፅዕት ብለው ለእርሷ (ምልዕተ ክብር ለሆነችው) የሚጨምሩላት አንዳች ክብር እንደሌለ የታወቀ ነውና። ለሰው ልጅ ሁሉ ቅድስናንና ጽድቅን የሚያድለውን አምላክን ወልዳለችና ስለዚህ ትውልድ ብፅዕት ይሉኛል ማለቷ እርሷን በማመስገን ክብርን እንደሚያገኙ የሚያሳይ ነው።
ጌታችን ሲያስተምር፥ ከሕዝቡ አንዲት ሴት ድምፅዋን ከፍ አድርጋ የተሸከመችህ ማኅፀንና የጠባሃቸው ጡቶች ብፁዓን ናቸው አለችው። እርሱ ግን አዎን፥ ብፁዓንስ የእግዚአብሔርን ቃል ሰምተው የሚጠብቁት ናቸው አለ (ሉቃ 11:27-28)። ጌታችን በዚህ መልስ የእመቤታችንን ብፅዕና በምልዓት አስረግጧል። ምክንያቱም እመቤታችን ጌታችንን በሥጋ የወለደች ጡቶቿንም ያጠባች ብቻ ሳትሆን የእግዚአብሔርን ቃል የሰማች፣ በትሕትና የተቀበለች፣ በልቧም የጠበቀች ናትና። የእርስዋ ንጽሕና የነፍስም፣ የሥጋም፣ የመንፈስም ነውና። ጌታችን በዚህ መልሱ የብፅዕናን ትርጉም አስፍቶ ብፅዕና የእግዚአብሔርን ቃል ሰምተው ለሚጠብቁት ሁሉ መሆኑን አስተማረ። የቅድስት ድንግል ማርያም ብፅዕናም በማኅፀኗ በመሸከምና ጡቶቿን በማጥባት ብቻ ሳይሆን (አካላዊ ብቻ ያይደለ) በንጽሕና፣ በድንግልና፣ በፍፁም መታዘዝ ጭምር እንደሆነ አስተማረ። አንድም ብፅዕና የሚገኘው የእግዚአብሔርን ቃል ሰምቶ በመፈጸም እንጂ መምህራንን በማድነቅ እንዳልሆነ አስተማረ። አንድም እውነተኛ ክርስትና የእግዚአብሔርን ቃል ሰምቶ በማድነቅ ሳይሆን ቃሉን በመጠበቅ ክርስቶስን እንደ ሐዋርያት መከተል መሆኑን ሊያስረዳ ይህንን አለ። ይህችም ሴት (እያስተማረ እያለ በመካከል አቋርጣ አድናቆትን አቅርባለችና) እርሱ የሚያስተምረውን ቃል ሰምታ፣ ጠብቃ ብፅዕናን እንድታገኝ ሊያስተምራት ይህንን አለ።
እስመ ገብረ ሊተ ወኃይለ ዐቢያተ/ብርቱ የሆነ እርሱ በእኔ ታላቅ ሥራ አድርጓልና
በእመቤታችን ትህትና የእግዚአብሔር ታላቅነት ተገልጧል። እርስዋ ንጽሕናዋን፣ መመረጧን፣ የአምላክ እናት መሆንዋን የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው በማለት የተናገረች የፍፁም ትህትና ምሳሌ ናት። እግዚአብሔር ብርቱ አምላክ ስለሆነ በዘመናት ብዙ ታላላቅ ነገሮችን አድርጓል፣ ያደርጋልም። ከእመቤታችን ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ ተወልዶ ሰውን ያዳነበት ሥራው ግን ከሁሉም እጅግ ታላቅ ነው። ቅዱሳን አባቶቻችን “እግዚአብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ይልቅ ዓለምን ያዳነበት ጥበቡ እጅግ ይደንቃል” የሚሉትም ለዚህ ነው። ስለዚህ ነው እመቤታችን በእኔ ሰውን ያዳነበትን ታላቅ ሥራ አድርጓል ያለችው። እርሷ የድኅነታችን መጀመሪያ፣ የንፅሕናችን መሠረት፣ የባህርያችን መመኪያ ናትና። ብፅዕት የምንልበት ምክንያትም በእርስዋ ይህ ታላቅ የማዳኑ ሥራ ስለተደረገልን ነው። የክርስቶስን የማዳኑን ሥራ የሚናገር ሁሉ ከእርስዋ ከመወለዱ ይጀምራልና፣ ይህም እስከ ዘለዓለም ሲነገር የሚኖር ነው።
ወቅዱስ ስሙ/ስሙም ቅዱስ ነው
እግዚአብሔር በባሕርይው ቅዱስ ነው። አስቀድሞ ብዙ ቅዱሳን ስሙ ቅዱስ ነው ብለው አመስግነውታል (መዝ 111:9 ኢሳ 57:15 1ኛ ሳሙ 2:2)። በቅዱሳን መላእክትም ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ እየተባለ የሚመሰገን አምላክ ነው(ኢሳ 6:3 ራዕይ 4:8)። እመቤታችን ስሙም ቅዱስ ነው ያለችው ግን የተለየ ነው። ይህም የማዳኑን ሥራ የሚመለከት ቅድስናውን ነው። የወደቀውን አዳምን ያሰበውን፣ ሊታደገውም በማኅፀኗ ያደረውን የማዳን ሥራውን የሚመለከት ነው። በእርስዋ የተገለጸውን ምህረቱን፣ ርህራሄውንና ቤዛነቱን የሚመለከት ቅድስናውን ነው። ከቀደሙት ቅዱሳን የእመቤታችንን ስሙ ቅዱስ ነው ማለት የሚለየው እነርሱ ቅዱስ ያሉት በመንበሩ ያለውን አምላክ ሲሆን እርሷ ቅዱስ ነው ያለችው በማኅፀኗ ያደረውን አምላክ መሆኑ ነው። ይህ በእውነት እንዴት ያለ ምስጋና ነው? ስምህ ይቀደስ ብላችሁ ጸልዩ ያለንን አምላክ ገና በማኅፀኗ ሳለ ስሙ ቅዱስ ነው ብሎ ማመስገን በእውነት እንዴት ያለ ቅድስና ነው?
ወሣህሉኒ ለትውልደ ትዉልድ ለእለ ይፈርህዎ/ለሚፈሩትም ምሕረቱ እስከ ትውልድና ትውልድ ነው
የእግዚአብሔር ምህረት በትውልድ የማይገደብ ዘላለማዊ ነው። ቅዱስ ዳዊት ምህረቱ ለዘለዓለም ነውና እያለ ያመሰገነው ስለዚህ ነው (መዝ 107፥1)። ምህረቱ ለዘለዓለም ነው ስንል አንድ ጊዜ ያደረገው ምህረት ለዘለዓለም ይኖራል ማለት ነው። እንዲሁም እስከ ዘለዓለም ለሚነሳው ትውልድ ሁሉ ምህረትን ሲያደርግ ይኖራል ማለት ነው። የሚፈሩትም የተባሉ ትሁታን፣ እግዚአብሔርን የሚወዱና የሚያከብሩ ናቸው። ይህ መፍራት ከፍቅር የሚመነጭ ፍርሃት ነው፤ ከፍቅረ እግዚአብሔር የሚመነጭ ፍርሃት። ይህም የጥበብ መጀመሪያ የሆነው እግዚአብሔርን መፍራት ነው። ለሚፈሩት፣ በስሙ ላመኑት ከድንግል ማርያም ተውልዶ ያደረገልን ምህረት ለዘለዓለም የሚኖር ነው። አንድ ጊዜ የፈጸመው የማዳን ሥራ እስከ ትውልድና ትውልድ ነው። በእርሷ ያደረገው የማዳን ሥራ ለዘለዓለም መሆኑን ለመግለጽ ለሚፈሩትም ምህረቱ እስከ ትውልድና ትውልድ ነው አለች።
ወገብረ ኃይለ በመዝራዕቱ/ኃይልን በክንዱ አደረገ
ልበ አምላክ ክቡር ዳዊት ፈኑ እዴከ እምአርያም ወአድኅነኒ/እጅህን ከአርያም ላክ አድነኝም (መዝ 144:7) እንዳለው የእግዚአብሔር እጅ (ክንድ) የተባለ ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስም የእግዚአብሔርስ ክንድ ለማን ተገልጦአል? ያለው ክርስቶስን ነው። ቅዱስ ኤፍሬምም ፈነወ ለነ መዝራዕቶ ልዑለ/ልዑል ክንዱን ሰደደልን በማለት የእግዚአብሔር ክንድ ልጁ ወልድ መሆኑን ተናግሯል። ስለዚህ ኃይልን በክንዱ አደረገ ማለት ኃይልን በወልድ አደረገ ማለት ነው። ኃይልን የተባለውም ድንቅ የሆነና የማይመረመረው ከእርሷ ተውልዶ፣ ቤዛ ሆኖ የፈጸመው የማዳኑ ሥራ ነው። ከእርስዋ በተወለደው በተዋሕዶ በከበረው አምላክ የሰው ልጅ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከሲኦል ወደ ገነት ተሸጋግሯልና።
ወዘረዎሙ ለእለ ያዐብዩ ሕሊና ልቦሙ/በልባቸው አሳብ የሚኮሩ ትዕቢተኞችን በታተናቸው
ይህ የእግዚአብሔር ልጅ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያደረገውን በትንቢት የተናገረችበት ነው። ትዕቢት የውድቀት መሠረት ናት። በልባቸው ትዕቢት የተበታተኑት እነማን ናቸው? በመጀመሪያ በልባቸው ሀሳብ የሚኮሩ ትዕቢተኞች ሳጥናኤል (ዲያብሎስ) እና ጭፍሮቹ ናቸው። “አንተ የንጋት ልጅ አጥቢያ ኮከብ ሆይ፥ እንዴት ከሰማይ ወደቅህ! አሕዛብንም ያዋረድህ አንተ ሆይ፥ እንዴት እስከ ምድር ድረስ ተቈረጥህ! አንተን በልብህ። ወደ ሰምይ ዐርጋለሁ፥ ዙፋኔንም ከእግዚአብሔር ከዋክብት በላይ ከፍ ከፍ አደርጋለሁ፥ በሰሜንም ዳርቻ በመሰብሰቢያ ተራራ ላይ እቀመጣለሁ፤ ከዳመናዎች ከፍታ በላይ ዐርጋለሁ፥ በልዑልም እመሰላለሁ አልህ። ነገር ግን ወደ ሲኦል ወደ ጕድጓዱም ጥልቅ ትወርዳለህ …(ኢሳ 14:12-17)” እንደተባለው በኃይሉ በታትኗቸዋል።
አንድም በእግዚአብሔር ላይ ያምጹ የነበሩ ሕዝቡን እለቅ ዘንድ እግዚአብሔር ማነው? (ዘጸ 5:2) ብለው የሚጠይቁ እንደ ፈርኦን ያሉ፣ እግዚአብሔርን ክደው ጣኦትን ያስመልኩ የነበሩ እንደ ናቡከደነፆር ያሉና ክርስቶስንና ድንግል ማርያምን ያሳደዱ እንደ ሄሮድስ ያሉ በልባቸው ሀሳብ ይኮሩ የነበሩ ትዕቢተኞች ናቸው። እነዚህን በታትኗቸዋል። እንዲሁም በራሳቸው የሚመጻደቁ፣ ራሳቸውን ያጸደቁ፣ ግብዞች የነበሩትን ፈሪሳውያንን ነው። እናያለን እያሉ የማያዩ፣ እንሰማለን እያሉ የማይሰሙ በመንፈስ የታወሩ ፈሪሳውያንንና እነርሱን በግብር የሚመስሉትን ሁሉ ነው (ዮሐ 9:39)። እነዚህም ተበታትነዋል። በየዘመናቱ የሚነሡ የእነዚህ የግብር ልጆችም እንዲሁ ይበተናሉ።
ወነሠቶሙ ለኃያላን እመናብርቲሆሙ/ብርቱዎችንም(ኃያላንን) ከዙፋናቸው አዋረዳቸው
ቀደምት አባቶች እንዳስተማሩት ይህ ምድራዊ ስልጣንን የሚመለከት ሳይሆን መንፈሳዊ ትርጉም ያለው ነው። በሰው ልጅ ላይ ነግሠው የነበሩትን ትዕቢትን (ራስን ከፍ ከፍ ማድረግ)፣ ክፋትን፣ ኃጢአትን፣ አጋንንትን ከዙፋናቸው አዋረዳቸው ማለቷ ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በኤፌሶን መልእክቱ “በበደላችሁና በኃጢአታችሁ ሙታን ነበራችሁ፤ በእነርሱም በዚህ ዓለም እንዳለው ኑሮ፥ በማይታዘዙትም ልጆች ላይ አሁን ለሚሠራው መንፈስ አለቃ እንደ ሆነው በአየር ላይ ሥልጣን እንዳለው አለቃ ፈቃድ፥ በፊት ተመላለሳችሁባቸው(ኤፌ 2:2)” እንዳለው በአየር ላይ ስልጣን የነበራቸውን (“Powers of the air”) አለቅነትንና ሥልጣናትን ገፎ፥ ድል በመንሣት በእርሱ እያዞራቸው በግልጥ አሳያቸው (ቆላ 2:15)።
በተጨማሪም “መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ” (ኤፌ 6:12 1ኛ ጴጥ 5:8)” እንደተባለው እነዚህን አለቆችና ገዥዎች የሚመለከት ነው። ጌታችንም “አሁን የዚህ ዓለም ፍርድ ደርሶአል፤ አሁን የዚህ ዓለም ገዥ ወደ ውጭ ይጣላል(ዮሐ 12:31)” በማለት የተናገረው ይህንኑ ነው። እንዲሁም እስራኤልን በግፍ ይገዙ የነበሩትን ‘መንፈሳዊ’ ባለስልጣናትና የእነርሱን የግብር ልጆች የሚመለከት ነው። ልጇ ጌታችን በወንጌሉ “እንዲሁ ኋለኞች ፊተኞች፥ ፊተኞችም ኋለኞች ይሆናሉ (ማቴ 20:16)” እንዳለው ራሳቸውን በቅድስና ስፍራ ያስቀመጡትና የሚያስቀምጡትን ከዙፋናቸው አዋረዳቸው ማለቷ ነው። መንፈሳዊ ስልጣን ከግብዞቹ፣ ተመጻዳቂዎቹ፣ መንፈሳዊ አምባገነኖች ከነበሩት ከፈሪሳውያን ትለቃለች ማለቷ ነው።
አዕበዩሙ ለትሑታን/የተዋረዱትንም (ትሑታንን) ከፍ ከፍ አደረጋቸው
ትህትና የቅድስና ሕይወት መግቢያ በር ናት። ትሁታን ራሳቸውን ዝቅ ዝቅ የሚያደርጉ፣ ፈሪሃ እግዚአብሔር በልባቸው ያላቸው ናቸው። ትሁታን ራሳቸውን የሚያጸድቁ ሳይሆኑ ጽድቅን የሚራቡ ናቸው። አስቀድመን እንደገለጽነው እመቤታችንም የትሁታን ምሳሌ ናት። ክርስቶስ የመሠረታት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም የትህትና አምባ ናት። ክርስቶስ በዚህ ዓለም ሲያስተምር ይውል የነበረው በዓለም ዘንድ የተናቁ ከነበሩት ከኃጢአትኞችና ከቀራጮች ጋር ነበር። ከእነርሱም ሐዋርያትን መርጦ እስከመፍረድ የሚደርስ ልጣንን ሰጥቷቸዋል(ማቴ 19:28)። የተዋረዱትንም ከፍ ከፍ አደረጋቸው ያለችው እነዚህን ነው። ትህትና አስቀድሞ ነቢያት፣ ኋላም ክርስቶስና የእርሱ ሐዋርያት በሰፊው ያስተማሯት የመንፈሳዊ ሕይወት አንዷ መርኅ ናትና።
አስቀድሞ ልበ አምላክ ክቡር ዳዊት “እግዚአብሔር ትሁታንን ያነሣል፥ ኃጢአተኞችን ግን እስከ ምድር ድረስ ያዋርዳል (መዝ 147:6)” በማለት እግዚአብሔር ትሁታንን ከፍ ከፍ እንደሚያደርግ ተናግሯል። ጌታችንም በወንጌሉ “ራሱን ከፍ የሚያደርግ ሁሉ ይዋረዳልና፥ ራሱን ግን የሚያዋርድ ከፍ ይላል (ሉቃ 18:14)” በማለት ትህትናን አስተምሯል። ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስም “እንግዲህ በጊዜው ከፍ እንዲያደርጋችሁ ከኃይለኛው ከእግዚአብሔር እጅ በታች ራሳችሁን አዋርዱ (1ኛ ጴጥ 5:6)” ከፍ ለማለት ራስን ማዋረድ እንደሚገባ ተናግሯል። ሐዋርያው ያዕቆብም እንዲሁ “እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ይቃወማል፥ ለትሑታን ግን ጸጋን ይሰጣል። በጌታ ፊት ራሳችሁን አዋርዱ ከፍ ከፍም ያደርጋችኋል (ያዕ 4:6፣10)” ብሏል።
ወአጽገቦሙ እምበረከቱ ለርኁባን/የተራቡትንም ከበረከቱ አጠገባቸው
የተራቡት የተባሉ ጽድቅን የሚራቡ፣ ማዳኑን የሚጠባበቁ ናቸው። በረከቱም ጸጋው፣ ጥበቡና ማዳኑ ነው። ጽድቅን/እውነትን (ክርስቶስን) ተርበው የነበሩት አሕዛብ ሐዋርያትን ልኮ በወንጌሉ አጠገባቸው። ይህም ክቡር ዳዊት በመዝሙሩ “የተራበችን ነፍስ አጥግቦአልና፥ የተራቈተችንም ነፍስ በበረከት ሞልቶአልና(መዝ 107:9)” እንዳለው ነው። ጌታችንም በወንጌሉ “ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው፥ ይጠግባሉና (ማቴ 5:6)” በማለት ያስተማረው ይህንኑ ያጠይቃል። አንድም ላመኑት ከሰማይ የወረደውን አማናዊ መና የተባለ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ሰጥቶ ጽድቅን ያጎናጽፋቸዋል ማለት ነው። ጌታችን በወንጌሉ “የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ፤ ወደ እኔ የሚመጣ ከቶ አይራብም በእኔ የሚያምንም ሁልጊዜ ከቶ አይጠማም። ከሰማይ የወረደ ሕያው እንጀራ እኔ ነኝ፤ ሰው ከዚህ እንጀራ ቢበላ ለዘላለም ይኖራል፤ እኔም ስለ ዓለም ሕይወት የምሰጠው እንጀራ ሥጋዬ ነው (ዮሐ 6:35 51)” በማለት ያስተማረው ምስጢረ ቁርባንን የሚያመለክት ነው።
ወፈነዎሙ ዕራቆሙ ለብዑላን/ባለጠጎችንም ባዶ እጃቸውን ሰደዳቸው
ባለጠጎች የሚባሉት በትዕቢት የተሞሉና ምንም እንደማያስፈልጋቸው የሚያስቡ ናቸው። ባለጠጎች የሚባሉት በምድራዊ ሀብት የረኩና መንፈሳዊ ነገር እንደማያስፈልጋቸው የሚያስቡ ናቸው። እነዚህ የእግዚአብሔርን በረከት አያገኙም። አንድም ባላጠጎች ራሳቸውን ያጸደቁ፣ የስልጣን ሀብታም የመንፈሳዊ ሕይወት ድሃ ሆነው ክርስቶስን የተቃወሙት የካህናት አለቆችና ፈሪሳውያን ናቸው። እነዚህን ሁሉ ባዶ እጃቸውን ሰደዳቸው። ሰደዳቸው ማለት እግዚአብሔር በኃይል እንዲህ አደረገባቸው ማለት አይደለም። ትዕቢታቸውና ክርስቶስን አለመቀበላቸው ምንም ጽድቅን ሳያገኙ ባዶ እጃቸውን አስቀራቸው ማለት ነው እንጂ። ቅዱስ ዮሐንስ በራዕዩ “ሀብታም ነኝና ባለጠጋ ሆኜአለሁ አንድም ስንኳ አያስፈልገኝም የምትል ስለ ሆንህ፥ ጐስቋላና ምስኪንም ድሀም ዕውርም የተራቆትህም መሆንህን ስለማታውቅ፥ ባለ ጠጋ እንድትሆን በእሳት የነጠረውን ወርቅ፥ ተጐናጽፈህም የራቁትነትህ ኃፍረት እንዳይገለጥ ነጭ ልብስን፥ እንድታይም ዓይኖችህን የምትኳለውን ኵል ከእኔ ትገዛ ዘንድ እመክርሃለሁ (ራዕ 3:17)” ያለው ይህንን የሚያረጋግጥ ነው። ጌታችንም ለባለጠጋ መንግስተ ሰማያት መግባት ጭንቅ ነው ያለው ለዚህ ነው (ማቴ 10:23) ።
ወተወክፎ ለእስራኤል ቍልዔሁ/ እስራኤል ባርያውን ተቀበለ (ረድቷል)
እስራኤል የሚለው በሁለት ወገን ይተረጎማል። የመጀመሪያው እስራኤል ዘሥጋ (ሕዝበ እስራኤል) ናቸው። እነዚህም (በሥጋ ዘር) የአብርሃም፣ የይስሐቅ፣ እስራኤል የተባለው የያዕቆብ አሥራ ሁለት ልጆች (ነገዶች) ናቸው። እግዚአብሔር እስራኤል ዘሥጋን ሕዝቤ ብሏቸው፣ ከግብፅ ባርነት አውጥቷቸው፣ ጠላቶቻቸውን እንዲያሸንፉ ረድቷቸው፣ ሕገ ኦሪትን ሰጥቷቸው፣ ብዙ ነቢያትን ልኮላቸው አስተምረዋቸዋል። ሊቀ ነቢያት ሙሴ “አትፍሩ፥ ዛሬ የምታዩአቸውን ግብፃውያንን ለዘላለም አታዩአቸውምና ቁሙ፥ ዛሬ ለእናንተ የሚያደርጋትን የእግዚአብሔርን ማዳን እዩ። እግዚአብሔር ስለ እናንተ ይዋጋል፥ እናንተም ዝም ትላላችሁ(ዘጸ 14:13-15)” እንዳላቸው የቃል ኪዳን ሕዝቦች ስለሆኑ እግዚአብሔር ተዋግቶላቸዋል። በነቢዩ በኢሳይያስም አድሮ “ባሪያዬ እስራኤል፥ የመረጥሁህ ያዕቆብ፥ የወዳጄ የአብርሃም ዘር ሆይ፥ አንተ ከምድር ዳርቻ የያዝሁህ ከማዕዘንዋም የጠራሁህና። አንተ ባሪያዬ ነህ፥ መርጬሃለሁ አልጥልህም ያልሁህ ሆይ፥ እኔ ከአንተ ጋር ነኝና አትፍራ፤ እኔ አምላክህ ነኝና አትደንግጥ፤ አበረታሃለሁ፥ እረዳህማለሁ፥ በጽድቄም ቀኝ ደግፌ እይዝሃለሁ (ኢሳ 41:8-13)” በማለት ይረዳቸው፣ ይጠብቃቸው ነበር።
ፍጻሜው ግን እስራኤል ዘነፍስ ለተባሉ ክርስቲያኖችን (ቤተ ክርስቲያንን) ነው (ገላ 6:16)። የረዳቸውም አንድያ ልጁን ለአርአያነትና ለቤዛነት በመላክ ነው (ዮሐ 3:16)። ቅዱስ ወንጌልን (የክርስቶስን ድምፅ) ሰምተው፣ በስሙ አምነው የተጠመቁትን የመንግሥቱ ወራሾች ይሆኑ ዘንድ በልጅነት ተቀበላቸው። እነዚህ ከሕዝበ እስራኤል ክርስቶስን የተቀበሉትን፣ ከአሕዛብ ያመኑትን፣ እስከ ዘላለምም በስሙ አምነው ክርስቲያን የሚባሉትን ሁሉ ያጠቃልላል። “እስራኤል” ማለት (ትርጉሙ) “እግዚአብሔርን የሚያዩ” ማለት ስለሆነ በሐዲስ ኪዳን ለክርስቲያኖች ሁሉ የሚሆን ምሳሌ ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም “ነገር ግን የእግዚአብሔር ቃል የተሻረ አይደለም። እነዚህ ከእስራኤል የሚወለዱ ሁሉ እስራኤል አይደሉምና… የሥጋ ልጆች የሆኑ የእግዚአብሔር ልጆች አይደሉም ማለት ነው (ሮሜ 9:6-8 ገላ 3:7 29 )” በማለት ይህንን አረጋግጦልናል። ቅዱስ ጴጥሮስም በመልእክቱ “እናንተ ግን ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የጠራችሁን የእርሱን በጎነት እንድትናገሩ የተመረጠ ትውልድ፥ የንጉሥ ካህናት፥ ቅዱስ ሕዝብ፥ ለርስቱ የተለየ ወገን ናችሁ፤ እናንተ ቀድሞ ወገን አልነበራችሁም አሁን ግን የእግዚአብሔር ወገን ናችሁ፤ እናንተ ምሕረት ያገኛችሁ አልነበራችሁም አሁን ግን ምሕረትን አግኝታችኋል (1ኛ ጴጥ 2:9-10)” በማለት እስራኤል ዘነፍስ መሆን በክርስቶስ በማመን ላይ ብቻ የተመሠረተ እንደሆነ አስተምሮናል።
ወተዘከረ ሣህሎ ዘይቤሎሙ ለአበዊነ ለአብርሃም ወለዘርዑ እስከ ለዓለም/ ለአባቶቻችን ለአብርሃምና ለዘሩም እስከ ዘላላሙ የተናገረውን ምህረቱን አሰበ
ይህ የእመቤታችን የጸሎት መደምደሚያ ከብሉይ ኪዳን ቅዱሳት መጻሕፍት፣ ከአብርሃም እስከ ክርስቶስ ካለው ትውልድ ጋር እንዲሁም ለሰው ልጅ ስለተሰጠው የመዳን ተስፋና ፍፃሜውን የሚያስተሳስር (የኪዳናት ጥምረት) ክፍል ነው። እግዚአብሔር አስቀድሞ ለአብርሃም ቃል ኪዳኔንም በእኔና በአንተ መካከል ከአንተም በኋላ ከዘርህ ጋር በትውልዳቸው ለዘላለም ኪዳን አቆማለሁ፥ ለአንተና ከአንተ በኋላ ለዘርህ አምላክ እሆን ዘንድ (ዘፍ 17:7) ብሎ የሰጠው ቃል ኪዳን በክርስቶስ የማዳኑ ሥራ ተፈጽሟል። ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ሲያብራራ “ለአብርሃምና ለዘሩም የተስፋው ቃል ተነገረ ስለ ብዙዎች እንደሚነገር ለዘሮቹም አይልም፤ ስለ አንድ እንደሚነገር ግን ለዘርህም ይላል፥ እርሱም ክርስቶስ ነው (ገላ 3:16)” በማለት ከዘርህ ጋር የተባለው ክርስቶስ መሆኑን ግልፅ አድርጎልናል።
እንዲሁም “ስለዚህ ከሕግ ብቻ ሳይሆን ከአብርሃም እምነት ደግሞ ለሆነ ለዘሩ ሁሉ የተስፋው ቃል እንዲጸና እንደ ጸጋ ይሆን ዘንድ በእምነት ነው፤ እርሱም ለብዙ አሕዛብ አባት አደረግሁህ ተብሎ እንደ ተጻፈ፥ ለሙታን ሕይወት በሚሰጥ የሌለውንም እንዳለ አድርጎ በሚጠራ ባመነበት በአምላክ ፊት የሁላችን አባት ነው (ሮሜ 4:16-18)” በማለት የአብርሃም ልጅነት በእምነት መሆኑን አስተምሯል። በተጨማሪም “እናንተም የክርስቶስ ከሆናችሁ እንኪያስ የአብርሃም ዘር እንደ ተስፋውም ቃል ወራሾች ናችሁ (ገላ 3:29)” ብሎ በክርስቶስ ያመነ ሁሉ የመንግሥቱ ወራሽ መሆኑን አስተምሯል። ስለዚህም ለአብርሃም የገባለት ቃል ኪዳንን አስቦ ከእርስዋ ተወልዶ እንደሚያድነን የተናገረችበት መደምደሚያ ነው። ቤተ ክርስቲያናችንም የተመሠረተችው በዚህ ቃል ኪዳን ፍፃሜ ላይ ነው። እመቤታችን ደግሞ ቃል ኪዳኑ የተፈጸመባት የመመኪያችን ዘውድ ናት።
ስብሐት ለአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ለዓለም ወለዓለመ ዓለም፤ አሜን!