ጸሎተ ሃይማኖት: እንዲህ እናምናለን፤ እንዲህም እንታመናለን!

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤ አሜን

ጸሎት ምስጋና ወይም ልመና ብቻ ሳይሆን የእምነት መግለጫ ነው። እምነቴ ምንድን ነው? ከሌሎች እምነቶችስ እንዴት ይለያል? ብለን ራሳችንን ብንጠይቅ ምላሽ የሚሰጠን ነው። እምነታችሁ ምንድን ነው? ተብለን ብንጠየቅ መልሳችን እርሱ ነው። ምን ብላችሁ ነው የምታምኑት? ብንባል ማስረጃችን እርሱ ነው። እርሱም የእምነታችን መሠረት የሆነው ጸሎተ ሃይማኖት (አንቀጸ ሃይማኖት/Creed of Faith) ነው። ከጥንት እስከ ዛሬ፣ ከዛሬም እስከ ዘለዓለሙ የእኛ መሠረተ እምነት እርሱ ነው። አንድ ሀገር በሕገ መንግሥት እንደሚመራው ሁሉ በእምነት የምንመራበት የእኛ ሕገ ሃይማኖት እርሱ ነው። የሕግጋተ ቤተ ክርስቲያንና የሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ሁሉ የበላይና ምንጫቸው ጸሎተ ሃይማኖት ነው። ጸሎተ ሃይማኖት ዘመናትን የተሻገረና የሚሻገር የእምነታችን መሠረት ነው።

የእምነታችን መጠሪያ የሆነው ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ትርጓሜ ጸሎተ ሃይማኖት ነው። የቀጥተኛይቱና እውነተኛይቱ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ምንነት (substance) የሚገለጠው በጸሎተ ሃይማኖት ነው። ጸሎተ ሃይማኖት ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ የተሰጠች ሃይማኖት መገለጫ ነው። ነቢያት የተናገሩትን፣ ክርስቶስ የሰበከውን፣ ሐዋርያትም ያስተማሩትን እውነተኛ እምነት ጠንቅቆ የሚገልጽልን የእምነታችን ጭብጥ ጸሎተ ሃይማኖት ነው። ጸሎተ ሃይማኖት “እንዲህ እናምናለን፤ እንዲህ እንታመናለን” ብለን በፍጹም ልባችን የምናምነው እምነት፣ በአንደበታችን የምንመሰክረው የማይለወጥ እውነት፣ ዘወትርም የምንጸልየው የኲላዊት ቤተ ክርስቲያን ድምፅ ነው። ጸሎተ ሃይማኖትን ብዙዎቻችን በቃላችን እናውቀዋለን፣ በዘወትር ጸሎት እንደግመዋለን፣ በቅዳሴ ውስጥም በስፋትና በጥልቀት ተብራርቶ እናደምጠዋለን። የያዘውን ጥልቅ የእምነታችንን ምስጢር በሚገባ ያስተዋልን ግን ስንቶቻችን እንሆን? በዚህች የአስተምህሮ ትምህርታዊ ጽሑፍ የጸሎተ ሃይማኖትን አመጣጥ፣ ይዘትና አገልግሎት በአጭሩ እንዳስሳለን።

የጸሎተ ሃይማኖት አመጣጥ

የጸሎተ ሃይማኖት መሠረቱ የብሉይና ሐዲስ ኪዳን ቅዱሳት መጻሕፍት ናቸው። እነዚህም ሕገ ኦሪት፣ ትንቢተ ነቢያት፣ የጌታችን የአምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስብከት፣ የአርአያነትና የቤዛነት ሥራ፣ የቅዱሳን ሐዋርያት ሕግጋትና አስተምህሮ ናቸው። አሁን ያለው ጸሎተ (አንቀጸ) ሃይማኖት በዚህ ይዘትና ቅርጽ የተዘጋጀው በመንፈስ ቅዱስ መሪነት በ325 ዓ.ም. አርዮስን ለማውገዝ በኒቂያ በተሰበሰቡት ሃይማኖታቸው በቀና በ318ቱ (ሠለስቱ ምዕት) ሊቃውንት ነው። አንቀጾቹን በማርቀቁ ሂደት የእስክንድርያውን ሊቀ ጳጳስ እለእስክንድሮስን (Pope Alexander) ተከትሎ የሄደው በወቅቱ ዲያቆን (በኋላ ቅዱስ፣ 20ኛው የእስክንድርያ ፓትርያርክ) አትናቴዎስ ጉልህ ሚና አበርክቷል። ቀጥሎም መንፈስ ቅዱስን ፍጡር (ሕፁፅ) ያለውን መቅዶንዮስን ለማውገዝ በ381 ዓ.ም. በተካሄደው የ150 ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የቁስጥንጥንያ ጉባዔ መንፈስ ቅዱስን የሚመለከቱ አንቀጾች ተካተውበታል። ንስጥሮስን ለማውገዝ በ431 ዓ.ም. በተካሄደው የ200 ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የኤፌሶን ጉባዔ ደግሞ ያለውን ይዘት በማጽናት፣ የመግቢያ አንቀጽ በማከል፣ ማንም እንዳይጨምር እንዳይቀንስ ተደንግጓል። ከዚያ እስከ ዛሬ ድረስ በቅዱሳን አባቶቻችንና እናቶቻችን የእምነት ተጋድሎ ተጠብቆ ቆይቷል። የሦስቱ ዓለም አቀፍ ጉባዔያትና የጸሎተ ሃይማኖትን አመጣጥ ከታች ባለው slide ይመልከቱ።

የጸሎተ ሃይማኖት ይዘት

ጸሎተ ሃይማኖት የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ መሠረት ነው። የእምነታችንን ምንነት የምንገለጸው በአንቀጸ ሃይማኖት ነው። ይህም በተለይ አምስቱን አዕማደ ምስጢራት የሚመለከት ነው። ጸሎተ (አንቀጸ) ሃይማኖት  ምስጢረ ሥላሴን (በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ማመናችንን)፣ ምስጢረ ሥጋዌን (ከሦስቱ አካላት አንዱ ወልድ እኛን ለማዳን (በተዋሕዶ) ሰው መሆኑን ማመናችንን)፣ ምስጢረ ጥምቀትን (በአንዲት ጥምቀት የሥላሴ ልጅነትን የምናገኝ መሆኑን ማመናችንን)፣ ምስጢረ ቁርባንን (ከቅዱስ ቁርባኑ ምስጢር በምታሳትፈን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ማመናችን)፣ ምስጢረ ትንሣኤ ሙታንን (የሙታንን ትንሣኤና የሚመጣውን ዘላለማዊ ሕይወት ተስፋ ማድረጋችንን) የሚገልጽ ነው። እንዲሁም ጸሎተ ሃይማኖት በውስጡ ጸንተው የሚኖሩትን እምነትን፣ ፍቅርንና ተስፋን አዋሕዶ ይዟል። እናምናለን (ወነአምን) የሚለው እምነትን፣ ስለእኛ ስለ ሰዎች እኛን ለማዳን (ወበእንተ መድኃኒትነ) የሚለው እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍቅር፣ ወንሴፎ (ተስፋ እናደርጋለን) የሚለው ተስፋን ይገልፃሉ። ስለዚህም ጸሎተ ሃይማኖት የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ሃይማኖታችን ዶግማ ነው። የጸሎተ ሃይማኖትና የአምስቱ አዕማደ ምስጢራትን ግንኙነት ከታች ባለው slide ይመልከቱ።

የጸሎተ ሃይማኖትን ይዘት ለዚህ ጽሑፍ አቀራረብ እንዲያመች በሰባት አንቀጾች ከፍለን እንመለከታለን።

አንቀጽ 1: በእግዚአብሔር አብ እናምናለን

ጸሎተ ሃይማኖት ሀልዎተ እግዚአብሔርን በመመስከር የሚጀምር ሲሆን አንደኛው አንቀጽ “ነአምን በአሐዱ አምላክ እግዚአብሔር አብ አኃዜ ኲሉ ገባሬ ሰማያት ወምድር ዘያስተርኢ ወዘኢያስተርኢ” የሚለው ነው። ይህም “አኃዜ ኲሉ (ሁሉን የፈጠረ፣ የሁሉ አስገኚ፣ ሁሉን የያዘና የሁሉ ገዥ) አንድ አምላክ በሚሆን በእግዚአብሔር አብ እናምናለን፤ ሰማይና ምድርን የሚታየውንና የማይታየውን የፈጠረ እርሱ ነው” ማለት ነው። የጸሎተ ሃይማኖት የመጀመሪያዎቹ አንቀጾች ነአምን ብለው መጀመራቸው የምናምነውን እምነት ምንነት ስለሚናገሩ ነው። ይህም የመጀመሪያው አንቀጽ ሁሉን በፈጠረ በአንድ አምላክ (One God) የምናምን መሆኑን ያስረዳናል (ማር 12:29)። በምስጢረ ሥላሴ እንደምናውቀው እግዚአብሔር በባሕርይው፣ በመለኮቱ፣ በአገዛዝ፣ በስልጣን፣ በፈቃድ፣ ይህን ዓለም በመፍጠርና በመሳሰሉት አንድ ሲሆን በስም፣ በአካል፣ በግብር ግን ሦስት ነው። እግዚአብሔር አንድነቱ ሦስትነቱን ሳይጠቀልለው፤ ሦስትነቱ አንድነቱን ሳይከፋፍለው በአንድነትና በሦስትነት የሚመሰገን አንድ ሕያው አምላክ ነው ብለን እናምናለን። ይህ የመጀመሪያው አንቀጽ ከሦስቱ አካላት አንዱን አብን የሚገልጽም ነው። ከወልድና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ አምላክ በሆነ፣ ሁሉን በፈጠረ፣ በያዘና በሚገዛ በእግዚአብሔር አብ እናምናለን በማለት። ይህንን የሚያስረዱን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን ከታች ባለው slide ይመልከቱ።

አንቀጽ 2: በአንድ ጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ እናምናለን

ሁለተኛው አንቀጽ “ወነአምን በአሐዱ እግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስ ወልደ አብ ዋሕድ ዘህልው ምስሌሁ እምቅድመ ይትፈጠር ዓለም። ብርሃን ዘእምብርሃን አምላክ ዘእምአምላክ ዘበአማን።  ዘተወልደ ወአኮ ዘተገብረ ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ። ዘቦቱ ኲሉ ኮነ ወዘእንበሌሁሰ አልቦ ዘኮነ ወኢምንትኒ ዘበሰማይኒ ወዘበምድርኒ” የሚል ነው። ይህም  ዓለም ሳይፈጠር ከእርሱ ጋር በነበረ የአብ አንድ ልጅ በሚሆን በአንድ ጌታ [የሁሉ ጌታ/አምላክ ነውና] በኢየሱስ ክርስቶስ እናምናለን። ከብርሃን የተገኘ ብርሃን[ክርስቶስ የዓለም ብርሃን ነውና፣ አንድም ሥላሴ በብርሃን ይመሰላሉና]፤ ከእውነተኛ አምላክ የተገኘ እውነተኛ አምላክ [ወልድ ፍጹም አምላክ ነውና]፤ የተወለደ እንጂ ያልተፈጠረ[አርዮስ በክህደቱ ወልድን ‘የተፈጠረ’ ብሏል፣ ሃይማኖታቸው የቀና 318ቱ ሊቃውንት ደግሞ ‘የተወለደ እንጂ ያልተፈጠረ’ ብለዋል]፤ በባሕርይው ከአብ ጋር የሚተካከል [በባህርይው ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ ነውና]፤ ሁሉ በእርሱ የሆነ [የሁሉ ፈጣሪና ገዥ ነውና]፤ በሰማይም ካለው በምድርም ካለው ያለ እርሱ ግን ምንም ምን የሆነ የለም ማለት ነው። ሁሉ ከእርሱና በእርሱ ለእርሱም ነውና።

ይህ አንቀጽ ከሦስቱ አካላት አንዱ የሆነው ወልድ ላይ የሚያተኩር አንቀጽ ነው። ወልድ ዓለም ሳይፈጠር ከአብ [መቀዳደም በሌለበት መወለድ፣ አባቱ የማይቀድመው ልጅ ሆኖ] ተወለደ ብለን የምናምን መሆኑን የሚያረጋግጥ አንቀጽ ነው። ይህም ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው ቅድመ ዓለም የተወለደው ነው። እርሱ ከብርሃን የተገኘ ብርሃን ነው። ከእውነተኛ አምላክ የተገኘ እውነተኛ አምላክ ነው። እርሱ ተወለደ እንጂ አልተፈጠረም። በባህርይው ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ አምላክ ነው ብለን እናምናለን። አብ አባት ስለሆነ ከወልድ አይበልጥም፣ ወልድም ተወላዲ ስለሆነ ከአብ አያንስም፣ መንፈስ ቅዱስም አያንስም፣ አይበልጥም፣ ትክክል ናቸው። ይህንን ዓለም በመፍጠርም እንዲሁ። “መለኮት ግን አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ አንድ አምላክ አንዲት መንግሥት አንዲት ሥልጣን አንዲት አገዛዝ ነው” እንዲል (ቅዳሴ ማርያም)። ይህንን የሚያስረዱን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን ከታች ባለው slide ይመልከቱ።

አንቀጽ 3: ስለኛ ስለ ሰዎች እኛን ለማዳን ከሰማይ ወረደከቅድስት ድንግል ማርያምም ሰው ሆነ።

ሦስተኛው የጸሎተ ሃይማኖት አንቀጽ “ዘበእንቲአነ ለሰብእ ወበእንተ መድኃኒትነ ወረደ እምሰማያት። ተሰብአ ወተሠገወ እመንፈስ ቅዱስ ወእማርያም እምቅድስት ድንግል። ኮነ ብእሴ ወተሰቅለ በእንቲአነ በመዋዕለ ጲላጦስ ጴንጤናዊ ሐመ ወሞተ ወተቀብረ ወተንሥአ እሙታን አመ ሣልስት ዕለት በከመ ጽሑፍ ውስተ ቅዱሳት መጻሕፍት። ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት ወነበረ በየማነ አቡሁ ዳግመ ይመጽእ በስብሐት ይኰንን ሕያዋነ ወሙታነ ወአልቦ ማኅለቅት ለመንግሥቱ” የሚለው ምስጢረ ሥጋዌን የሚያስረዳን ነው። ይህም ቅድመ ዓለም ከአብ የተወለደው ወልድ የዘመኑ ፍፃሜ ሲደርስ እኛን ለማዳን ከሰማይ መውረዱን፣ ከቅድስት ድንግል ማርያምም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ (በተዋሕዶ – የፈጠረውን ሥጋ ተዋሕዶ) መወለዱን የሚናገር ነው። ዘበእንቲአነ ለሰብእ ወበእንተ መድኃኒትነ (ስለእኛ ሰለስዎች እኛን ለማዳን) የሚለው ሐረግ ሰው የሆነው ለእኛ መዳን ሲል መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው።

እመንፈስ ቅዱስ (በመንፈስ ቅዱስ ግብር) ያለው ያከበረ፣ ያዋሐደ እርሱ መንፈስ ቅዱስ ነውና ነው። ወእማርያም እምቅድስት ድንግል (ከቅድስት ድንግል ማርያም) የሚለው ደግሞ ከሥጋዋ ሥጋን ከነፍሷ ነፍስን ነስቶ ሰው መሆኑን ያመለክታል። አባ ሕርያቆስም በቅዳሴው “ፍቅር ሰሀቦ ለወልድ ኀያል እመንበሩ ወአብጽሖ እስከ ለሞት፤ ኀያል ወልድን ፍቅር ከዙፋኑ ሳበው እስከ ሞትም አደረሰው” (ቅዳሴ ማርያም) እንዳለው ስለእኛ ተወለደ። ቅዱስ ቄርሎስ “ወረደ ከመ ያዕርገነ ለነ ኀበ ሀገሩ አርያማዊ ኀበ ሀሎ አቡሁ፤ የባሕርይ አባቱ ካለበት ሰማያዊ ሀገሩ ያገባን ዘንድ እርሱ ወደ እኛ ወረደ” በማለት እንደ ተናገረ እኛን ለማዳን ተወለደ። ልደቱም ቅዱስ ኤፍሬም “ኦ ዝ መንክር ልደተ አምላክ እማርያም እምቅድስት ድንግል/ ልዩ ከሆነች ድንግል ማርያም ይህ የአምላክ መወለድ ምን ይደንቅ” እንዳለው ድንቅ ተብሎ የሚገለጽ ነው።

ሰው ሆኖም በጴንጤናዊው በጲላጦስ ዘመን ስለኛ መከራ መቀበሉን፣ በመስቀል መሰቀሉን፣ መሞቱንና መቀበሩን የምናምን መሆናችንን የምንገልጽበት አንቀጽ ነው። በሦስተኛውም ቀን ከሙታን መነሣቱን፣ ይህም ቅዱሳን መጻሕፍት ያረጋገጡልን እውነት እንደሆነና ትንሣኤውንም እንደምናምን የምንመሰክርበት አንቀጽ ነው። ከትንሣኤው በኋላም ለሐዋርያት እየተገለጸላቸውና እያስተማራቸው ቆይቶ በአርባኛው ቀን ወደ ሰማይ ማረጉንና በአባቱም ቀኝ (በኃይልና ክብር) መቀመጡን እናምናለን። በዕርገቱ የተገለጡት ቅዱሳን መላእክት “ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ የወጣው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ሲሄድ እንዳያችሁት፥ እንዲሁ ይመጣል” እንዳሉት ለሁሉም (በሕያዋንና በሙታን ሊፈርድ- ለጻድቃንም በኃጥአንም ሊፈርድ) እንደየሥራው ዋጋውን ለመክፈል ዳግመኛ እንደሚመጣም እናምናለን። የእርሱ መንግሥትም ፍጻሜ የሌለው ዘላለማዊ መሆኑን እንደምናምን የምናረጋግጥበት አንቀጽ ነው። በአጠቃላይ ይህ አንቀጽ ነገረ ድኅነትን (ከጌታችን ፅንሰት እስከ ዳግም ምጽአት) የሚመለከት ነው። ይህንን የሚያስረዱን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን ከታች ባለው slide ይመልከቱ።

አንቀጽ 4: በመንፈስ ቅዱስ እናምናለን

ይህ አንቀጽ ከሦስቱ አካላት አንዱ የሆነውን መንፈስ ቅዱስን የሚመለከት አንቀጽ ነው። ይዘቱም “ወነአምን በመንፈስ ቅዱስ እግዚእ ማሕየዊ ዘሠረፀ እምአብ ንስግድ ሎቱ ወብሰብሖ ምስለ አብ ወወልድ ዘነበበ በነቢያት” የሚል ሲሆን ትርጉሙ በመንፈስ ቅዱስ እናምናለን፤ እርሱ ጌታ፣ ሕይወትን የሚሰጥ፤ ከአብ የሠረጸ፤ ከአብና ከወልድ ጋራ እንሰግድለታለን፣ እናመሰግነዋለን፣ እርሱ  በነቢያት የተናገረ ነው ማለት ነው። መንፈስ ቅዱስም እናምናለን ስንል ልክ በአብና በወልድ እንደምናምነው ከሦስቱ አካላት አንዱ በሆነውና ከአብና ከወልድ ጋር በመለኮት፣ በአገዛዝ፣ በስልጣን አንድ በሆነው በመንፈስ ቅዱስም እናምናለን ማለታችን ነው። መንፈስ ቅዱስን “እግዚእ/ጌታ” ስንል አምላክ፣ ፈጣሪ፣ ገዢ መሆኑን እየመሰከርን ነው። መንፈስ ቅዱስ ማሕየዊ (ሕይወትን የሚሰጥ) ነው ስንል መንፈሳዊ ሕይወትን የምናገኘው በእርሱ መሆኑን የሚያመለክት ነው። ይህም ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ በጥምቀት ስንወለድ የምናገኘው መንፈሳዊ ሕይወት (ልጅነት) ነው። አንድም ከቅዱስ ቁርባን ምስጢር ስንሳተፍ የምናገኘው ዘላለማዊ ሕይወት ነው። መንፈስ ቅዱስ ለቤተ ክርስቲያንም ሕይወቷ ነው። የቤተ ክርስቲያን ልደት የሚባለው በዓለ ጰራቅሊጦስ ነውና። ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያንም ሁሉ የሚከብሩት በመንፈስ ቅዱስ ነውና።

በተጨማሪም ይህ አንቀጽ መንፈስ ቅዱስ የሚሠርጸው ከአብ ብቻ እንደሆነ የሚናገር ነው። ከወልድም ይሠርጻል ብለው የሚያምኑ አሉና። ይህ አንቀጽ መንፈስ ቅዱስን ሕፁፅ (ፍጡር) በማለቱ በጉባዔ ቁስጥንጥንያ የተወገዘው መቅዶንዮስ እንዳለው ሳይሆን መንፈስ ቅዱስ አምላክ፣ ፈጣሪ የሆነና ከአብና ከወልድ ጋር አንድ አምላክ ብለን የምናመልከውና የምንሰግድለት መሆኑን የሚገልጽ ነው። በነቢያትም አድሮ የተናገረው እርሱ መሆኑን የሚያረጋግጥ አንቀጽ ነው። በነቢያት ስንል በብሉይ ኪዳን የነበሩ ዐበይትና ደቂቀ ነቢያትን ብቻ ማለታችን አይደለም። በዘመነ ብሉይ በነበሩ ቅዱሳን ነቢያትና መምህራን፣ በሐዲስ ኪዳንም በነበሩ ቅዱሳን ሐዋርያትና ቅዱሳን አበው ሁሉ ማለታችን ነው እንጂ። በቅዱሳን ነቢያት አድሮ የተናገረው፣ በቅዱሳን ሐዋርያትም ላይ የወረደው አንዱ መንፈስ ቅዱስ ነው። በእነርሱ አድሮ የተናገረው ምስጢርንም የገለጠው መንፈስ ቅዱስ ነው ብለን እናምናለን። ስለዚህ እነርሱ የጻፏቸው ቅዱሳት መጻሕፍት ሁሉ የእነርሱ ቃል ሳይሆኑ የመንፈስ ቅዱስ ቃል ናቸው ብለን እናምናለን። በእነርሱ አድሮ የተናገረው እርሱ ነውና (2ኛ ጴጥ 1:21 2ኛ ጢሞ 3:16)። ዛሬም ቤተ ክርስቲያን የምታከናውነውን መንፈሳዊ አገልግሎት የሚመራው መንፈስ ቅዱስ ነው ብለን እናምናለን። ይህንን አንቀጽ የሚያብራሩልን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን ከታች ባለው slide ይመልከቱ።

አንቀጽ 5: በአንዲት ቅድስት፣ ሐዋርያዊትና ኲላዊት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን

ነገረ ቤተ ክርስቲያንን የሚመለከተው አንቀጽ “ወነአምን በአሐቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ላዕለ ኲሉ ጉባኤ ዘሐዋርያት” የሚል ሲሆን ትርጉሙም ከሁሉም በላይ በምትሆን የሐዋርያት ጉባዔ በምትሆን በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን ማለት ነው። ጌታችን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አካሉ እንድትሆን አድርጎ አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ በምትለው አለት ላይ መሥርቷታል። ይህ አንቀጽ አራቱን የቤተ ክርስቲያን ባህርያት የሚገልጽ አንቀጽ ነው። ቤተ ክርስቲያን አንዲት (አሐቲ – ያልተከፈለች(በ451 ዓም እንግዳ ትምህርት ተወግዞ ተለየ እንጂ ቤተ ክርስቲያን አልተከፈለችም)፣ ያልተቋረጠች (ቀጣይነት ያላት)፣ ያልተለወጠች(ሳትለወጥ የቀጠለች)) ናት። ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት ስንል በአንዱ ክርስቶስ የተመሠረተች፣ አንዲት እምነትን የምታምንና የምታስተምር፣ ከአንድ ሰማያዊ ምስጢር የምታሳትፍ፣ በአፀደ ሥጋና በአፀደ ነፍስ ያሉ ክርስቲያኖች በክርስቶስ ያላቸው አንድነት፣ ወደ አንዲት መንግሥተ ሰማያት የምታስገባ ማለታችን ነው።

ቤተ ክርስቲያን ቅድስት (አንተ ውእቱ ክርስቶስ ወልደ እግዚአብሔር ሕያው በሚለው በሰማያዊ መገለጥ በተገኘው እውነት (ቅዱስ ቃል) ላይ የተመሠረተች፣ በምስጢር (ከጎኑ በፈሰሰው ውኃና ደም) የመሠረታት) ናት። ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊት (በአስተምህሮ፣ በተልዕኮና በሲመት ሀረግ) ናት። ቤተ ክርስቲያን ኲላዊት ናት። ይህም ማለት ቤተ ክርስቲያን የሁሉም፣ ለሁሉም፣ እስከ ዘለዓለም የምትኖር፣ ምሉዕ (ምንም የጎደላት የሌለ)፣ ከሁሉ በላይ የምትሆን፣ ክርስቶስ ያስተማረውን በሙሉ (ምንም ሳታጓድል) የምታምንና የምታስተምር ናት ማለት ነው። ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ነገረ ቤተ ክርስቲያንን የገለፀበት ትምህርት እጅግ ድንቅ ነው። ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ አካሉ (ኤፌ 1:22-23 4:15-16)፣ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ (ኤፌ 2:19-22)፣ የክርስቶስ ሙሽራ (ኤፌ 5:25-32)፣ የእግዚአብሔር ቤተሰብ (ኤፌ 2:13)፣ በክርስቶስ የተጠሩት ኅብረት (1ኛ ቆሮ 1:2)፣ የእውነት ዐምድ (1ኛ ጢሞ 3:15)፣ የክርስቶስ መልእክተኞች (ሐዋርያት) ማኅበር (2ኛ ቆሮ 5:18-20) ናት።

የቤተ ክርስቲያን ዓላማ ክርስቲያኖችን ከቅዱስ ቁርባን ምስጢር በማሳተፍ ለእግዚአብሔር መንግሥት ማብቃት ነውና ይህ አንቀጽ በተለይ ምስጢረ ቁርባንን የሚመለከት ነው። በአንዲት፣ ቅድስት፣ ሐዋርያዊትና ኲላዊት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን ስንል ክርስቶስ ራሱ የመሠረታት መሆኑን፣ የምታምነውና የምታስተምረው ክርስቶስ ያስተማረውን እውነት መሆኑን፣ በእርስዋ የሚፈጸሙ ሰባቱ ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያን በአንድ መንፈስ ቅዱስ የሚከብሩ መሆኑን እናምናለን ማለታችን ነው እንጂ ‘ቤተ ክርስቲያንን (ተቋሙን ወይም ሕንፃውን) እናመልካለን’ ማለት አይደለም። ይህንን አንቀጽ የሚያስረዱን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን ከታች ባለው slide ይመልከቱ።

አንቀጽ 6: ኃጢአት በሚሰረይባት በአንዲት ጥምቀት እናምናለን

ምስጢረ ጥምቀትን የሚመለከተው አንቀጽ “ወነአምን በአሐቲ ጥምቀት ለሥርየተ ኃጢአት” የሚል ሲሆን ትርጉሙም ኃጢአት በሚሰረይባት በአንዲት ጥምቀት እናምናለን ማለት ነው። ይህ በቀጥታ የክርስትና መግቢያ በር ከሆነችው ከምስጢረ ጥምቀት ጋር የሚገናኛኝ አንቀጽ ነው። ጌታችን ምስጢረ ጥምቀትን በትምህርት ለኒቆዲሞስ አስተምሮ፣ በተግባር በዮርዳኖስ ተጠምቆ አብነት ሆኖ፣ በትዕዛዝ ለሐዋርያት በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጥምቁ ብሎ ሠርቷታል። ይህ አንቀጽ ጥምቀት በሚታይ አገልግሎት የማይታይ ጸጋን (የእግዚአብሔር ልጅነትን) የምታስገኝ መሆኗን፣ ይህች የሥላሴን ልጅነት የምታስገኘው ጥምቀት አንዲት መሆኗን፣ የኃጢአትም ማስተሥረያ መሆኗን የሚያረጋግጥ አንቀጽ ነው። ጥምቀት አንዲት ናት ስንል ሁላችንም በጸሎተ ሃይማኖት የሰፈረውን አንዲት እምነት አምነን የምንጠመቅ መሆናችንን፣ ሁላችንም በአንድ አምላክ (በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም) የምንጠመቅ መሆኑን፣ የሁላችንም ጥምቀት የሥላሴ ልጅነት የምታስገኝ መሆኗን የሚያመለክት ነው። ቀደምት አበው ቅዱሳን የተጠመቁት ጥምቀት እኛም የተጠመቅናት ጥምቀት አንድ ናቸው የምንለው በዚህ ነው። እኛም ምስጢረ ጥምቀትን በተመለከተ እንዲህ እናምናለን፣ እንዲህም እንታመናለን።

በተጨማሪም ጥምቀት አንዲት ናት ስንል የማትደገም ምስጢር ናት ማለታችን ነው። ከአባትና ከእናት በሥጋ አንድ ጊዜ ብቻ እንደምንወለደው ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ከማኅፀነ ዮርዳኖስም በጥምቀት አንድ ጊዜ ብቻ የምንወለድ ነንና። ለሥርየተ ኃጢአት (ኃጢአት በሚሰረይባት) የሚለውም በአንዲት ጥምቀት አሮጌውን ሰው ትተን አዲስ ፍጥረት እንደምንሆን የሚያመለክት ነው። ቅዱስ ጴጥሮስ መንፈስ ቅዱስ በወረደባት በዕለተ ጰራቅሊጦስ በሰበከው ስብከት “ንስሐ ግቡ፥ ኃጢአታችሁም ይሰረይ ዘንድ እያንዳንዳችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ፤ የመንፈስ ቅዱስንም ስጦታ ትቀበላላችሁ።” (ሐዋ 2:38) በማለት ጥምቀት ኃጢአትን እንደምታስተሰርይ ተናግሯል። ጥምቀት ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ዳግመኛ እንድንወለድ (ዮሐ 3:5)፣ ከክርስቶስ ጋር ተቀብረን እንድንነሳ (ቆላ 2:12)፣ በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ (ሮሜ 6:3-5)፣ ከአሮጌው ፍጥረት ወደ አዲስ ፍጥረት እንድንሸጋገር (2ኛ ቆሮ 5:17)፣ ክርስቶስን እንድንለብሰው (ገላ 3:27) የምታደርግ ልዩ ምስጢር ናት። ይህን ምስጢር ነው አባቶቻችን ለሥርየተ ኃጢአት (ኃጢአት በሚሰረይባት) በማለት የገለጹት። ይህንን አንቀጽ የሚያስረዱን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን ከታች ባለው slide ይመልከቱ።

አንቀጽ 7: የሙታንንም መነሣት ተስፋ እናደርጋለን፤ የሚመጣውንም ሕይወት ለዘላለሙ

ይህ አንቀጽ ምስጢረ ትንሣኤ ሙታንን የሚመለከት ነው። የጸሎተ ሃይማኖት የመጨረሻው አንቀጽ “ወንሴፎ ትንሣኤ ሙታን ወሕይወተ ዘይመጽእ ለዓለመ ዓለም” የሚል ሲሆን ትርጉሙም የሙታንንም መነሣት ተስፋ እናደርጋለን፤ የሚመጣውንም ሕይወት ለዘላለሙ ማለት ነው። በቀደሙት አንቀጾች ወነአምን (እናምናለን) ሲል መጥቶ እዚህ ላይ ወንሴፎ (ተስፋ እናደርጋለን) ማለቱ ትንሣኤ ሙታን (ትንሣኤ ዘጉባዔ) ወደፊት በተስፋ የምንጠባበቀው መሆኑን ለማመልከት ነው። ስለዚህም ክርስቶስ ለሙታን ሁሉ በኩር ሆኖ ተነሥቶ አብነት ሆኖናል። ከትንሣኤ ዘጉባዔም በኋላ የሚመጣ ዘላለማዊ ሕይወትን ተስፋ እንደምናደርግ ይህ አንቀጽ ያስረዳናል። የሥጋ ሞት የሕይወት መጨረሻ (ማብቂያ) አይደለም፣ መሻገሪያ እንጂ። ምክንያቱም የማትሞት የማትበሰብስ ነፍስ በውስጣችን አለችና። ከሥጋ ጋር የማትሞትና የማትጠፋ ነፍስ በሥጋችን ውስጥ እንዳለች እናስተውል እንዲል አመክንዮ ዘሐዋርያት። በትንሣኤ ዘጉባዔም እውነተኛ የእግዚአብሔር ፍርድ ትደረጋለች፣ እያንዳንዱም እንደየሥራው ይከፈለዋል (ራእይ 20:11-13)። ከዚያም በኋላ በአዲሲቷ ኢየሩሳሌም የሚመጣው ተብሎ የተገለጸው፣ በእግዚአብሔር መንግሥት ዘላለማዊ ሕይወት እንዳለ እናምናለን።

ይህ አንቀጽ መጨረሻ ላይ መቀመጡ አንድም በመጨረሻው ዘመን የሚፈጸም ስለሆነ ነው። አንድም የእምነታችን መደምደሚያ (ማሠሪያ) አንቀጽ ስለሆነ ነው። ያለ ትንሣኤ ሙታን እምነታችን ከንቱ ናት። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ትንሣኤ ሙታንስ ከሌለ ክርስቶስ አልተነሣማ፤ ክርስቶስም ካልተነሣ እንግዲያስ ስብከታችን ከንቱ ነው እምነታችሁም ደግሞ ከንቱ ናት፤ ደግሞም ክርስቶስን አስነሥቶታል ብለን በእግዚአብሔር ላይ ስለመሰከርን ሐሰተኞች የእግዚአብሔር ምስክሮች ሆነን ተገኝተናል፤ ሙታን ግን የማይነሡ ከሆነ እርሱን አላስነሣውም። ሙታን የማይነሡ ከሆነ ክርስቶስ አልተነሣማ፤ ክርስቶስም ካልተነሣ እምነታችሁ ከንቱ ናት፤ እስከ አሁን ድረስ በኃጢአታችሁ አላችሁ። እንግዲያስ በክርስቶስ ያንቀላፉት ደግሞ ጠፍተዋላ። በዚች ሕይወት ብቻ ክርስቶስን ተስፋ ያደረግን ከሆነ፥ ከሰው ሁሉ ይልቅ ምስኪኖች ነን።” (1ኛ ቆሮ 15:13-19) በማለት እንዳስተማረው የሙታን ትንሣኤ ከሌለ እምነታችን ከንቱ ናት። ይህንን አንቀጽ የሚያስረዱን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን ከታች ባለው slide ይመልከቱ።

የጸሎተ ሃይማኖት አገልግሎት

ጸሎተ ሃይማኖት የሐዋርያዊት እምነታችን ማረጋገጫ ነው። እኛ የምናምነው እምነት የቀደሙት አባቶቻችን ያመኗት እምነት መሆኗን የምናረጋግጥበት የእምነት መለኪያ እውነተኛ ሚዛን ጸሎተ ሃይማኖት ነው። ጸሎተ ሃይማኖት  የመንፈሳዊ አገልግሎቶች ሁሉ መሠረት ነው። የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ አምልኮ የተመሠረተው በጸሎተ ሃይማኖት በሠፈረው እምነታችን ላይ ነው። ከዘወትር ጸሎት ጀምሮ፣ ሥርዓተ ቅዳሴን ጨምሮ ያሉት የሥርዓተ አምልኮ አገልግሎቶች ሁሉ በዚህ እምነታችን ላይ የተመሠረቱ ናቸው። ጸሎተ ሃይማኖት  የክርስትና አስተምህሮ መመሪያም ነው። የክርስትና አስተምህሮ ማዕከል ጸሎተ ሃይማኖት ነው። የክርስትና አስተምህሮ ዓላማ የሰው ልጆች በጸሎተ ሃይማኖት የተቀመጠውን እምነት እንዲያምኑ፣ በዚህ እምነት ላይ የታነጸውን ሥርዓተ አምልኮ እንዲፈጽሙና ለመንግሥተ ሰማያት እንዲበቁ ማስቻል ነው።  

ጸሎተ ሃይማኖት  የክርስቲያናዊ አንድነታችን መገለጫ ነው። ከሌሎች አኃት አብያተ ክርስቲያናት ጋር አንድ መሆናችን ወይም ከሌሎች ቤተ እምነቶች መለየታችን የሚታወቀው በመሠረተ እምነት ነው። በመሠረተ እምነት ላይ ተለያይተን በሌሎች ጉዳዮች አንድ ልንሆን አንችልም። በመሠረተ እምነት አንድ ከሆንን ደግሞ ሌሎች ልዩነቶች አይለያዩንም። ክርስትና ስንነሳ (ስናነሳ) – ወደ ቤተ ክርስቲያን አንድነት ስንጨመር – የምንመሰክረው (የምንጸልየው) ይህንን ጸሎተ ሃይማኖት ነው። ጸሎተ ሃይማኖት  የኦርቶዶክሳዊት እምነት መጠበቂያ ነው። የአንድ አስተምህሮ እውነተኛነት የሚመዘነው በዚህ በጸሎተ ሃይማኖት ላይ በሠፈሩት አንቀጾች ይዘት መሠረት ነውና። ልክ አባቶቻችን እነ አርዮስንና መቅዶንዮስን አውግዘው እምነታቸውን በጸሎተ ሃይማኖት እንዳጸኑት ዛሬ እኛም እምነታችንን የምንጠብቀው (ዕቅበተ እምነት የምናከናውነው) በጸሎተ ሃይማኖት ነው።

መደምደሚያ

ጸሎተ ሃይማኖት ድቅድቅ ጨለማ በሞላው ዓለም እያበራን ወደ ሕይወት የምንጓዝበት የብርሃን ፋና ነው። ጸሎተ ሃይማኖት የመንፈሳዊ ሕይወታችን መራኄ ፍኖት (compass) ነው። ጸሎተ ሃይማኖት አባቶቻችን ሐዋርያት ያቆዩልንን እውነት የምንጠብቅበት የእምነት ጋሻችን ነው። ጸሎተ ሃይማኖት ንጽሕት እምነታችንን ትውልድን የሚያሻግርና ትውልድን ከትውልድ የሚያስተሳስር የእምነት ሀረግ ነው። ጸሎተ ሃይማኖት አዕማደ ምስጢራትንና ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያንን የምንረዳበት መክፈቻ ቁልፍ ነው። ጸሎተ ሃይማኖት እምነታችን ንጽሕትና የማትናወጽ ሆና የቆመችበት ጽኑዕ አለት ነው። ጸሎተ ሃይማኖት አባቶቻችን በጥበብ ያነጹት የማይናወጥ ግንብ የተተከለበት፣ የእውነተኛው የአስተምህሮ ቅፅር የሚጠበቅበት የእምነት ድንበር ነው። ጸሎተ ሃይማኖት የምንጠቅሰው መዝገብ ብቻ ሳይሆን የምንኖረው የክርስትና ሕይወት፣ የምንጋደልለት እውነትና የዘላለም ሕይወትን የምናገኝበት እምነት ነው። ጸሎተ ሃይማኖት እውነት ያሸነፈችበትና የምታሸንፍበት የድል ዓርማ ነው። ስለዚህ ጸሎተ ሃይማኖትን በሚገባ ልንረዳው፣ የእውነተኛ አስተምህሮ መለኪያ አድርገን ልንጠቀምበት፣ መንፈሳዊ ማንነታችንን ልናንጽበት፣ ለትውልድ ልናሻግረው፣ በየዕለቱ ልንጸልየው፣ በሕይወት ልንኖረውና በጽናት ልንጋደልለት የሚገባ የእምነታችን መሠረት ነው።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር