ሕግጋተ ወንጌል (ክፍል ፫): እግዚአብሔር የመሠረተውን ቅዱስ ጋብቻ አታፍርስ

ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሦስተኛዋ ሕገ ወንጌል “ሚስቱን የሚፈታት ሁሉ የፍችዋን ጽሕፈት ይስጣት ተባለ። እኔ ግን እላችኋለሁ፥ ያለ ዝሙት ምክንያት ሚስቱን የሚፈታ ሁሉ አመንዝራ ያደርጋታል፥ የተፈታችውንም የሚያገባ ሁሉ ያመነዝራል (ማቴ 5:31-32 ሉቃ 16:18)” በማለት አስቀደማ ፍጽምት ተደርጋ ተሠርታ የነበረችውን የጋብቻን ሕግ ወደ ቀደመ ክብሯ መልሷታል። ጌታችን ያለ ዝሙት ምክንያት ሚስቱን የሚፈታ ሁሉ አመንዝራ ያደርጋታል ሲል በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚፈፀመው የቅዱስ ጋብቻ ቃል ኪዳን እስከሞት የሚጸና መሆኑንና ይህ ቃል ኪዳን ሊፈርስ የሚችለው በግብር በሚፈፀመው የዝሙት ኃጢአት (አመንዝራነት) ምክንያት ብቻ መሆኑን ሲያስተምር ነው።

ከዝሙት ውጭ በሆነ ምክንያት ሚስቱን የሚፈታ አመንዝራ ያደርጋታል። ምክንያቱም ከዝሙት ውጭ በሆነ ምክንያት የሚደረግን ፍቺ እግዚአብሔር ስለማይፈቅደው በሰው ዘንድ ‘ፍቺ ተፈፅሟል’ ቢባልም የጋብቻ ቃል ኪዳኑ በእግዚአብሔር ዘንድ የጸና ነው። ስለዚህ ያለ ዝሙት ምክንያት የፈታው ሌላ ሲያገባ አመንዝራ ይሆናል፣ የተፈታችውም ሌላ ስታገባ አመንዝራ ትሆናለች። ለዚህም ያለ ዝሙት ምክንያት የፈታ(ች)ው ተጠያቂነት አለበ(ባ)ት ሲል ነው። ያለ ዝሙት ምክንያት የተፈታ(ች)ውን የሚያገባም ሁሉ ያመነዝራል (ታመነዝራለች)፣ ምክንያቱም የመጀመሪያው ጋብቻ በእግዚአብሔር ዘንድ የጸና ነውና። ስለዚህ ያለ ዝሙት ምክንያት የፈታውን ወይም የተፈታችውን ማግባት በትዳር ያለ(ች)ውን እንደማግባት ይቆጠራልና አመንዝራነት ነው።

በተለይም ‘አልተጋባንም ግን አብረን መኖር ጀምረናል’ በሚባልበት፣ ፍቺ በተንሰራፋበት፣ ትዳርን ማፍረስና ፍቺን መፈጸም እንደቀላልና የተለመደ ነገር በሚወሰድበት፣ ሳይፋቱ ተለያይቶ መኖር እየበዛ በመጣበት፣ ‘ተፋተናል ግን አልተለያየንም’ እየተባለ በድፍረት በየሚዲያው በሚወራበት በዚህ ዘመን ላለን ሰዎች ይህንን ሕግ ማስታወስ እጅግ አስፈላጊ ነው። “ከዚህ ወገን ጋር የተጋባህ ተፋታ!” እየተባለ በአደባባይ የጥላቻ ቅስቀሳ በሚደረግበት ዘመን የቅዱስ ጋብቻን ክብር የማስተማር ታላቅ ኃላፊነት አለብን። ከዚህም አልፈን ቅዱስ ጋብቻን የዝምድና መመሥረቻ፣ የሀብት ማደላደያ፣ ወደ ሰለጠነው ዓለም መሻገሪያ ላደረግንና ፍቺን መዳረሻ አድርገን ትዳርን ለምንመሠርት ለእኛ ፍጽምት የሆነች የጋብቻ ሕግን የምትመለከተውን ሕገ ወንጌል ማስተማር ይገባል። ስለዚህ እኛም በዚህች የአስተምህሮ ጽሑፍ ይህችን ሦስተኛዋን ሕገ ወንጌል እንዳስሳለን።

ቅዱስ ጋብቻ እግዚአብሔር የመሠረተው መንፈሳዊ ተቋም ነው።

በመጀመሪያ ሊታወቅ የሚገባው እውነት ቅዱስ ጋብቻ እግዚአብሔር የመሠረተው ቅዱስ ተቋም መሆኑ ነው። ቅዱስ ጋብቻን የሚመለከቱ ሕግጋት ሁሉ መሠረት ይህ ነው። በቅዱስ መጽሐፍ እንደሰፈረውና ብዙዎቻችን ስንማር እንዳደግነው “እግዚአብሔር አምላክም በአዳም ከባድ እንቅልፍን ጣለበት፥ አንቀላፋም፤ ከጎኑም አንዲት አጥንትን ወስዶ ስፍራውን በሥጋ ዘጋው። እግዚአብሔር አምላክም ከአዳም የወሰዳትን አጥንት ሴት አድርጎ ሠራት፤ ወደ አዳምም አመጣት። አዳምም አለ ‘ይህች አጥንት ከአጥንቴ ናት፥ ሥጋም ከሥጋዬ ናት፤ እርስዋ ከወንድ ተገኝታለችና ሴት’ ትባል። ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል፥ በሚስቱም ይጣበቃል፤ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ (ዘፍ 2:21-25)” በማለት በተገለጸው መሠረት ነው ይህ ቅዱስ ተቋም የተመሠረተው። ቅዱስ ጋብቻ “ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሉአት” የሚለውን አምላካዊ ትዕዛዝ የሚፈፀምበት፣ ቅዱሳን የሚወለዱበት፣ በምድር ላይ ያለችው ቤተ ክርስቲያን የምትቀጥልበት መንገድ ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ታሪካቸው የሠፈረው አዳምና ሔዋን፣ አብርሃምና ሣራ፣ ይስሐቅና ርብቃ፣ ያዕቆብና ራሄል፣ ቦዔዝና ሩት፣ ሕልቃናና ሐና፣ ዘካርያስና ኤልሳቤጥ፣ አቂላና ጵርስቅላ እና ሌሎችም የተባረከ ትዳር የነበራቸው ዋኖቻችን ናቸው።

ይህ መንፈሳዊ ተቋም (ቅዱስ ጋብቻ) የተመሠረተው የሰው ልጅ ከመውደቁ አስቀድሞ ነው። የሰው ልጅ ውድቀትም ይህንን ተቋም ጎዳው እንጂ አላጠፋውም። ለአዳም ሔዋን፣ ለሔዋንም አዳም እንደሚያስፈልጉ አውቆ አዳምን ከአፈር የሠራው፣ ሔዋንንም ከአዳም አጥንት ሠርቶ ወደ አዳም ያመጣት እግዚአብሔር ነው። ለአንድ አዳም አንዲት ሔዋንን፣ ለአንዲት ሔዋንም አንድ አዳምን ፈጥሮ ቅዱስ ጋብቻን የሠራው እግዚአብሔር ነው። ሁለቱም ከአንድ ሥጋና አጥንት ተገኝተው አንድ ሥጋ እንዲሆኑ ያደረገ እግዚአብሔር ነው። ይህንንም ያደረገው በሕይወታቸው ዘመን ሁሉ አብረው ሆነው “ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሉአት” የተባለውን አምላካዊ ቃል ይፈጽሙ ዘንድ ነው። እንግዲህ እግዚአብሔር ቅዱስ ጋብቻን እንዲህ ፍጹም አድርጎ ራሱም በአዳምና በሔዋን መካከል ምስክር ሆኖ ነው መሠረተው። የቀደመችው የጋብቻ ሕግም “መፋታት” የሌለባት ፍጽምት የሆነችውና እስከሞት ድረስ የምትጸናው የጋብቻ ቃል ኪዳን ናት። በዚህም መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ሙሽሮች የፍቅር ማሠሪያ በሆነው በእግዚአብሔር ፊት በቤተ ክርስቲያን ቆመው እንደሚከተለው ቃለ መሐላ እንዲፈጽሙ ታደርጋለች።

ሙሽራው: “እኔ [ሙሽራው] [ሙሽሪትን] የሕግ ሚስት ትሆነኝ ዘንድ ወድጄ ተቀብያታለሁ። ስለዚህም ከዛሬ ጀምሮ በሥራዋ ሁሉ በተቻለኝ እረዳታለሁ። በሕመሟና በጤናዋ፣ በደስታዋና በኃዘንዋም ጊዜ ከእርስዋ ጋር እሆናለሁ። መከነች፣ ሰነፈች በማለት ይህንን በመሳሰለው ምክንያት ሁሉ በልዑል እግዚአብሔር ትዕዛዝ ከእርሷ በሞት እስክለይ አልተዋትም፤ ወድጄ ተቀብያታለሁና። ስለዚህም በእግዚአብሔርና በተቀደሰችው በኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ጉባዔ ፊት በመሐላ ቃሌን እሰጣለሁ።”

ሙሽራዋ: “እኔ [ሙሽሪት] [ሙሽራውን] የሕግ ባል ይሆነኝ ዘንድ ወድጄ ተቀብዬዋለሁ። ስለዚህም ከዛሬ ጀምሮ በሥራው ሁሉ በተቻለኝ እረዳዋለሁ። በኃዘኑና በደስታው፤ በሕመሙና በጤናው ጊዜ ከእርሱ ጋር እሆናለሁ። በልዑል እግዚአብሔር ትዕዛዝ ከእርሱ በሞት እስክለይ ድረስ ከእርሱ ጋራ እሆናለሁ፤ እታዘዘዋለሁም። ቃሌንም በእግዚአብሔርና በኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ጉባዔ ፊት በመሐላ እሰጣለሁ።”

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በዕብራውያን መልእክቱ “ጋብቻ (መጋባት) በሁሉ ዘንድ ቅዱስ (ክቡር)፣ መኝታውም ንጹሕ ይሁን፤ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል (ዕብ 13:4)” በማለት እንደተናገረው ጋብቻ በእግዚአብሔር፣ በተጋቢዎቹ፣ በቤተሰብ፣ በማኅበረሰብ ዘንድ ክብር ያለው መንፈሳዊ ተቋም ነው። እግዚአብሔር አክብሮ መሥርቶታልና ሁሉም ሊያከብረውና ሊጠብቀው ይገባል። አንድም ሳያገቡ በድንግልና መኖር ይበልጣል ብለው የሚያስቡ ነበሩና ጋብቻ ክቡር መሆኑን ሲናገር ነው። “መኝታውም ንጹሕ ይሁን” ማለቱ በባልና ሚስት መካከል የሚደረገው ተራክቦ ንጹሕ ይሁን ማለቱ ነው። ንጹሕ የሚሆነው እንደምን ነው ቢሉ የቅዱስ ጋብቻን ቃል ኪዳን በመጠበቅ (በመተማመን) ነው። ሩካቤ ሥጋ የተፈቀደው በባልና ሚስት መካከል ብቻ ነውና መኝታውን ንጹሕ የምናደርገው ራሳችንን ከዝሙት በመጠበቅ ነው። መኝታውን (በባልና ሚስት መካከል ያለውን የጋብቻ ቃል ኪዳን) በኃጢአት የሚያሳድፉትን ሴሰኞችና አመንዝራዎች ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል በማለት ሐዋርያው አስጠንቅቋል።

ሙሴ ፍችን የፈቀደው በእስራኤላውያን የልብ ጥንካሬ የተነሳ ነበር።

ነገር ግን የሰው ልጆች ልብ እየደነደነ፣ ቅዱስ ጋብቻም እየፈረሰ፣ መፋታትም እየበዛ ሲመጣ ሊቀ ነቢያት ሙሴ በሕገ ኦሪት መፋታትን ፈቀደላቸው። ይህም “ሰው ሴትን ወስዶ ቢያገባ፥ የእፍረት ነገር ስላገኘባት በእርሱ ዘንድ ሞገስ ባታገኝ፥ የፍችዋን ጽሕፈት ጽፎ በእጅዋ ይስጣት፥ ከቤቱም ይስደዳት። ከቤቱም ከወጣች በኋላ ሌላ ወንድ ብታገባ፥ ሁለተኛውም ባል ቢጠላት፥ የፍችዋንም ጽሕፈት ጽፎ በእጅዋ ቢሰጣት፥ ከቤቱም ቢሰድዳት፥ ወይም ሚስት አድርጎ ያገባት ሁለተኛው ባልዋ ቢሞት፥ የሰደዳት የቀድሞ ባልዋ ከረከሰች በኋላ ደግሞ ያገባት ዘንድ አይገባውም፤ ያ በእግዚአብሔር የተጠላ ነው፤ አምላክህም እግዚአብሔር ርስት አድርጎ የሰጠህን ምድር አታርክስ (ዘዳ 24:1-4)” በማለት የተገለጸው ነው። ሙሴ የፈቀደላቸው በልባቸው ጥንካሬ ምክንያት ፍቺ የተስፋፋ ስለነበር ለመቆጣጠር፣ የሴቶችን መብቶች ለማስጠበቅና ከብዝበዛ ለመከላከል እንዲሁም ማኅበረሰባዊ ሥርዓትን ለማስፈነን ነበር እንጂ መፍታትን ሕጋዊ ለማድረግ አልነበረም። ነገር ግን ፈሪሳውያን ይህንን እንደ ሕጋዊ ፈቃድ ወስደውት ነበር።

ክርስቶስ ጋብቻን ወደ ቀደመው ክብሩ መለሰው።

ሕግና ነቢያትን ለመሻር ሳይሆን ለመፈጸም (ፍጹም ለማድረግ) የመጣው ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የቅዱስ ጋብቻን ሕግ ወደ ቀደመው ክብሩና ፍጹምነት መለሰው። ይህም ፈሪሳውያን ሊፈትኑት ወደ እርሱ ቀርበው “ሰው በሆነው ምክንያት ሁሉ ሚስቱን ሊፈታ ተፈቅዶለታልን?” ብለው ለጠየቁት ጥያቄ በሰጠው መልስ ተገልጿል። ጌታችንም “ፈጣሪ በመጀመሪያ ወንድና ሴት አደረጋቸው፥ አለም ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል፥ ከሚስቱም ጋር ይተባበራል፥ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ የሚለውን ቃል አላነበባችሁምን? ስለዚህ አንድ ሥጋ ናቸው እንጂ ወደ ፊት ሁለት አይደሉም። እግዚአብሔር ያጣመረውን እንግዲህ ሰው አይለየው” በማለት የቀደመችውን ፍጽምት የሆነችውን የጋብቻ ሕግ አጽንቶ ነገራቸው (ማቴ 19:3-9 ማር 10:2-12)።

እግዚአብሔር ያጣመረውን እንግዲህ ሰው አይለየው” የሚለው የጌታችን ቃል እጅግ ታላቅ ቃል ነው። ይህም አንደኛ ሁለቱን የትዳር አጋሮች የሚያጣምራቸው እግዚአብሔር መሆኑን በግልፅ ያስተማረበት ቃል ነው። ባልና ሚስትን የሚያጣምራቸው እርሱ እግዚአብሔር መሆኑን የሚያረጋግጥ ቃል ነው። ስለዚህ ነው ቅዱስ ጋብቻ እግዚአብሔር የመሠረተው ተቋም ነው የምንለው። ስለዚህም ባልና ሚስትን የሚያጣምራቸው ሰው የሠራው፣ ምድራዊው የጋብቻ ስምምነት ወረቀት ሳይሆን እግዚአብሔር ራሱ ነው። ሁለተኛው ይህንን እግዚአብሔር ያጣመረውን (ቅዱስ ጋብቻ) ሰው አይለየው (ሊያፋታቸው አይችልም) የሚለው ነው። አዎን እግዚአብሔር የመሠረተውን ተቋም ሰው ሊያፈርሰው አይችልም። እግዚአብሔር የመሠረተው የቅዱስ ጋብቻ ቃል ኪዳን የሚያበቃው በእርሱ ፈቃድ አንዱ በሞት ሲጠራ ነው።

ፈሪሳውያኑም “እንኪያስ ሙሴ የፍችዋን ጽሕፈት ሰጥተው እንዲፈቷት ስለምን አዘዘ?” ብለው የሙሴን ሕግ እንደ መከራከሪያ ቢያቀርቡለት “ሙሴስ ስለልባችሁ ጥንካሬ ሚስቶቻችሁን ትፈቱ ዘንድ ፈቀደላችሁ፤ ከጥንት ግን እንዲህ አልነበረም” በማለት ወደ መጀመሪያዋና በኤደን ገነት ወደ ተመሠረተችው ሕግ መለሳቸው። ከዚያም አማናዊትና ፍጽምት የሆነችውን የቅዱስ ጋብቻ ሕግ “እኔ ግን እላችኋለሁ፥ ያለ ዝሙት ምክንያት ሚስቱን ፈትቶ ሌላዪቱን የሚያገባ ሁሉ ያመነዝራል፥ የተፈታችውንም የሚያገባ ያመነዝራል (ማቴ 19:3-9 ማር 10:2-12)” በማለት አስቀድሞ በተራራው ስብከቱ ያስተማራትን ሕገ ወንጌል ነገራቸው። “ያለ ዝሙት ምክንያት” የሚለው የበስተቀር አንቀጽ (exception clause) ነው። ከዚህ ምክንያት በስተቀር መፍታት አይቻልም ማለት ነው።

ጌታችን በዝሙት ምክንያት ከሆነ መፋታትን የፈቀደው ስለብዙ ምክንያቶች ነው። የመጀመሪያውና ዋናኛው ዝሙት እግዚአብሔር የመሠረተውን የቅዱስ ጋብቻን ቃል ኪዳን የሚያፈርስ ኃጢአት ስለሆነ ነው። ስለዚህም መፋታት ቃል ኪዳኑ መፍረሱን የሚገልጽ ነው። ሁለተኛው ዝሙት ያልፈጸመውን አካል ከኃጢአት ለመጠበቅ ነው። ሦስተኛው ምክንያት ደግሞ ቅዱስ ጋብቻ እግዚአብሔር ከሰው ልጆች ጋር ያለውን ቃል ኪዳን ያመለክታልና ዝሙት ደግሞ ይህንን ቃል ኪዳን መተላለፍ ስለሆነ ዝሙት ምን ያህል አስከፊ ኃጢአት መሆኑን ለማረጋገጥ ነው። በብሉይ ኪዳንም ዝሙት በሞት የሚያስቀጣ ኃጢአት ስለነበር (ዘሌ 20:10 ዘዳ 22:22) በሐዲስ ኪዳንም ቢሆን የሚያስቀጣ መሆኑን ለማረጋገጥ ነው። ይህም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል (ዕብ 13:4)” በማለት ዝሙት የሚፈፅሙትን እንደሚፈረድባቸው እንደገለጸው ነው።

ወንድና ሴት አድርጎ የፈጠራቸው እግዚአብሔር “ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ” ማለቱ ፍጽምት የሆነችው የጋብቻ ሥርዓት አንድ ወንድ ለአንድ ሴት፣ አንድ ሴትም ለአንድ ወንድ ብቻ የምትለው (Monogamy) መሆኗን ሲያረጋግጥልን ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም እንዲሁ ዲያቆን (ለሁሉም ክርስቲያን የሚሠራ ሕግ ነው ) የአንዲት ሴት ባል የሆነ መሆን እንዳለበት አስተምሯል (1ኛ ጢሞ 3:12 ቲቶ 1:6)። እንዲሁም “ነገር ግን ስለ ዝሙት ጠንቅ ለእያንዳንዱ ለራሱ ሚስት ትኑረው ለእያንዳንዲቱ ደግሞ ለራስዋ ባል ይኑራት (1ኛ ቆሮ 7:2)” በማለት አንድ ለአንድ ብቻ መሆኑን አስተምሯል። በብሉይ ኪዳንም “ንጉሥ ልቡ እንዳይስት ሚስቶችን አያብዛ” የሚል ሕግ ነበር (ዘዳ 17:17)። ታዲያ “ስለምን በብሉይ ኪዳን የነበሩ ታላላቅ ነገሥታትና አባቶች (ለምሳሴ ንጉሥ ዳዊት፣ ንጉሥ ሰሎሞን) ብዙ ሚስቶችን ነበራቸው?” ብለን ብንጠይቅ ይህ የሰዎች ባህልና የልብ ጥንካሬ ያመጣው፣ እግዚአብሔርም ያላጸደቀው ነገር ግን በመሀሪነቱ የታገሰው ነው የሚል ምላሽን እናገኛለን።

የቅዱስ ጋብቻ ምሥጢር ታላቅ ነው

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለ ቅዱስ ጋብቻ ባስተማረው ትምህርት “ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ” የሚለው የቅዱስ ጋብቻ ምስጢር በሦስት መንገድ አብራርቶታል። የመጀመሪያው የባህርይ አንድነት ነው። ይህም ሔዋን ከአዳም በመገኘቷ ሁለቱ አንድ አይነት ባህርይ (ባህርያተ ሰብእ) ያላቸው መሆኑ ነው። ሁለተኛው የአካል አንድነት ነው። ይህም ቅድመ ጋብቻ ሁለት አካል የነበሩት በቅዱስ ጋብቻ ምስጢር አንድ አካል ይሆናሉ፣ ይህም አንድነታቸው ከእነርሱ በሚወለዱት ልጆች ይገለጣል። ሦስተኛው የመንፈሳዊ ሕይወት (የመንፈስ) አንድነት ነው። ሁለት የነበሩት በቅዱስ ጋብቻ (በክርስቶስ ሥጋና ደም ማኅተምነት) አንድ ሆነው ቤታቸውን ትንሿ ቤተ ክርስቲያን አድረገው፣ ሕይወታቸው የእግዚአብሔር ፍቅር መገለጫ ሆኖ አንድ መንፈሳዊ ሕይወትን ይኖራሉ። እግዚአብሔርም በቅዱስ ጋብቻ አንድ ለሆኑት ሁሉ ከእነርሱ ጋር ነው።

ቅዱስ ጋብቻ በክርስቶስና በቤተ ክርስቲያን መካከል ያለው ቃል ኪዳን ምሳሌ ነው። ይህም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ቅዱስ ጋብቻንና በቤተ ክርስቲያንና በክርስቶስ መካከል ያለውን ቃል ኪዳን በማነጻጸር እንዳስተማረው ነው። ሐዋርያው “ሚስቶች ሆይ፥ ለጌታ እንደምትገዙ ለባሎቻችሁ ተገዙ፤ ክርስቶስ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ራስ እንደ ሆነ እርሱም አካሉን የሚያድን እንደ ሆነ ባል የሚስት ራስ ነውና። ዳሩ ግን ቤተ ክርስቲያን ለክርስቶስ እንደምትገዛ እንዲሁ ሚስቶች ደግሞ በሁሉ ለባሎቻቸው ይገዙ” በማለት ሚስቶች ለባሎቻቸው በፍቅር እንዲገዙ አስተምሯል።

ባሎችም ሚስቶቻቸውን ምን ያህል መውደድ እንዳለባቸው ሲያስተምር “ባሎች ሆይ፥ ክርስቶስ ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን እንደ ወደዳት ሚስቶቻችሁን ውደዱ፤ በውኃ መታጠብና ከቃሉ ጋር አንጽቶ እንዲቀድሳት ስለ እርስዋ ራሱን አሳልፎ ሰጠ፤ እድፈት ወይም የፊት መጨማደድ ወይም እንዲህ ያለ ነገር ሳይሆንባት ቅድስትና ያለ ነውር ትሆን ዘንድ ክብርት የሆነችን ቤተ ክርስቲያን ለራሱ እንዲያቀርብ ፈለገ። እንዲሁም ባሎች ደግሞ እንደ ገዛ ሥጋቸው አድርገው የገዛ ሚስቶቻቸውን ሊወዱአቸው ይገባቸዋል። የገዛ ሚስቱን የሚወድ ራሱን ይወዳል፤ ማንም የገዛ ሥጋውን የሚጠላ ከቶ የለምና፥ ነገር ግን የአካሉ ብልቶች ስለሆንን፥ ክርስቶስ ደግሞ ለቤተ ክርስቲያን እንዳደረገላት፥ ይመግበዋል ይከባከበውማል” በማለት በንጽጽር አቅርቧል። 

አስቀድሞ እግዚአብሔር የመሠረተው፣ ክርስቶስም ወደ ቀደመ ፍጹምነት የመለሰው የቅዱስ ጋብቻ ምስጢር ምን ያህል ታላቅ እንደሆነ ሲናገርም “ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር ይተባበራል ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ። ይህ ምሥጢር ታላቅ ነው፥ እኔ ግን ይህን ስለ ክርስቶስና ስለ ቤተ ክርስቲያን እላለሁ። ሆኖም ከእናንተ ደግሞ እያንዳንዱ የገዛ ሚስቱን እንዲህ እንደ ራሱ አድርጎ ይውደዳት፥ ሚስቱም ባልዋን ትፍራ (ኤፌ 5:22-33)” በማለት የጋብቻን ጽኑዕነት መስክሯል። አዎን! በምሥጢረ ተክሊል እንደምንማረው የቅዱስ ጋብቻ ምስጢር የተዋሕዶን ምስጢር የሚመስል ታላቅ ምስጢር ነው።

ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስም ስለዚህ ታላቅ ምስጢር “እንዲህ በቀድሞ ዘመን በእግዚአብሔር ተስፋ ያደረጉት ቅዱሳት ሴቶች ደግሞ ለባሎቻቸው ሲገዙ ተሸልመው ነበርና፤ እንዲሁም ሣራ ለአብርሃም። ጌታ ብላ እየጠራችው ታዘዘችለት፤ እናንተም ከሚያስደነግጥ ነገር አንዳች እንኳ ሳትፈሩ መልካም ብታደርጉ ልጆችዋ ናችሁ። እንዲሁም፥ እናንተ ባሎች ሆይ፥ (በጥንት ዘመን በነበረው አካላዊ ጥንካሬ) ደካማ ፍጥረት ስለሆኑ ከሚስቶቻችሁ ጋር በማስተዋል አብራችሁ ኑሩ (በመጨቆን ሳይሆን በፍቅር በመጠበቅ)፤ ጸሎታችሁ እንዳይከለከል (በእኩልነት) አብረው ደግሞ የሕይወትን ጸጋ እንደሚወርሱ አድርጋችሁ አክብሩአቸው (1ኛ ጴጥ 3:5-7)” በማለት ቅዱስ ጋብቻ የትዳር አጋሮች በማስተዋልና በጥበብ በመከባበርም አብረው ኖረው የሕይወትን ጸጋ የሚወርሱባት ምስጢር እንደሆነት አስተምሯል።

እግዚአብሔር መፋታትን ይጠላል

መፋታት የሁለት የትዳር አጋሮች (የባልና የሚስት) መለያየት ብቻ ተደርጎ መወሰድ የለበትም። እግዚአብሔር ምስክር ሆኖ የመሠረተው ቅዱስ ተቋም (የትንሿ ቤተ ክርስቲያን) መፍረስ እንጂ። በቅዱስ ጋብቻ በባለትዳሮች መካከል ለሚከናወነው ቃል ኪዳን ምስክሩ እግዚአብሔር ነው። ይህም በአዳምና በሔዋን መካከል ለነበረው የጋብቻ ቃል ኪዳን ምስክሩ እርሱ እንደነበረው ነው። ስለሆነም ሰው የጋብቻን ቃል ኪዳን ሊጠብቀው ይገባል። እግዚአብሔርም መፋታትን ይጠላል። በነቢዩ ሚልክያስም አድሮ ስለዚህ ሲናገር “ሚስትህ ባልንጀራህና የቃል ኪዳንህ ሚስት ሆና ሳለች እርስዋን አታልለሃታልና እግዚአብሔር በአንተና በልጅነት ሚስትህ መካከል ምስክር ስለሆነ ነው። እግዚአብሔር የሕይወትን መንፈስ አንድ አድርጎ ጠብቆልን የለምን? እርሱም የሚፈልገው ምንድር ነው? ዘር አይደለምን? ስለዚህ መንፈሳችሁን ጠብቁ፥ ማንም የልጅነት ሚስቱን አያታልል። መፋታትን እጠላለሁ (ሚል 2:14-16)” ብሏል። እግዚአብሔር መፋታትን የሚጠላው ሰው እግዚአብሔር የፍቅር ማሠሪያ ሆኖ በመሠረተው በቅዱስ ጋብቻ ቃል ኪዳን መጽናቱን ስለሚወድ ነው። መፈታት ይህን እርሱ ያጣመረውንና የሚወደውን ቅዱስ ጋብቻን ያፈርሳልና ይጠላዋል።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም መፋታትን እግዚአብሔር እንደሚጠላ ሲናገር “ሚስትም ከባልዋ አትለያይ፥ ብትለያይ ግን ሳታገባ ትኑር ወይም ከባልዋ ትታረቅ፥ ባልም ሚስቱን አይተዋት ብዬ የተጋቡትን አዛቸዋለሁ (1ኛ ቆሮ 7:9-14)” በማለት ትዕዛዝን አስተላልፏል። የሃይማኖት ልዩነት ቢኖር (አንዱ ብቻ ወደ ክርስትና ቢመለስ) ወይም ቢፈጠር (አንዱ አካል ወደ ሌላ እምነት ቢሄድ) እንኳን ጋብቻቸው መቀጠል የሚችልበትን መንገድ ሲናገር “ከወንድሞች ወገን ያላመነች ሚስት ያለችው ቢኖር እርስዋም ከእርሱ ጋር ልትቀመጥ ብትስማማ፥ አይተዋት፤ ያላመነ ባል ያላት ሚስትም ብትኖር ይህ ከእርስዋ ጋር ሊቀመጥ ቢስማማ፥ አትተወው። ያላመነ ባል በሚስቱ ተቀድሶአልና፥ ያላመነችም ሚስት በባልዋ ተቀድሳለች፤ አለዚያ ልጆቻችሁ ርኵሳን ናቸው፤ አሁን ግን የተቀደሱ ናቸው። የማያምን ግን ቢለይ ይለይ፤ ወንድም ቢሆን ወይም እኅት እንዲህ በሚመስል ነገር አይገዙም፤ እግዚአብሔር ግን በሰላም ጠርቶናል (1ኛ ቆሮ 7:9-14)” በማለት የማያምነው ወገን በጋብቻው መቀጠል ከፈለገ እንዲቀጥል ፈቅዷል። በአንዲት እምነት እያሉ ጋብቻን ፈፅመው አንደኛው አካል ሃይማኖቱን ቢክድ ጋብቻው ወዲያውኑ እንዲፈርስ አይደረግም። ሃይማኖቱን የካደው ወገን በንስሐ እንዲመለስ መጸለይ ይገባል። በእምነቱ የጸናው ወገን በጋብቻው ውስጥ በፍቅርና በትዕግስት የክርስቶስ ምስክር እንዲሆን ይመከራል።

መፋታትን የሚጠላው እግዚአብሔር በአመንዝራነት የወደቀው አካል ከአመንዝራነት በፍጹም ልቡ ቢመለስ ይቅር ማለት እንደሚገባ በነቢዩ ሆሴዕ በኩል አስተምሯል። ነቢዩ ሆሴዕ ይህንን ሲናገር “እግዚአብሔርም የእስራኤል ልጆች ወደ ሌሎች አማልክት ቢመለሱና የዘቢብ ጥፍጥፍን ቢወድዱ እንኳ፥ እግዚአብሔር እንደሚወድዳቸው አንተም ውሽማዋን የምትወድደውን አመንዝራይትን ሴት ውደድ አለኝ። እኔም በአሥራ አምስት ብርና በአንድ ቆሮስ መስፈሪያ ተኩል ገብስ ገዛኋት። ከእኔ ጋር ብዙ ወራት ተቀመጪ፥ አታመንዝሪም፥ ለሌላ ሰውም አትሁኚ፤ እኔም እንዲሁ እሆንልሻለሁ አልኋት (ሆሴዕ 3:1-3)” ብሏል። በአመንዝራነት የወደቀው አካል በንስሐ መመለሱ ለመንፈሳዊ ሕይወቱ አስፈላጊ ቢሆንም በራሱ ጋብቻውን ወደ ቀደመው ቦታው አይመልሰውም። እርቅ ፈፅሞ በጋብቻው መቀጠል ወይም መፋታት በዝሙት ያልወደቀው አካል መብት ነው። ቤተ ክርስቲያን በአመንዝራነት ምክንያት መፋታትን ትፈቅዳለች እንጂ እንዲፋቱ ወይም አብረው እንዲቀጥሉ አታስገድድም።

የቅዱስ ጋብቻ ቃል ኪዳን የሚጸናው እስከ መቼ ነው?

በእግዚአብሔርና በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ፈት የሚፈጸም የቅዱስ ጋብቻ ቃል ኪዳን እስከሞት ድረስ የጸና ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ስለዚህ ሲናገር “ወንድሞች ሆይ፥ ሕግን ለሚያውቁ እናገራለሁና ሰው ባለበት ዘመን ሁሉ ሕግ እንዲገዛው አታውቁምን? ያገባች ሴት ባልዋ በሕይወት ሲኖር ከእርሱ ጋር በሕግ ታስራለችና፤ ባልዋ ቢሞት ግን ስለ ባል ከሆነው ሕግ ተፈትታለች። ስለዚህ ባልዋ በሕይወት ሳለ ለሌላ ወንድ ብትሆን አመንዝራ ትባላለች፤ ባልዋ ቢሞት ግን ከሕጉ አርነት ወጥታለችና ለሌላ ወንድ ብትሆን አመንዝራ አይደለችም (ሮሜ 7:1-3)” ብሏል። እንዲሁም “ሴት ባልዋ በሕይወት ሳለ የታሠረች ናት፤ ባልዋ ቢሞት ግን በጌታ ይሁን እንጂ የወደደችውን ልታገባ ነጻነት አላት (1ኛ ቆሮ 7:39)” በማለት የቅዱስ ጋብቻ ቃል ኪዳን እስከሞት ድረስ እንደሆነ አስተምሯል። ጌታችንም በትምህርቱ “በትንሣኤስ እንደ እግዚአብሔር መላእክት በሰማይ ይሆናሉ እንጂ አያገቡም አይጋቡምም (ማቴ 22:30)” በማለት የቅዱስ ጋብቻ ቃል ኪዳን እስከሞት ድረስ መሆኑን አስተምሯል።

ለጋብቻ መፍረስ እንደ ምክንያት የሚጠቀሱ ነገሮች ምንድን ናቸው?

የመንፈሳዊ ሕይወት ዝለትና ፈተና (Spiritual factors): ከመንፈሳዊ አስተምህሮ አንጻር ለጋብቻ መፍረስ ዋነኛ ምክንያት ተደርጎ የሚወሰደው በመንፈሳዊ ሕይወት ሳይበስሉ ጋብቻን መመሥረት፣ በጋብቻ ውስጥ የሚገጥም የመንፈሳዊ ሕይወት ድክመትና ፈተናን መቋቋም አለመቻል ናቸው። መንፈሳዊነት የሚፈተንበት አንዱ ዘርፍ የትዳር ሕይወት መሆኑን ልናውቅ ይገባናል። በተለይም በጋብቻ ውስጥ ከቤተ እግዚአብሔር መራቅና ዓለማዊነትን መለማመድ፣ በጾም በጸሎትና በምክረ ካህን አለመጽናትና ቅዱስ ቁርባንን አለመቀበል ዋነኛ ምክንያቶች ናቸው። ሰው ከእግዚአብሔር እየራቀ በሄደ ቁጥር በቅዱስ ጋብቻ የመጽናቱ ነገርም እንዲሁ ጥያቄ ውስጥ እየገባ ይመጣል። የትዳር አጋሮችም የሚተማመኑት ተፈራርተው ሳይሆን እግዚአብሔርን ፈርተው ነውና በመንፈሳዊ ሕይወት መዛል እግዚአብሔርን ወደ አለመፍራትና የስነምግባር ብልሹነት ያደርሳል። ይህም ቅዱስ ጋብቻን ሊያፈርስ ይችላል።

ስሁት አስተምህሮዎች: ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ሚስት በገዛ ሥጋዋ ላይ ሥልጣን የላትም፥ ሥልጣን ለባልዋ ነው እንጂ፤ እንዲሁም ደግሞ ባል በገዛ ሥጋው ላይ ሥልጣን የለውም፥ ሥልጣን ለሚስቱ ነው እንጂ። ለጸሎት ትተጉ ዘንድ ተስማምታችሁ ለጊዜው ካልሆነ በቀር፥ እርስ በርሳችሁ አትከላከሉ፤ ራሳችሁን ስለ አለመግዛት ሰይጣን እንዳይፈታተናችሁ ደግሞ አብራችሁ ሁኑ (1ኛ ቆሮ 7:5)” በማለት በትዳር ውስጥ ስለሚኖረው ግንኙነት አስተምሯል። የከተማ ‘መነኮሳትና ባህታውያን’ በማይመለከታቸው የሰው ትዳር ገብተው ይህንን የሐዋርያውን ቃል ለጥጦና አጣሞ በመተርጎም ምክንያት እየፈጠሩ ባልና ሚስት ያለፈቃዳቸው ለረጅም ጊዜ ምንጣፍ እንዲለዩ በመምከር በትዳር ውስጥ መቃቃርና መራራቅ እንዲፈጠር የሚያደርጉ የስህተት ትምህርት የሚያስተምሩ አሉ። እነዚህም ትዳር እንዲፈተንና እንዲፈርስ ሊያደርጉ ስለሚችሉ ምዕመናን የንስሐ አባት ሲይዙ ጥንቃቄ ሊያደርጉ ይገባል።

ከፀባይና ግንኙነት ጋር የተያያዙ ምክንያቶች (Behavioral and relationship factors): ከትዳር አጋሮቹ ፀባይና ግንኙነት አንጻር ሲታይ ደግሞ አንዱ በአንዱ ላይ ጥቃት መፈጸም፣ የሀሳብ ልዩነቶችን ተወያይቶ ከመፍታት ይልቅ ብዙ ጊዜ መጨቃጨቅና መጋጨት፣ አለመከባበር አለመደማመጥና አለመረዳዳት፣ አለመተማመን የሚፈጥሩ ግንኙነቶችን ከሌሎት ሰዎች ጋር ማድረግ፣ ከትዳር የምንጠብቀው ነገር (expectation) መለዋወጥ እና የመሳሰሉት እንደ ምክንያት ሊጠቀሱ ይችላሉ። ከትዳር በፊት (በእጮኝነት ዘመን) የነበረ ፀባይ መቀየርም እንዲሁ ትዳርን ይፈትናል።

ማኅበራዊ ምክንያቶች (Social and demographic factors): ከማኅበራዊ ሕይወት አንጻር ሲታይ ደግሞ የጓደኛ፣ የቤተሰብ፣ የማኅበረሰብ አሉታዊ ግፊት፣ የርዕዮተ ዓለም ልዩነትን አቻችሎ መኖር አለመቻል፣ ሳይበስሉ ማግባት፣ የዕድሜ መራራቅ፣ የወላጆች ትዳር መፍረስ፣ ዝቅተኛ የትምህርት ደረጃና የመሳሰሉት ይገኙበታል። ከእነዚህም በተለይ የቤተሰብ ጣልቃ ገብነትና ክፉ የጓደኛ ምክር ዋናዎቹ ናቸው። ቅዱስ መጽሐፍ ሰው እናትና አባቱን ይተዋል፣ ከሚስቱም ጋር ይተባበራል፣ ሁለቱም አንድ ሥጋ ናቸው እንዳለው የትዳር አጋሮች አንድ ሆነው ትንሿን ቤተክርስቲያን ሊኖሯት ይገባል እንጂ ሌላ አካል በመካከላቸው ጣልቃ ማስገባት የለባቸውም።

ኢኮኖሚያዊ ምክንያቶች (Economic factors): ከኢኮኖሚ አንጻር ካየነው ደግሞ በቂ ሥራ (መተዳደሪያ) ሳይኖር ወደ ትዳር መግባት ወይም አብሮ በቂ መተዳደሪያ መፍጠር አለመቻል፣ በጋብቻ ሕይወት ውስጥ የሚያጋጥም ድህነት (ለምሳሌ ከሥራ መፈናቀል፣ ሥራ ማጣት)፣ ገንዘብ ከማጣት ጋር የተያያዘ ጭንቀት፣ ሥራ ፍለጋ ወደ ሌላ ቦታ (ሀገር) የሚደረግ ስደትና የመሳሰሉት ትዳርን ሊፈትኑና ሊያፈርሱት ይችላሉ። ከልክ ያለፈ የሠርግ ወጪ የሚያመጣው ኢኮኖሚያዊ ተጽዕኖም ከዚህ ይካተታል።

ከሕግና ባህል ጋር የተያያዙ ምክንያቶች (Legal and cultural factors): ከሕግና ከባህል አንጻር ለሚመለከት ሰው ደግሞ ሕጋዊ ጋብቻን ሳይፈፅሙ አብሮ መኖር፣ ሕጋዊ ፍች መፈፀም ቀላል መሆን (ለምሳሌ አንዱ ወገን ከጠየቀ እንዲፋቱ ማድረግ)፣ እኩልነትን አለመቀበል ወይም በውሳኔ አሰጣጥ ሂደት ውስጥ ለሴቶች ዝቅተኛ ቦታ መስጠት፣ በትዳር ውስጥ ያሉ ሴቶች ተምረው ራሳቸውን ከማሳደግ ይልቅ የልጅ ተንከባካቢ የቤት እመቤት ብቻ ሆነው እንዲኖሩ ማድረግና የመሳሰሉት ይገኙበታል።

ከጤና ጋር የተያያዙ ምክንያቶች (Health-related factors): ከጤና ጋር የተያያዙ ምክንያቶች የሚባሉት ደግሞ ጽኑ ሕመም (chronic disease)፣ የአእምሮ ሕመም፣ መውለድ አለመቻልና ሌሎች ከስነተዋልዶ ጋር የተያያዙ በሽታዎችና ችግሮች፣ ሱሰኝነት (ስካርን ጨምሮ) እና የመሳሰሉትን ያካትታል። በተለይም በተፈለገው ጊዜ ልጅ መውለድ አለመቻል ጋብቻን ይፈትናል። ይህ ችግር ቅዱስ ጋብቻን የመሠረተውን እግዚአብሔርን መፍትሔ በመጠየቅ እንጂ እርሱ የመሠረተውን ጋብቻ በማፍረስ ሊፈታ አይገባም። አንደኛው አካል የጤና ችግር ሲገጥመውም አብሮ ሆኖ መርዳት እንጂ መፍታት አይገባም። የጋብቻ አንዱ ዓላማ እንዲህ ባለው ክፉ ጊዜ መረዳዳት ነውና።

ምዕመናን በትዳራቸው ፈተና ሲገጥማቸው ምን ያድርጉ? ማንንስ ያማክሩ?

በትዳር ውስጥ ዋነኛ አካላት ባል፣ ሚስትና የፍቅራቸው ማሠሪያ የሆነው እግዚአብሔር ናቸው። ሌሎች አካላት ምክር ከመስጠት ባለፈ ውሳኔ ሰጭነት ላይ ድርሻ ሊኖራቸው አይገባም። ስለዚህም በትዳር ውስጥ ፈተና ሲያጋጥም የመጀመሪያው መፍትሔ በጸሎት እግዚአብሔርን መጠየቅ ሊሆን ይገባል። እግዚአብሔር እርሱ የመሠረተውን ተቋም ለፈተና አሳልፎ አይሰጠውም። ከዚያም ሁለቱ የትዳር አጋሮች እግዚአብሔርን በመፍራት ሆነው በመከባበር ተረጋግተው በመወያየት ለችግሮቻቸው መፍትሔን ይፈልጉ ዘንድ ይገባል። ለመፍትሔው ግብአት የሚሆን መንፈሳዊ ምክር ሲፈልጉ ደግሞ ከመምህር ንስሐ መንፈሳዊ ምክርንና በጸሎት እንዲራዱ መጠየቅ ይገባል። የስነልቦና ምክር ካስፈለጋቸው ደግሞ ሕጋዊ ፍቃድ ካለው የስነልቦና ባለሙያ ቀርበው አገልግሎት ማግኘት ይችላሉ።

ከዚህ ላይ ሊስተዋል የሚገባው ልዩነት ከካህናት አባቶች የሚገኘው መንፈሳዊ ምክር (Pastoral Counseling)፣ ከባለሙያዎች የሚገኘው ደግሞ ስነልቦናዊ ምክር (Marriage counseling) መሆኑ ነው። ከዚህ በተጨማሪ መልካም ትዳር ካላቸው መንፈሳዊያን ወንድሞችና እኅቶች ልምድ መቅሰምም ይጠቅማል። ከዚህ ውጪ ስለትዳር መንፈሳዊና ስነልቦናዊ ጉዳዮች በቂ ዕውቀት፣ልምድ ወይም ክህሎት ከሌላቸው ‘የትዳር አማካሪ ነን’ ባዮች ወይም ስለትዳር እናስተምራለን ከሚሉ ወጣት ሰባኪያን፣ አጥማቂያን፣ የከተማ መነኮሳትና ባህታዊያን ራስን መጠበቅ ይገባል። በባለሙያ ያልተረጋገጠ መረጃንም ከበይነ መረብና ከማኅበራዊ ሚዲያ ወስዶ ትዳር ላይ መሞከር አደጋ አለው።

ጋብቻ እንዳይፈርስ አስቀድሞ በጽኑ መሠረት ላይ ማነጽ፣ ከታነጸም በኋላ መጠበቅ ይገባል።

ዐውደ ምሕረት ላይ ቆሞ “ትዳርን መፍታት አይገባም፣ ጋብቻን ማፍረስ ኃጢአት ነው” እያሉ መደጋገም ብቻውን ጋብቻን ከመፍረስ አያድነውም። በተጨባጭ ትዳር እንዲቀጥል የሚያስችል መንፈሳዊና ማኅበራዊ ሥራ መሥራት እንጂ። ቅዱስ ጋብቻን ለመመሥረት ቅድመ ጋብቻ፣ እስከ መጨረሻው ድረስ ለማጽናት ደግሞ በጋብቻ ሕይወት ላሉ ቀጣይነት ያለው መንፈሳዊ ትምህርትና ምክር መስጠት ይገባል። ይህም ላልተገባ ፍቺ ምክንያት ሊሆኑ የሚችሉ ችግሮችን አስቀድሞ ለመለየትና መፍትሔም ለማበጀት፣ ባለትዳሮችንም በመንፈሳዊ ሕይወት ለማበርታት ይጠቅማል። ጋብቻን ለሚመሠርቱ ወጣቶች የጋብቻን ክቡርነት፣ እስከሞት ድረስ የሚቀጥል ቃል ኪዳን መሆኑን፣ እግዚአብሔርን መፋታትን እንደሚጠላ በበቂ ሁኔታ ማስተማር ይገባል።

‘ቅዱስ ጋብቻን ማፍረስ አይገባም፣ መፋታት አይገባም’ ማለት ከታመመ ትዳር ጋር እየተሰቃያችሁ ዝም ብላችሁ አብራችሁ ኑሩ ማለት አይደለም። መፋታት መፍትሔ ስለማይሆን የታመመውን ትዳር በመንፈሳዊ ሕክምና ወደ ቀደመው ጤንነቱ መመለስ ይገባል ማለት እንጂ። የታመመ ሰው መታከም እንደሚገባው ሁሉ የታመመ ትዳርም ሊታከም ይገባዋል። ለታመመ ትዳር መፋታት መፍትሔ አይሆንም የምንለው በሽታውን ትቶ ተቋሙን ማፍረስ መፍትሔ ስለማይሆን ነው። ትዳር ሲታመም ማፍረስ ማለት ሰው ሲታመም በሽታውን ትቶ ታማሚውን እንደመግደል ወይም ቤት በነፍሳት ሲወረር ነፍሳቱን ማጥፋትን ትቶ ቤቱን እንደማፍረስ ያለ ነው።

ትዳራቸው የታመመባቸውም ሲያጋጥሙ የሚታከምበትንና የሚድንበትን መፍትሔዎች ማመላከት ይገባል። ችግሩን ሊፈቱት የሚገባቸው ግን ባልና ሚስት ናቸው። “የችግራችሁ መፍትሔ ይህ ነው” የሚል አካሄድ (Prescriptive approach) ትዳርን ያፈርሳል እንጂ አያክምም። አንዳንድ በዘር፣ በብሔርና በፖለቲካ አመለካከት መነሻነት ትዳራቸውን የሚያፈርሱትንም ቅዱስ ጋብቻ ከእነዚህ ምድራዊያንና ሰው ሠራሽ ነገሮች ሁሉ በላይ መሆኑን ማስተማር ይገባል። በእነዚህ መነሻነትም እግዚአብሔር የመሠረተውን የሌሎች ትዳር እንዲፈርስ የሚያበረታቱ (አገልጋዮችም ቢሆኑ) ከጥፋታቸው እንዲመለሱ ማስተማር ይገባል። ክርስቲያኖችም ለትዳር ተገቢውን ዋጋ በመስጠት ጋብቻን እውነተኛ ላልሆኑ ዓላማዎች (non-genuine objectives) ከማዋል ሊታቀቡ ይገባል እንላለን።