“ቤተክርስቲያን” የሚለው የግዕዝ ቃል ሲሆን “ቤት-” እና “ክርስቲያን” ከሚሉት ቃላት የተቀመረ ነው፡፡ ይህም በግሪክ አቅሌስያ (Ecclesia) ከሚለው ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ቤት የሚለው ቃል ወገን፤ ነገድ፤ ዘር፤ ትውልድ፤ ጉባኤ፤ ማኅበር ማለት እንደሆነ አለቃ ኪዳነወልድ ክፍሌ በመዝገበ ቃላት መጽሐፋቸው ላይ ጠቅሰዋል፡፡(ኪ.ወ.ክ ገጽ 268) የያዕቆብ ወገን ቤተ ያዕቆብ (ቤተ እስራኤል)፤የዳዊት ወገን ቤተ ዳዊት እንዲባል በመንፈሳዊና በምሥጥራዊ ልደት ከክርስቶስ የተወለዱ ምእመናንም ቤተ ክርስቲያን ይባላሉ፤ ቤተ ክርስቶስ (የክርስቶስ ወገን) እንደ ማለት ነው፡፡ ዳሩ ግን በዘመናችን ስምና ግብር ለየቅል ሆነው በተቃራኒ ያሉት ወገኖች ሳይቀሩ ስሙን መጠሪያ አድርገው አናስተውላለን፤ ዘመናችን አማናዊቱ ቤተ ክርስቲያን ስምዋን ወስደው በሚጠሩ አስመሳዮች የተወረረችበት ወቅት በመሆኑ እውነተኛዋን ለይቶ ማወቅ ግድ ይላል፡፡ ብዙ መምህራን ቤተክርስቲያን የሚለው ቃል ሦስት ትርጉም አለው ብለው ያስተምራሉ፡፡ ትርጉሙን በጥልቀት ለተመለከተው ግን አራት ነገሮችን ይገልፃል፡፡ ይቀጥላል፡፡