መግቢያ
እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን እንደ እንግዳ ደራሽ በድንገት የተቋቋመች አይደለችም፡፡ ይህች አውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን እንደ ወሃ ደራሽ በድንገት የደረሰችም አይደችም፡፡ አማናዊቷ ቤተክርስቲያን እንደ ወፍ ዘራሽ በድንገት የተመሠረተችም አይደለችም፡፡ ዓለም ከተፈጠረበት ዘመን ከተቆጠረበት ጊዜ ጀምሮ በተለያዩ ምሳሌዎች እተመሰለች (በምሳሌዎች እየተገለጸች) በጥላ ውስጥ የነበረችና የኖረች ናት እንጂ፡፡
ሌሎች ራሳቸውን ቤተክርስቲያን የሚሉ ድርጅቶች ግን እንደዚህ አይደሉም፡፡ መሥራቾቻቸው ሰዎች ሰለሆኑ በድንገት ወይም በጥናት በሰው ሀሳብ የተመሠረቱና የሚመሠረቱ ናቸው፡፡ ያ የተመሠረቱበት ሀሳብና ዓላማ ሲያረጅ መታደስ ያስፈልጋቸዋል፤ አለበለዚያ ይፈርሳሉ፡፡ እንደ ምድራዊ ተቋም በሰው አስተሳሰብ የሚመሩ ናቸውና፡፡ ከእነዚህ ድርጅቶች ውስጥ አንዳንዶች ህገ ደንቡ ወይም አሠራሩ ወይም አመራሩ አልመች ሲላቸው ተገንጥለው ሌላ የራሳቸው ‘ቤተክርስቲያን’ ይመሠርታሉ፡፡ እንደዚያ እንደዚያ እያለ ዛሬ በሺዎች የሚቆጠሩ የእምነት ድርጅቶች ለመመሥረት በቅተዋል፡፡ አማናዊት ቤተክርስቲያን ግን እንደዚህ አይደለችም፡፡ ዘላለማዊና አንዱ አምላክ የመሠረታት ዘላለማዊትና አንዲት ናት እንጂ፡፡
የክርስቶስ ሐዋርያት ክርስቲያን ተብለው (ሐዋ 11፡26)፣ እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያንም በክርስቶስ ደም ተዋጅታና (ሐዋ 23፡20) አማናዊት ሆና እስክትገለጥ ድረስ በሕገ ልቡናና በሕገ ኦሪት ዘመን ብዙ ምሳሌዎች ነበሯት፡፡ ምሳሌ ያው ምሳሌ ነው፡፡ እውነተኛውን ነገር ለማስረዳት እንጂ ለመተካት የሚቀርብ አይደለም፡፡ እነዚህ ምሳሌዎች ለእውነኛይቱ የክርስቶስ ቤተከርስቲያን እንጂ ለሌሎች ራሳቸውን ቤተክርስቲያን ብለው ለሰየሙት ድርጅቶች የሚስማሙ አይደሉም፡፡ ለመረዳት ያህል በሕገ ልቡናና በዘመነ ኦሪት ሥርዓተ አምልኮ ይፈጽምባቸው ከነበሩት የቤተክርስቲያን ምሳሌዎች ከብዙ በጥቂቱ የሚከተሉት ይገኙበታል፡፡
ይቀጥላል