ቅዱስ መስቀል: እግዚአብሔር ያገለገለባት መቅደስ ወዮ እንደምን ያለች ናት?!

መግቢያ

የተመረጠ ምስጋና መፍሰሻ የሆነች ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ዕለት ዕለት በምታቀርበው ምስጋና ከሥሉስ ቅዱስ (በፍጹም አንድነትና በልዩ ሦስትነት ከሚመሰገን እግዚአብሔር) ቀጥሎ ለሁለት ፍጥረታት በልዩ አንክሮ የጸጋ ምስጋናን ታቀርባለች። እነዚህም ሥጋን የተዋሐደ የመለኮት ክብር መገለጫ፣ የኢየሱስ ክርስቶስ የማዳን ስራ ምክንያትና ምልክት የሆኑት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ቅዱስ መስቀል ናቸው። ለእያንዳንዱ የሚገባውን ምስጋና ቆጥረው ለይተው ያስተማሩን ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት ስለ ቅዱስ መስቀልም “ስብሐት ለመስቀለ ክርስቶስ ዕፀ መድኃኒት ኃይልነ ወጸወንነ/ ኃይላችን፣ መመኪያችን (መጠጊያችን)፣ የመድኃኒት መገኛ ለሆነ ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ መስቀልም ምስጋና ይገባል።” የሚለውን ምስጋና አስተምረውናል። በዚህች ጦማር ቅዱስ መስቀልን የምናከብርበትንና የምናመሰግንበትን ምክንያት እናብራራለን፣ ተያይዘው የሚነሱ የመናፍቃን ማምታቻዎችን እንሞግታለን፣  በየዓመቱ መስከረም 17 የሚከበረውን የመስቀል በዓል ሃይማኖታዊና ታሪካዊ መሠረት እንዳስሳለን፣ የመስቀል በዓል ለምን የአዲስ ዘመን ምልክት ተደርጎ እንደሚከበርም እናብራራለን።

ለእሉ ክልኤቱ ፍጡራን ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ እስመ ተዐረዩ በክብሮሙ!

ከቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የጸሎት መጻሕፍት አንዱ የሆነው “መስተብቁዕ ዘመስቀል” እመቤታችን ድንግል ማርያምና ቅዱስ መስቀል በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የማዳን ሥራ ያላቸውን ሱታፌ አድንቆ፣ የጸጋ ምስጋናቸውን አመክንዮ ሲያስረዳ “ለእሉ ክልኤቱ ፍጡራን ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ እስመ ተዐረዩ በክብሮሙ/ለእነዚህ ሁለት ፍጥረታት (ለእመቤታችን ማርያምና ለቅዱስ መስቀል)  የፈጣሪ ምስጋና ይገባቸዋል፣ በክብር ተካክለዋልና (ተመሳስለዋልና) ይላል።” ቅዱሳት መጻሕፍትን በሚገባ ተረድቶ ለተመስጦ፣ ለጸሎት ከመጠቀም ይልቅ ትርጓሜን የፊደል ጨዋታ የሚያስመስሉ ሰዎች ይህን ምስጋና ባለማወቅ ይተቹታል። ሰይጣን ለአዳም የተሰጠ ትዕዛዝን አዛኝ መስሎ በማጣጣል ወደሞት እንደመራው እነዚህም ሰዎች መግቢያ ቀዳዳ በመሰላቸው መንገድ ሁሉ እየገቡ ርትዕት አስተምህሯችንን፣ የቀናች የቅዱሳን አባቶቻችንን ሃይማኖት በአላዋቂነት በመተቸት የሚደነግጡላቸውን የዋሀን ምዕመናንና ያወቁ የመሰላቸው ፊደላውያን ካህናትና መምህራንን ያስታሉ።

ይሁንና ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያናችን የሥላሴን ክብር ለፍጡራን አትሰጥም። የእመቤታችንና የቅዱስ መስቀልም ክብር ተለይቶ የታወቀ ነው። “ለእሉ ክልኤቱ ፍጡራን” የሚለው የመስተብቁዕ ክፍልም ማን ፍጡር፣ ማን ፈጣሪ እንደሆነ የሚያሳይ ነው፣ የሚያከራክርም አይደለም። ስህተት ፈላጊዎቹ ግን በግልፅ ከሚታወቅ አስተምህሮ ይልቅ እንደ ሰይጣን “የተደበቀ  ዓላማ” ያለው የሚመስላቸውን “እስመ ተዐረዩ በክብሮሙ” የሚለውን በመጥቀስ የጸጋ ግምጃ ቤት የሆነች የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ይተቻሉ። ይህም በሕግ ቋንቋ እግረ መንገድ የተጠቀሰን አገላለፅ (obiter) እንደዋና ሀሳብ ወስዶ፣ ያንንም አጣሞ የሚተረጉም አላዋቂ ነገረፈጅ መሆናቸውን ያሳያል። ፍጡራን የፈጣሪን ምስጋና በጸጋ ወሰዱ ማለት “ፈጣሪ ሆኑ” ማለት ነው ብሎ ማሰብ እንዴት ያለ አላዋቂነት ነው?!

በቀላል ምሣሌ ለማስረዳት ቅዱሳን መላእክት እግዚአብሔርን የሚያመሰግኑበት ልዩ ምስጋና “ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ እግዚአብሔር” የሚለው መሆኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ይነግሩናል። (ኢሳ. 6:3፣ ራዕይ 4:8) በጥሬ ንባብ ካየነው መጽሐፍ ቅዱስ ከእግዚአብሔር በቀር ቅዱስ የለም ይለናል። (መጽሐፈ ሳሙኤል ቀዳማዊ 2:2) በአንፃሩ ደግሞ ቅዱሳን ሰዎችን፣ መላእክትን፣ ከተሞችና ተራሮችን ሳይቀር “ቅዱስ” ብሎ ይጠራቸዋል? (1ኛ ጴጥ. 1:16፣ 2ኛ ጴጥ. 1:18፣ ኢሳ. 62:1-3፣ ራዕይ 21:2) ይህ ማለት መጽሐፍ ቅዱስ የፈጣሪን ምስጋና ለፍጡራን ሰጠ ያስብላል? አያስብልም። ይቅርና የእግዚአብሔርና የፍጡራን ቅድስና፣ በፍጡራን መካከል ያለ የቅድስና ደረጃ እንኳ በቃላት ቅፅል ብቻ የሚለይ፣ የሚታወቅ አይደለም።

እግዚአብሔርን ቅዱስ ስንል የቅድስና ምንጭ፣ በባሕርይው ምንም ምን ሕፀፅ የሌለበት መሆኑን እንናገራለን። እመቤታችንን ቅድስት ስንል ለተዋሕዶ መመረጧን፣ ከመርገመ ሥጋ ከመርገመ ነፍስ መለየቷን/መጠበቋን እንናገራለን። ቅዱስ መስቀልን ስናስብ የመዳናችን ዓርማና ምልክት መሆኑን እንመሰክራለን። ለሁሉም “ቅዱስ” የሚለውን መግለጫ መጠቀማችን ለፊደላውያን አንድ ቢመስላቸውም በመንፈስ ለሚኖሩ፣ በአግባቡ ለሚረዱ ግን ትርጉሙ የተገለጠ ነው። መስተብቁዕ ዘመስቀል ከላይ በተገለፀው ዐውድ እመቤታችንና መስቀልን “በክብር የተካከሉ” ማለቱም የመለኮት ዙፋን በመሆን የተካከለ (የተመሳሰለ) ግብር አምላካዊ ስለተገለጠባቸው እንጂ የፍጡራን ምስጋና ከፈጣሪም ሆነ እያንዳንዳቸው በንፅፅር የሚምታቱ፣ የሚደበላለቁ ናቸው ማለት አይደለም።

"ኦ መቅደስ ዘኮነ ባቲ እግዚአብሔር ካህነ/ እግዚአብሔር ያገለገለባት መቅደስ ወዮ እንደምን ያለች ናት?!" 

የኪስኪስ ኤጲስ ቆጶስ ሊቁ አባታችን ቅዱስ ኤራቅሊስ እመቤታችንና ቅዱስ መስቀል ዕሩያን (የተካከሉ) የሆኑበትን የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የማዳን ሥራ በአንክሮ በገለጠበት የሃይማኖተ አበው ንባብ ያመሰጠረው ምሥጢር፣ የመሰከረው ሃይማኖት የእኛም ሃይማኖት ነው። “ኦ ከርሥ ዘተጽሕፈ ውስቴታ መጽሐፈ ግእዛን እምግብርናት ለኩሉ ሰብእ!/ለሰው ሁሉ ከመገዛት የነፃነት መጽሐፍ የተጻፈበት ማሕፀን ወዮ እንደምን ያለች ናት?” ብሎ  ማሕፀነ ድንግል ማርያምን እንዳመሰገነ “ኦ መቅደስ ዘኮነ ባቲ እግዚአብሔር ካህነ/ እግዚአብሔር ያገለገለባት መቅደስ ወዮ እንደምን ያለች ናት?!” በማለት ደግሞ የቅዱስ መስቀልን ክብር፣ የእመቤታችንን ልዕልና አስተምሮናል። (ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ኤራቅሊስ ምዕራፍ 48:15-17)

የቅዱስ መስቀል የክብሩ መሰረት እግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ያገለገለበት መቅደስ መሆኑ ነው። ካህን (አገልጋይ) መባል ለፍጡር የሚስማማ ነው። የሰማይና የምድር ጌታ እግዚአብሔር ካህን (አገልጋይ) መሆኑ (መባሉ) ግን ይደንቃል። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጸሎተ ሐሙስ በአገልጋይ ሥርዓት ዝቅ ብሎ የደቀ መዛሙርቱን እግር ካጠበ በኋላ “ያደረግሁላችሁን ታስተውላላችሁን (ዐወቃችሁን)?” በማለት በዮሐ. 13:12 የተናገረው ቅዱስ ቃል በዕለተ ዓርብ የፈጸመውን ዘላለማዊ አገልግሎት በአንክሮ ለመረዳት ይጠቅመናል። መምህረ ትህትና፣ ሰው የሆነ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስን ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ልዪ ሊቀ ካህናት ብላ የምታመሰግነው አገልጋይነቱ ከኅሊናት ኹሉ በላይ ስለሆነ ነው።

በቸርነቱ ልዩ ሊቀ ካህናት ሆኖ ራሱን የተወደደ መሥዋእት አድርጎ ያቀረበ፣ መሥዋእቱን እንደ እግዚአብሔርነቱ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የተቀበለ ኢየሱስ ክርስቶስ ያገለገለበት የቀራንዮ መቅደስ እንደምን የከበረ ነው?! ፍጡራን የሆኑ የብሉይ ኪዳን ሊቃነ ካህናት ዘላለማዊ ሕይወት የማያስገኝ፣ የሚያልፍ መሥዋእት ያቀረቡባቸው መቅደሶች ክቡራን ከተባሉ ራሱ እግዚአብሔር ያገለገለበት፣ የከበረ ሥጋውን፣ የተቀደሰ ደሙን መሥዋእት አድርጎ እስከ ዓለም ፍፃሜ ለሚመጡ ካህናትና ምእመናን ባርኮ የሰጠበት፣ መዳናችን የተፈጸመበት ቅዱስ መስቀል ክብሩ፣ ገናናነቱ እንዴት ሊገለፅ ይችላል? ስለሆነም ዘወትር በመልክአ ኢየሱስ ጸሎታችን “ኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህናቲነ አስተጋብአነ ኀበ ትረፍቅ መካነ እስመ ዝርዋን አግብርቲከ ንህነ።” እያልን በፈቃዱ አገልጋይ ለተባለ ጌታ በፈቃዳችን እንገዛለታለን፣ ያገለገለበትን መቅደስ: ቅዱስ መስቀሉንም በልዩ ክብር እናከብረዋለን።

ሰይጣን ባጣመመው የመናፍቅነት ልቦና ይህን የምታነብ ዓይን ሆይ አንድ ጥያቄ እንጠይቅህ: “ከሙሴና ከሙሴ ፈጣሪ ከክርስቶስ ማን ይልቃል? ሙሴ ከእግዚአብሔር ጋር የተነጋገረባት ድንኳን ከተገለጸው ረድኤተ እግዚአብሔር የተነሳ ንዑድ ክቡር ተብላ ጫማውን ያላወለቀ የማይገባባት ከሆነች ራሱ እግዚአብሔር ያገለገለባት፣ መቅደስ (ቅዱስ መስቀልማ) ክብሯ ምን ያህል ይሆን? ምዕመናን ከእግዚአብሔር ጋር እንዲገናኙባት በሙሴ እጅ የተሰጠችውን ታቦት ክብሯን ንቀው ያቃለሉት ዳታንና አቤሮን ምድር ተከፍታ ከዋጠቻቸው ራሱ እግዚአብሔር ያገለገለበትን (ሥጋውን ደሙን ያዘጋጀበትን) ቅዱስ መስቀል ክብር በሰይጣን ማታለል የሚያቃልል ሰውማ በቸርነቱ አገልጋይ በተባለ ጌታ ፊት ምን ያህል ጎስቋላ ይሆን?!” ስለዚህ ኅሊናችንን በክህደት አናጎስቁል። ይልቁንስ እንደ ቅዱስ ኤራቅሊስ ያሉ የከበሩ ምስክሮች ካሉልን እኛም እንደ አባቶቻችን “በክብር የተካከሉ” እመቤታችን ድንግል ማርያምንና ቅዱስ መስቀልን በጸጋ ምስጋና እናመሰግናቸዋለን፣ እናከብራቸዋለን እንጂ አዳምና ሔዋንን እንዳሳተ ሰይጣን፣ ያልተባለውን እንደተባለ አስመስለው ከቀናች አስተምህሮ ሊያወጡን የሚደክሙትን ፊደላውያን አንከተላቸውም።

የሞት ምልክት የነበረ መስቀል የሕይወት መገኛ ሆነ!

የመስቀል በዓል የሚከበረው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት የከበረ የእንጨት መስቀል በአይሁድ ክፋት ከተቀበረበት የቆሻሻ ክምር በቅዱሳን ጸሎት፣ በምዕመናን ጥረት፣ በእግዚአብሔር ተዓምር የተገኘበትን ዕለት ለማሰብ፣ ከበዓሉም በረከትን ለመሳተፍ ነው፡፡ ጌታችን እኛን ለማዳን ሰው ሆኖ፣ የእኛን ሞት ተቀብሎ የእርሱን ሕይወት ለመስጠት በአይሁድ ዘንድ የተረገመ ተብሎ ይታወቅ በነበረው የመስቀል ስቅላት ሞትን በፈቃዱ ተቀብሎ የሞት ምልክት የነበረ መስቀልን የሕይወት መገኛ ወደመሆን ለውጦታል፡፡

ቅዱስ መስቀል ከጌታችን ትንሣኤ በኋላ የተዓምራት ምንጭ ሆኖ የሚዳስሱት ከልዩ ልዩ ደዌያት ይድኑ ነበር፡፡ ይህም የአይሁድን የሐሰት ወሬ የገለጠ ነበር፡፡ አይሁድ በሐሰት ወሬ ጌታችን ከሞት ተለይቶ መነሳቱን ይክዱ ነበርና፡፡ ይልቁንም ደቀ መዛሙርቱ ሥጋውን ሰረቁት እንጂ አልተነሳም ይሉ ነበር፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት ደግሞ በእውነት ሞትን ድል አድርጎ የተነሣውን፣ ከትንሣኤም በኋላ በልዩ ልዩ መንገድ የተገለጠላቸውን የጌታችንን ትንሣኤ አጽንተው ይመሰክሩ ነበር፡፡ ከቅዱስ መስቀሉ የተነሳ የሚደረገው ተዓምር የአይሁድን ሐሰት፣ የቅዱሳን ሐዋርያትን እውነት ስለገለጠ ብዙዎች በክርስቶስ አምነው ይጠመቁ ነበር፡፡ አይሁድም በዚህ ተበሳጭተው በኢየሩሳሌም ከተማ ባለ ቆሻሻ መጣያ ቅዱስ መስቀሉን ቀብረው በዘመናት ሂደት የቆሻሻ ተራራ ፈጠሩበት፡፡

የአይሁድ ተንኮል የክርስትናን መስፋፋት አላስቀረውም!

ምንም እንኳ የአይሁድ ተንኮል የሐዋርያትን አገልግሎት፣ የክርስትናን መስፋፋት ባያስቀረውም የድኅነታችን ዓርማ፣ የሕይወት ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም መገኛ ቅዱስ መስቀል መጣልና መጥፋት በዘመኑ የነበሩ ክርስቲያኖች “የቤትህ ቅንዓት በላኝ” (መዝ. 68፡9፣ ዮሐ. 2፡17) እያሉ እንዲቆጩ ያደርጋቸው ነበር፡፡ ይሁንና በዘመኑ ኃያላን የነበሩት የሮማ ነገሥታት ጣዖት አምላኪዎች ስለነበሩ ክርስቲያኖችን በማሳደድና በመግደል፣ የክርስትና ቅርሶችንም በማጥፋት የሚታወቁ ስለነበሩ የመስቀሉን ነገር ማንሳት ከባድ ነበር፡፡ ከዘመናት በኋላ የእውነት አምላክ እግዚአብሔር ሥራውን የሚሰራበት፣ ተዓምራቱን የሚገልጥበት ጊዜ መጣ፡፡ “የቤትህ ቅንዓት በላኝ” እያሉ ስለክርስቶስ መስቀል መጥፋት ይጨነቁ ከነበሩ ጽኑዓን ክርስቲያኖች አንዷ ቅድስት እሌኒ ነበረች፡፡ እርሷም የክርስቶስን መስቀል መሳለም፣ ከተቀበረበት ፈልጎ ማውጣት ተምኔቷ ነበር፡፡ በ326 ዓ.ም. ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ስለነገሠ ጽኑ ክርስቲያን የሆነች እናቱ ቅድስት እሌኒ መስቀሉን መፈለግ ጀመረች፡፡ ፍለጋዋ ግን አስቸጋሪ ነበር፡፡

ከ70 ዓ.ም. ጀምሮ ኢየሩሳሌም በወራሪዎች ፈራርሳ፣ ህዝቡም ተበትኖ ስለነበር ታሪኩን የሚያውቅ ማግኘት ከባድ ነበር፡፡ የቤተክርስቲያንን ታሪክ ያለምስክር የማይተው ጌታ ግን ቅድስት እሌኒን ኪራኮስ ከሚባል አረጋዊ ጋር አገናኛት፡፡ ኪራኮስም ለንግሥት እሌኒ “ከእነዚያ ሦስት የቆሻሻ ተራሮች በአንዱ መስቀሉ ተቀብሯል፡፡” አላት፡፡ አይሁድ ግራ ለማጋባት ሦስት የቆሻሻ ተራሮችን ከ300 ዓመት በላይ በሆነ ጊዜ ፈጥረው ነበርና ለንግሥት እሌኒ ትክክለኛውን ተራራ መርጦ ለመቆፈር በጥበበ እግዚአብሔር የእንጨት ደመራን ደምራ በመለኮስ እጣን ጨመረችበት፡፡ የደመራው እሳትና ጭስ የቅዱሳን ጸሎት ከሚያርግበት እጣን (ራዕይ. 5፡8) ጋር ተቀላቅሎ መስቀሉ የተተከለበትን ተራራ ጠቆመ፡፡ እንጨቶችና ቅጠሎች በአንድነት ነድደው የእንጨቶች ሁሉ ንጉሥ የሆነ ቅዱስ መስቀል የተቀበረበትን አሳዩ፡፡ እመቤታችን ግዕዛን ካላቸው ፍጡራን (ሰዎችና መላእክት) ሁሉ የበላይ እንደሆነች ቅዱስ መስቀልም ግዕዛን ከሌላቸው ፍጡራን (እንስሳትና ዕጽዋት) የበላይ መሆኑ ተገለጠ፡፡

ቅድስት እሌኒ ቅዱስ መስቀሉን ከተቀበረበት ያወጣችው መጋቢት 10 ቀን ነው::

ያን ተራራ ከመስከረም 17 እስከ መጋቢት 10 ድረስ ከስድስት ወራት በላይ ቆፍረው ሦስት መስቀሎችን አገኙ፡፡ ከእነርሱ አንዱ ጌታችን የተሰቀለበት ሲሆን ሁለቱ ደግሞ በግራና በቀኙ የተሰቀሉት ሽፍቶች መስቀል ነበር፡፡ የቅድስት እሌኒ መንግስታዊ ባለጸግነትና ጥበብ ተራራ መቆፈር እንጂ እውነተኛ የክርስቶስ መስቀልን ከሚመሳሰሉት የሽፍቶች መስቀል መለየት አያስችልም፡፡ ቅድስት እሌኒም ቀድማ እንዳደረገችው በጥበቧና በጥረቷ ብቻ ሳትመካ በፈቃደ እግዚአብሔር እውነተኛው መስቀል እንዲገለጥላት ከካህናትና ምዕመናን ጋር ጸሎት አቀረበች፡፡

የተዓምራት ባለቤት እግዚአብሔርም ከቅዱስ መስቀሉ ልዩ ልዩ ተዓምራትን ገለጠ፡፡ የጌታ መስቀል በተዓምራቱ ከሽፍቶቹ መስቀሎች ተለይቶ ታወቀ፡፡ ቅድስት እሌኒም የጌታን መስቀል አገኘች፤ ተምኔቷ ተፈጸመ፡፡ ከዘመናት በኋላም በየሀገራቱ ያሉ ክርስቲያን ነገሥታት መስቀሉን ለበረከት ተካፈሉት፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያም በደጉ ክርስቲያናዊ ንጉሥ በአጼ ዳዊት ዘመን የጌታችንን ግማደ መስቀል (የቀኙን ክፍል) በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በደጋግ ምዕመናንና ነገሥታት እምነትና ትጋት አገኘች፡፡ ዛሬ በግሸን ደብረ ከርቤ የሚገኝ ይህ መስቀል ከብሉይ ኪዳን ስጦታችን ከታቦተ ጽዮን ቀጥሎ ከጌታ ሀገራችን ኢትዮጵያ የተቀበለችው የእምነት ስጦታ ነው፡፡

ቅድስት እሌኒ መስቀሉን ለማግኘት ያደረገችው ፍለጋ የክርስትና ሕይወት ምሳሌ ነው፡፡

በክርስቶስ ክርስቲያን የተባላችሁ የእግዚአብሔር ልጆች አስተውሉ ቅድስት እሌኒ መስቀሉን ለማግኘት ያደረገችው ፍለጋ፣ ጥረትና የእግዚአብሔር ረዳትነት ለእያንዳንዳችን የክርስትና ሕይወት ምሳሌ የሚሆን ነው፡፡ የክርስትና ዓላማ ሰማያዊ መንግስትን መውረስ ነው፡፡ ያለ እምነት (በክርስቶስ አምላክነት ሳያምኑ) ሰማያዊ መንግስትን ማግኘት አይቻልም፡፡ (ሮሜ. 3፡25) ያለ እምነት በሥራ በመመካት የሚገኝ ጽድቅ የለም፡፡ (ሮሜ. 9፡31) ይሁንና በዘመናችን ስንፍናቸውን በጥቅስ ለመሸፈን የሚፈልጉ፣ መጽሐፍ ቅዱስን በተራ ጥራዝ ነጠቅ የመረጣ ንባብ ለሚረዱና ለሚተረጉሙ ሰዎች (picky readers) እንደሚመስላቸው እምነት ያለሥራ ለድኅነት የሚያበቃ አይደለም፡፡ ሰዎችን ከአጋንንት የሚለያቸው እምነት ሳይሆን በእምነት ላይ ተመርኩዞ የሚደረግ በጎ ምግባር ነው፡፡

እምነቱን በምግባር የማይገልጽ ሰውም በእግዚአብሔር መንግስት ድርሻ የለውም፤ ከአጋንንት ጋር ይቆጠራል እንጂ፡፡ (ያዕቆብ 2፡17-26፣ ሐዋ. 14፡22) በምግባራችን ደካሞች ብንሆን እንኳ ሰው በምግባሩ ብቻ እንደማይድን አውቀን የእግዚአብሔርን ረዳትነት ተስፋ እያደረግን የአቅማችንን ልንፈጽም ይገባል እንጂ በውድድር መሀል ህጉን እንደሚቀይር አጭበርባሪ “ለመዳን ስራ አያስፈልግም” ለሚል ፍጹም ሰይጣናዊ ማመቻመች ተላልፈን መሰጠት የለብንም፡፡ ይህንንም ዛሬ የተቀደሰ ታሪኳን ከምናነሳላት ከቅድስት እሌኒ መማር እንችላለን፡፡ ጽኑዕ ክርስቲያን የሆነች እምነትን ከምግባር በተዋሕዶ ያስተሳሰረች ቅድስት እሌኒ በሥራዋ ብቻ መስቀሉን ፈልጋ አላገኘችውም፤ ፍለጋዋ በእምነት የተመሠረተ ነበር፡፡ እንዲሁም በእምነት ተመክታ እንደሰነፎች “ጌታ ተራራውን እንዲቆፍርላት” በመመኘት አላቆመችም፡፡ የራሷን ድርሻ ስለተወጣች ከአቅሟ በላይ የሆነውን በእምነት የፈለገችው ጌታ ገለጠላት፡፡ እኛም ከአስመሳዮች ማታለል ተጠብቀን እምነታችንን በሥራ ልንተረጉም እንደሚገባ ትምህርት ስለሆነችን ታሪኳን እንዘክራለን፣ በጸሎታችን እናስባታለን፣ በጸሎቷ እንማጸናለን፡፡ ክርስቲያን በሕይወተ ሥጋ ካለው የጸሎት ኃይል ይልቅ ከሥጋ ሞት በኋላ የሚኖረው ጸሎት የበለጠ ነውና፡፡

ቀደምት ሊቃውንት በዓለ መስቀሉ መስከረም 17 ቀን እንዲሆን ወስነዋል!

ወደቀደመ ነገራችን እንመለስና ቅድስት እሌኒ ቅዱስ መስቀሉን ከተቀበረበት ያወጣችው መጋቢት 10 ቀን ነው፡፡ ይሁንና ቀደምት ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት በዓሉ መስቀሉ ከተቀበረበት ከወጣበት ቀን ይልቅ ደመራው በተለኮሰበት፣ ቁፋሮው በተጀመረበት፣ በቅዱስ መስቀል ስም የታነጸ ቤተክርስቲያን ቅዳሴ ቤት በከበረበት መስከረም 17 ቀን እንዲሆን ወስነዋል፡፡ ለዚህ ከሚቀርቡ ምክንያቶች ውስጥ አንዱ መጋቢት 10 የፆም ወቅት ስለሆነ በመስቀሉ መገኘት እንደተደሰቱ እንደ ንግስት እሌኒና በዘመኗ የነበሩ ምዕመናን በዓሉን በደስታ፣ በመብል በመጠጥ ለማክበር ስለማይመች ነው፡፡ ይህም ለቅዱስ መስቀል ብቻ ሳይሆን ለሌሎች በአርባ ፆም የሚከበሩ የንግሥ በዓላትም የሚሰጥ አመክንዮ ነው፡፡ ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ መስከረም ለኢትዮጵያውያን የዘመን መለወጫ ወር ስለሆነ ቅዱስ መስቀልም በብዙ መልክ የአዲስ ዘመን ምልክት ስለሆነ የአዲስ ዘመንን ምልክት በአዲስ ዘመን መጀመሪያ ለማክበር ነው፡፡

ቅዱስ መስቀል የአዲስ ዘመን ብስራት መሆኑን ማሳያዎች 

ቅዱስ መስቀል በዓለመ መላእክት ዲያብሎስ (ሳጥናኤል) በቅዱሳን መላእክት ላይ የነበረው ኃይል በኋላ ዘመን በሚገለጥ የመስቀል ኃይል የተሸነፈበት፣ በዓለመ መላእክት ለነበረች ቤተ ክርስቲያን አዲስ ዘመን የተበሰረበት ምልክት ነው፡፡ (ራዕይ 12፡11) በዘመነ ብሉይ መስቀል የመርገም ምልክት ነበር፡፡ በዘመነ ሐዲስ ግን ቅዱስ መስቀል ከኦሪት መርገም የተላቀቅንበት የሐዲስ ኪዳን (የአዲስ ዘመን) የምንመካበት ምልክት ነው፡፡ (ገላትያ 3፡13፣ ገላትያ 6፡14፣ 1ኛ ቆሮ. 1፡18)

“መስቀል” ማለት መከራ ማለት ነው፡፡ መስቀል ስንልም ጌታ የተሰቀለበትን ቅዱስ መስቀል ብቻ ሳይሆን እኛን ለማዳን ከጽንሰት እስከ ሞት የተቀበለውን መከራ ሁሉ ማለታችን ነው፡፡ መስቀል የሚለው በዋናነት የክርስቶስን የመስቀል ላይ መከራ ለመግለጽ የሚውለውም የመከራው ከባዱ ክፍልና፣ ፍጻሜ ስለሆነ ነው፡፡ በዘመነ ብሉይ የነበሩ ቅዱሳን ስለሃይማኖታቸው፣ ስለ እግዚአብሔር ቃል እጅግ ብዙ መከራዎችን (መስቀል) ተቀብለዋል፡፡ ይሁንና ድኅነት በራስ ጥረት ሳይሆን በእምነት የሚገኝ የእግዚአብሔር ስጦታ ነውና ከክርስቶስ ቤዛነት (መከራ መስቀል) በፊት የነበረ መከራቸው ድኅነትን አላስገኘላቸውም፡፡ እንዲያውም መልካም ስራቸው “እንደ መርገም ጨርቅ” ሆነ ተብሏል፡፡ (ኢሳይያስ 64፡6)

ከጌታችን መከራ መስቀል በኋላ ግን ስለ ሃይማኖት (እምነት) መከራ መቀበል እንደ ዘመነ ብሉይ ዋጋ የሌለው ሳይሆን በእምነት ተደግፈን ወደ እግዚአብሔር መንግስት የምንገባበት መሰላል እንጂ ዋጋ የሌለው አይደለም፡፡ (ሐዋ. 14፡22፣ ማቴ. 5፡1-ፍጻሜ) ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም “መስቀሉን ተሸክሞ የማይከተለኝ ለእኔ ሊሆን አይገባውም፡፡” (ማቴ. 10፡38) ያለው ይህንኑ ነው፡፡ ቅዱስ መስቀል እንደ መርገም ጨርቅ ይቆጠር የነበረ ምግባር ኃይል ያገኘበት የአዲስ ዘመን ብስራት ነው፡፡ (ፊልጵ. 2፡12)

መስከረም የአዲስ ዘመን መገለጫ መሆኑ አከባበሩም ከደመራና ከመስቀል ጋር የተያያዘ መሆኑ በልዩ ልዩ የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች ዘንድ የታወቀ ነው፡፡ መሠረት ባለው መንፈሳዊ አስተምህሮ የማይመሩ፣ ይልቁንም የታሪክ አጋጣሚዎችንና ማኅበራዊ ተቃርኖዎችን በመጠቀም ለዘመናት በኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ጸንቶ ይኖር የነበረውን (በተለይም በደቡቡ የኢትዮጵያችን ክፍል የሚገኙ ምዕመናንን) በለብ ለብ ይዘት አልባ ጩኸት (contentless noise) በክርስትና ስም ወደ ተሳሳተ አስተምህሮ የወሰዱ ቡድኖች ለዘመናት የሰሩት ታሪክን የማጥፋት ተንኮል ቢያደበዝዘውም ያላጠፋው የታሪካችን አካል ነው፡፡ እኛም ኦርቶዶክሳውያን እንደ ቅድስት እሌኒ የተቀበረውን የምናወጣበት፣ የተንኮልን ተራራ በጥበበ እግዚአብሔር የምንንድበት ጥበብ ከመቼውም ጊዜ በላይ የሚያስፈልገን ወቅት ላይ እንገኛለን፡፡ ይህን ወቅት መሻገር የምንችለው እንደ አባቶቻችን መንፈሳዊውን ነበር በማስቀደም ቤተ ክርስቲያንን የየትኛውም ፖለቲካዊ አጀንዳ ማራገቢያ ከማድረግ ስንጠበቅ ነው፡፡

የመስቀሉ ቃል ለእኛ የእግዚአብሔር ኃይል ነው!

ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት ነው፡፡ ለእኛ ለምንድን ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነው (1ኛ ቆሮ 1፡18)፡፡ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ‹‹የመስቀሉ ቃል›› የሚለውን በሦስት ይተረጉሙታል፡፡ የመጀመሪያው በመስቀል ላይ የተሰቀለው ቃል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ሁለተኛው ጌታችን በመስቀል ላይ የተናገረው ቃል ነው፡፡ እነዚህም ሰባቱ አጽርሀ መስቀል ናቸው፡፡ በሦስተኛም የመስቀሉ ቃል የሚለው ነገረ መስቀሉን (መከራውንና ምልክትነቱን) ነው፡፡

ሰቃልያነ እግዚእ አይሁድ ክርስቶስን አንገላተው የሰቀሉት ምዕመናን እንዳይከተሉት፣ እንዳያምኑበት አስበው ነበር። ኃይል ያሳጡት መስሏቸው ነበር። አይሁድ የድካም ምልክት የመሰላቸው የጌታችን ትሁት ስብእና (በአትኅቶ ርእስ የተፈፀመ የማዳን ሥራ) ለእኛ በስሙ ለምናምን ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነው። ስለሆነም “የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን”፣ እንመካበታለንም። “ይህም ለአይሁድ ማሰናከያ ለአሕዛብም ስንፍና (ሞኝነት) ነው። ለእኛ ለዳንነው ግን…ክርስቶስ የእግዚአብሔር ኀይል ነው።” (1ኛ ቆሮ. 1:23-25) ስለሆነም “ልዑል ክንዱን ሰደደልን”፣ እግዚአብሔር የኃይሉን መገለጫ ኢየሱስ ክርስቶስን ልኮ አዳነን በማለት ዘወትር በሰኞ ውዳሴ ማርያም እናመሰግነዋለን።

በሁለተኛ ደረጃ የመስቀሉ ቃል ተብለው የሚተረጎሙት ጌታችን በዕፀ መስቀል ላይ፣ ዘላለማዊ አገልግሎትን ባገለገለበት መቅደስ ላይ ሆኖ የተናገራቸው ሰባቱ አጽርሃ መስቀል (የመስቀል ላይ ንግግሮች) ናቸው። ፈያታዊ ዘየማንን (በጌታችን ቀኝ የተሰቀለውን ሽፍታ) ያዳኑ፣ ዲያብሎስን በእሳት ዛንጅር ያሰሩ፣ የአዳምንና የልጆቹን የአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን የሰቆቃ ለቅሶ ያስቀሩ፣ እመቤታችንን በዮሐንስ በኩል ለቤተ ክርስቲያን በእናትነት የሰጡ፣ የሰው ልጆችን የጽድቅ ጥማት ያረኩ፣ ከአዳምና ከሔዋን ጀምሮ የነበሩ፣ እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚኖሩ ምዕመናንን በደልና ኃጢአት ያስተሠረዩ፣ የድኅነት ተስፋቸውን “ተፈፀመ” ብለው ያወጁ እነዚህ አምላካዊ የመስቀል ላይ ቃላት ጌታችንን ለሰቀሉ አይሁድ፣ ነገረ ስቅለቱን እንደ ተራ ታሪክ ለሚያስቡ ሰዎች የድካምና የሞኝነት ንግግሮች ቢመስሉ እንኳ ለእኛ በመስቀሉ ለዳንን፣ ለምንድን ምዕመናን ግን የእግዚአብሔር ኀይል መገለጫዎች ናቸው። “የእግዚአብሔር ስንፍና ከሰው ይልቅ ይጠበባልና፣ የእግዚአብሔርም ድካም ከሰው ይልቅ ይበረታልና።” (1ኛ ቆሮ. 1:25)

በሦስተኛ ደረጃ የእግዚአብሔር ኀይል የተባለው እግዚአብሔር ራሱ ያገለገለበት መቅደስ፣ ቅዱስ መስቀል ነው። ቅዱስ መስቀል የክርስቶስ የሚያድን መከራ፣ የሚፈውስ ቁስል ወካይና ክርስቲያኖች ቀስት ከተባለ የዲያብሎስ ፍላጻ ራሳችንን፣ ቤተሰቦቻችንን፣ ሀገራችንን የምንጠብቅበት ከእግዚአብሔር የተሰጠ ምልክት ነው። ክቡር ዳዊት በመዝሙሩ እንዲህ እንዳለ “ወወሃብኮሙ ትእምርተ ለእለ ይፈርሁከ፣ ከመ ያምስጡ እም ገፀ ቅስት ወይድኃኑ ፍቁራኒከ/ ከቀስት ፊት ያመልጡ ዘንድ ለሚፈሩህ ምልክትን ሰጠሃቸው፣ ወዳጆችህ እንዲድኑ።” (መዝ. 59:4)  በዓለመ መላእክት ለዲያብሎስና ሰራዊቱ፣ በዘመነ ሐዋርያት ለሲሞን መሠርይና መሰሎቹ፣ በዘመነ ሊቃውንት ለንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ወደረኞች፣ በእኛ ዘመንም ላሉ የመስቀሉ ጠላቶች የመስቀል ምልክት ኃያልነት አልገባቸውም፣ አይገባቸውም።

ስለሆነም አካላዊም አስተሳሰባዊም ቆሻሻ እየከመሩ መስቀሉን ሊያጠፉ፣ ትእምርትነቱን በአልባሌ ነገር ሊተኩ ሞክረዋል፣ እየሞከሩም ነው። ለእኛ ለዳንን፣ ለምንድን ግን መስቀል የድኅነታችን ዓርማ፣ የቤተ ክርስቲያን በመከራ ውስጥ አሸናፊ የመሆን ምልክት ነው። ስለሆነም ሊቃውንት አባቶቻችን እንዳስተማሩን “ተሲነነ ዘወንጌል ቃለ ኅቡረ ተመርጉዘነ መስቀለ/የወንጌልን ቃል ተጫምተን መስቀልን በኅብረት (በአንድነት) እንመረኮዛለን።” ብለን እንዘምራለን፣ በሕይወታችን ኹሉ በቅዱስ መስቀል ምልክት የጠላቶቻችንን ቀስት እንመክታለን፣ እንደ ቅዱሳን መላእክትም የዲያብሎስን ሠራዊት እናሸንፍበታለን።

ይህንንም ዘወትር በጸሎታችን እንዲህ እያልን እንመሰክራለን:- “መስቀል ኃይልነ፣ መስቀል ጽንዕነ፣ መስቀል ቤዛነ፣ መስቀል መድኃኒተ ነፍስነ፣ አይሁድ ክህዱ ንሕነሰ አመነ፣ ወእለአመነ በኃይለ መስቀሉ ድኅነ/መስቀል ኃይላችን ነው፣ መስቀል መጽኛችን (መጽናኛችን) ነው፣ መስቀል ቤዛችን (ቤዛነት የተፈጸመበት መቅደሳችን) ነው፣ መስቀል የነፍሳችን መዳኛ ነው። አይሁድ ይክዱታል፣ እኛ ግን እናምነዋለን (መቅደስነቱን፣ መድኃኒትነቱን እንመሰክራለን)፣ ያመነውም እኛ በመስቀሉ እንድናለን፣ ድነናልም።” (ጸሎት ዘዘወትር/የዘወትር ጸሎት)

ማጠቃለያ: መስቀሉን በመስቀል

በመስቀል በዓል ገኖና ከብሮ መነገር፣ መታየት፣ መብራራት፣ መሰበክ ያለበት ሕይወት የሆነን የክርስቶስ መስቀል (መከራ)፣ ድል ያደረግንበት፣ የምናደርግበት የቅዱስ መስቀል ክብር፣ አይሁድ በተንኮል የቀበሩት የጌታ መስቀል መገኘት፣ የመስቀሉን መንፈሳዊ ትርጉምና ታሪካዊነትም በመጠቀምም የምዕመናንን መንፈሳዊ ሕይወት ማጽናት ብቻ መሆን አለበት፡፡ ባለፉት ዓመታት “መስቀልን ባለማክበር ፖለቲከኞችን ማበሳጨት” በሚል ተንኮለኛ አጽራረ ቤተ ክርስቲያን በመናጆ አስተሳሰብ የቤተ ክርስቲያንን በዓል በሞኞች ልጆቿ ሲያስተጓጉሉ ታዝበናል፡፡ ለምሳሌ ከተወሰኑ ዓመታት በፊት ለተቃውሞ ፖለቲካ ማድመቂያ ሲባል በተንኮለኞች ምክር፣ በአላዋቂና ቂላቂል ሰዎች አስተባባሪነት መስቀልን በአደባባይ ያለማክበር ውሳኔ ማስታወስ ይቻላል።

ያ እንደ ቀልድ የተጀመረ ሃይማኖትና ፖለቲካን በወገንተኝነት የመቀላቀል ክፉ ልማድ የተመኘነው ይመስል አሁንም “መስቀልን አታከብሩም!” በሚሉ አፅራረ ቤተ ክርስቲያን ፉከራና የሞኞች ምዕመናን “መስቀልን ባለማክበር የፖለቲካ ትርፍ ፍለጋ” የሚያመጣውን መዘዝ እያየነው ነው።  ስለሆነም “በመስቀል በዓል ላይ ፖለቲካዊ ዓላማን በማራመድ” የሚገለጸው የመለካውያን አስተሳሰብ ቤተ ክርስቲያንን የሚጎዳ እንጂ የሚጠቅም ስላልሆነ የክርስቲያናዊ አንድነት መገለጫ የሆነ መንፈሳዊ በዓላችንን፣ እግዚአብሔር ያገለገለበትን የቅዱስ መስቀልን ክብር መንፈሳዊም ዓለማዊም ዕውቀትና ብልሃት በሌላቸው ሰዎች አስተሳሰብ እየተመራን ዕንቁአችንን በእሪያዎች ፊት መጣል አይገባንም እንላለን፡፡

ቤተ ክርስቲያን መመዘን በሚገባት መንፈሳዊ ሚዛን ሳይሆን ጥራዝ ነጠቆች በጫኑባት ልዩ ልዩ ርዕዮተ ዓለማዊ መነጽሮች መሆን የለበትም፡፡ የቤተ ክርስቲያን ጠላቶች ስስ ጉዳዮችን እየመረጡ ቤተክርስቲያንን ከምዕመናን፣ ምዕመናንን ከቤተ ክርስቲያን ለመነጠል ሲጠቀሙበት የየግልና ቡድን አስተሳሰባችንን ወደጎን በመተው ቅዱሳን ሐዋርያት የሰበሰቧትን፣ በየዘመኑ የተነሱ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የወንጌል መብራቶች ያጸኗትን የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ አንድነት በስሜት ሳይሆን በጥበብ ልንጠብቅ ይገባናል፡፡ ቤተ ክርስቲያን የሁሉ እናት መሆኗ የሚገለጠው በምድራዊ ምልክት ሳይሆን “የአዲስ ዘመን ብስራት” በሆነ በቅዱስ መስቀልና በመስቀሉ የተገለጠውን የእግዚአብሔር ማዳን በመግለጥ ነውና፡፡

አይሁድ እግዚአብሔር ያገለገለበትን መቅደስ (ቅዱስ መስቀልን) በመናቅና በማቃለል የቆሻሻ ክምር ቢደፍኑበትም የእነርሱ ክፉ ሥራ፣ የመስቀሉ ክብር እግዚአብሔር በፈቀደው ጊዜ የቀደመ ባሏ አናንቆ በጣላት፣ እግዚአብሔር ግን “የመቅደሱ ሠራተኛ” አድርጎ ባከበራት በእሌኒ ንግሥት ጥረት ድጋሚ ተገልጧል። ዛሬም ተረፈ አይሁድ የመስቀሉን ክብር መከፋፈልና ጥላቻን በሚወልድ ነገር ግን በሽንገላ ንግግር “ስለ ፍቅር” አብዝቶ በሚያወራ የጥላቻ ፖለቲካ ነጥብ ማስቆጠሪያ ክምር፣ በዘፈን በዳንኪራና በትርኢት ቁልል፣ ባሕሉን ሃይማኖት ሃይማኖቱን ባሕል በሚያስመስል ማምታታት ሊቀብሩት ሲሞክሩ እናያቸዋለን። እኛ ግን እግዚአብሔር ያገለገለበትን መቅደስ የምድራዊ ልዩነት፣ ወይም መንፈሳዊነት የተለየው ዓለማዊ አንድነት ማሳያ አድርገው ከሚስሉ ተረፈ አይሁድ ተለይተን እንደ አባቶቻችን መስቀሉን በመስቀል ሥፍራ እናቆማለን። እንደ ንግሥት እሌኒ በመስቀሉ ላይ የተደረቱ፣ የቆሸሹ መጋረጃዎችን በቀናች ኦርቶዶክሳዊት አስተምህሮ ብርሃንነት ለይተን እናሳያለን። በሊቁ አባታችን ቅዱስ ኤራቅሊስ አገላለፅ እግዚአብሔር ያገለገለበት መቅደስ፣ የቅዱስ መስቀሉ በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን እንላለን፡፡ አሜን ለዘለዓለም።

ስብሐት ለእግዚአብሔር፣ ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር

1 thought on “ቅዱስ መስቀል: እግዚአብሔር ያገለገለባት መቅደስ ወዮ እንደምን ያለች ናት?!

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s