ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን መሥራት: ትኩረት የሚሹ ዐበይት ጉዳዮች

መግቢያ

አምላካችን እግዚአብሔር ሰማይና ምድር የማይወስኑት ምሉእ በኵለሄ (በዓለም ሁሉ የመላ) አምላክ ነው። በዓለም ሁሉ የመላ አምላካችን ራሱን በተለየ ሁኔታ በረድኤት ይገልፃል። እግዚአብሔር ራሱን በረድኤት ከሚገልፅባቸው ቦታዎች ቀዳሚዎቹ ስሙ የሚቀደስባቸው፣ አምላክነቱ የሚመሰከርባቸው ሕንፃ አብያተ ክርስቲያናት ናቸው። በየዘመናቱ የነበሩ ቅዱሳን በታላቅ መንፈሳዊ ትጋት የተቀደሱ መቅደሶችን አንጸው ለሰማያዊው እግዚአብሔር የተቀደሰ ምድራዊ ማደሪያን አዘጋጅተዋል። በቅን ልቦና፣ በመንፈሳዊ ሀሳብ ያዘጋጁለትን መቅደስም የቅድስና ምንጭ ቅዱስ እግዚአብሔር ባርኮላቸዋል፣ የበረከት የጸጋ መገኛም አድርጎላቸዋል።

አስቀድሞ ሊቀ ነቢያት ሙሴ ሕዝበ እስራኤል ከእግዚአብሔር ጋር የሚገናኙበትን ደብተራ ድንኳን በእግዚአብሔር ትዕዛዝ በመሥራት የመጀመሪያው ነው። ሕዝበ እስራኤል በደብተራ ድንኳን ለ900 ዘመናት ያህል ሲገለገሉ ቆይተው ጠቢቡ ሰሎሞን የመጀመሪያውን ቤተ መቅደስ በእግዚአብሔር ፈቃድ እንዲሠራ ሆኗል። ይህ ቤተ መቅደስ እግዚአብሔር “ዓይኖቼና ልቤ በዚህ ይሆናሉ” ብሎ ቃል ኪዳን የገባበት ነበር። ይህም ቤተ መቅደስ በ500 ዓ.ዓ አካባቢ የፋርስ ንጉሥ በነበረው በናቡከደነፆር ቢፈርስም ከተወሰኑ ዓመታት በኋላ በዘሩባቤል እንደገና ተሠርቶ ነበር። ይህን ቤተ መቅደስ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ሆሳዕና ገብቶ ቤቴ ብሎታል፣ አጽድቶታል። በተነገረው ትንቢት መሠረትም በ70ዓ.ም በጥጦስ የሚመራ የሮም ሠራዊት ኢየሩሳሌምን ሲያጠፋት ቤተ መቅደሱንም አፍርሶታል።

በሐዲስ ኪዳን የነበሩት የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች ለጸሎት የሚተጉት በቤት ውስጥ ነበር። ለምሳሌም የማርቆስ እናት የማርያምን ቤት መጥቀስ ይቻላል። በዘመነ ሰማዕታትም የዓላውያን ነገሥታት ግፍና መከራ በክርስቲያኖች ላይ ከብዶ ስለነበር ክርስቲያኖች ጸሎት የሚያደርጉት፣ መሥዋዕትንም የሚያቀርቡት በግበበ ምድር (ካታኮምብ) ውስጥ ነበር። ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን በይፋ መሠራት የተጀመረው ክርስትና ከመሳደድ ወጥቶ ብሔራዊ ሃይማኖት ሆኖ በታወጀበት በንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ዘመን ነው። ከዚያን ዘመን ጀምሮ በተለያየ ቦታ፣ መጠን፣ ቅርፅና ዲዛይን፣ በተለያዩ ዘመናት ብዙ አብያተ ክርስቲያናት ታንጸዋል። በተለያዩ ዘመናት በእነዚህ ሕንፃዎች ላይ ጥቃት ቢደርስባቸውም ብዙዎቹ ከእኛ ዘመን ደርሰዋል።  ከቅርብ ዘመን ወዲህ ግን ከሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ግንባታ ሂደት ጋር ተያይዞ ብዙ ችግሮች ይስተዋላሉ። በዚህች ጽሑፍም ቢሻሻሉ የምንላቸውን አስተሳሰቦችና አሠራሮች እንዳስሳለን።

ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን

‘ቤተ ክርስቲያን’ የሚለው ቃል አንዱ ዘይቤያዊ ትርጉሙ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያንን ያመለክታል፡፡ ይኸውም የእግዚአብሔር ቤት፣ የክርስቲያኖች የጸሎት ቤት፣ የክርስቲያኖች መኖሪያ ማለት ነው፡፡ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ክቡር ደም መሠረትነት የምትተከል፣ በብጹዓን ሊቃነ ጳጳሳት በቅዱስ ሜሮን የከበረች፣ ሥላሴ በአንድነት በሦስትነት የሚመሰገኑባት፣ የክርስቶስ ሥጋዌ የሚነገርባት፣ በቀራንዮ የፈሰሰ የጌታችን ፈዋሽ ደም ዕለት ዕለት ከመንጠብም በላይ እንደአዲስ የሚቀዳባት፣ የከበረ ሥጋው የሚፈተትባትና ለምዕመናን የሚታደልባት ቅድስት መካን “ቤተ ክርስቲያን” ተብላ እንደምትጠራ ቅዱሳት መጻሕፍት በስፋት ያስተምሩናል።

ልበ አምላክ ክቡር ዳዊት “ወደ እግዚአብሔር ቤት እንሂድ ባሉኝ ጊዜ ደስ አለኝ” (መዝ. 121: 1) ብሎ እንደዘመረው፣ ቅዱስ ሉቃስም “በቤተ ክርስቲያንም አንድ ዓመት ሙሉ ተሰበሰቡ” (ሐዋ. 11፡21) እንዳለው የቤተ ክርስቲያን አንደኛው ዘይቤአዊ ትርጕም ሕንፃ ቤተ ክርስቲያንን ያመለክታል፡፡ በተጨማሪም “የእግዚአብሔር ቤት” (ዘፍ. 28: 17)፣ “በምሕረትህ ብዛት ወደ ቤትህ እገባለሁ” (መዝ 5: 7)፣ “የአባቴ ቤት” (ሉቃ 2፡49)፣ “የእግዚአብሔር ቤት” (ዕብ 10፡21) የሚሉት ንባባት ይህን የሚያስረዱ ማሳያዎች ናቸው፡፡ በተለይም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለልጁ ለጢሞቴዎስ “ብዘገይ ግን፣ በእግዚአብሔር ማደሪያ ቤት መኖር እንዴት እንደሚገባ ታውቅ ዘንድ እጽፍልሃለሁ፤ ቤቱም የእውነት ዓምድና መሠረት፣ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ነው” (1ኛ ጢሞ. 3፡15) በማለት የገለጠው በዋናነት የእግዚአብሔር ቤት (ሕንፃ) ቤተ ክርስቲያንን ነው፡፡

ሕንፀተ ቤተ ክርስቲያን

በሰኔ 20 ስንክሳር እንደተገለጠው ቅዱሳን ሐዋርያት በፊልጵስዮስ በአንድነት ሱባዔ ይዘው ከቆዩ በኋላ ጌታችን የሞቱትን አስነሥቶ፣ ያሉትንም ጠርቶ “በእናቴ በድንግል ማርያም ስም ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የሚሠራዉን የአብያተ ክርስቲያናት ሥራ ላሳያችሁ፤ ሥርዓቱንም ላስተምራችሁ ሰብስቤአችኋለሁ” ብሎ ወደ ምሥራቅ ይዟቸው ወጣ፡፡ በዚያ ሥፍራ የነበሩትን ሦስት ድንጋዮችንም የተራራቁትን አቀራርቦ፣ ጥቃቅኑን ታላላቅ አድርጎ ቁመቱን በ24፤ ወርዱን በ12 ክንድ ለክቶ ለቅዱሳን ሐዋርያት ሰጣቸው፡፡

ከዚህ በኋላ ቅዱሳን ሐዋርያት ሰም እሳት ሲያገኘው እንዲለመልም፣ ድንጋዩ በእጃቸው ላይ እየተሳበላቸው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑን ሠርተው ፈጽመዉታል፡፡ ይህ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን የተሠራዉም ጌታችን በዐረገ በ19ኛው፤ እመቤታችን በዐረገች በ4ኛው ዓመት ሰኔ 20 ቀን ሲሆን፣ በ21ኛው ቀን (በማግሥቱ) ኅብስት ሰማያዊ፣ ጽዋዕ ሰማያዊ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ወረደ፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችን ጋር ከሰማየ ሰማያት መጥቶ እመቤታችንን ታቦት (የክብሩ መገለጫ)፤ ሐዋርያትን ልዑካን አድርጎ፣ እርሱ ሠራዒ ካህን ሆኖ ቀድሶ ካቆረባቸው በኋላ “እምይእዜሰ አንትሙኒ ከመዝ ግበሩ /ከዛሬ ጀምሮ እናንተም እንደዚህ አድርጉ/” ብሎ አዝዟቸው በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐርጓል፡፡ ከወንጌላዊው ከቅዱስ ማርቆስ እናት ቤት ለአምልኮ ይሰበሰቡ የነበሩ ቅዱሳን ሐዋርያት (ሐዋ. 12:12) በፊልጵስዮስ በተሠራች በመጀመሪያዋ ቤተ ክርስቲያንም መንፈሳዊ ጉባኤያቸውን፣ አምልኮአቸውን ይፈጽሙ ነበር።

የሕንፃ ቤተ ክርስቲያን አሠራር

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት የአብያተ ክርስቲያናት ሕንፃዎች ቤተ ክርስቲያን፣ ደብር ወይም ገዳም ተብለው ይጠራሉ። ደብር ማለት ‘ተራራ’ ማለት ሲሆን አጥቢያ ቤተ ክርስቲያንን ያመለክታል። ተራራ ከምድር ከፍ ብሎ ዙሪያ ገባውን ለመቃኘት እንደሚያስችል ሁሉ ቤተ ክርስቲያንም ከዓለም ተለይታ፣ ከፍ ብላ፣ ጽድቅን ከኃጢአት ለመለየት የምታስችል መሆኗን ያመለክታል። በተራራ ሰዎች ከጎርፍ፣ ከመከራ እንደሚጠለሉ በቤተ ክርስቲያንም ምዕመናን ከመከራ ሥጋ፣ ከመከራ ነፍስ ይጠለሉባታልና። ገዳም ደግሞ አገልግሎቱ በገዳማውያን ሥርዓት መሠረት ስለሚከናውን ይህንን ስያሜ ይዟል።

የቤተ ክርስቲያናችን ትውፊታዊ የሥነ ሕንፃ ጥበብ ዓይነቶች አምስት ናቸው። እነርሱም ክብ ፤ መስቀል ቅርፅ ፤ ዋሻ ፤ ፍልፍል እና ሰቀልማ ናቸው። ክብ ሕንፃ አብያተ ክርስቲያናት በብዛት በገጠሪቷ ኢትዮጵያ የሚገኙ ሲሆን ባለሦስት ዙሪያ ክፍል ዙሪያ ክብ አሠራር ሆነው ውስጣቸው በሦስት ግድግዳ የተከፈለ (ቅኔ ማኅሌት፣ ቅድስት፣ መቅደስ) ሲሆን ስያሜው የተወረሰው ከግብሩ፣ ከሚሠጠው አገልግሎት ነው፡፡ መስቀል ቅርጽ ያላቸው አብያተ ክርስቲያናት ደግሞ በብዛት በከተማ አካባቢ ይገኛሉ። ይህ አሠራር የምኩራብ ዓይነት ሲሆን የተወረሠው ከአይሁድ ምኩራብና በዘመነ ክርስትናም የታላቁ ቆስጠንጢኖስ እናት ቅድስት እሌኒ በኢየሩሳሌም ካሠራችው ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡

ዋሻ አብያተ ክርስቲያናት ደግሞ በብዛት በተራራማ አካባቢዎች የሚገኙ ሲሆን በመጋረጃ የተከፈሉ ናቸው። ይህ አሠራር ራሱን ችሎ በዘመነ ሐዲስ መናንያን የሚገለገሉበት ቤተ ክርስትያን ነው፡፡ ሰማዕታት ከዓላውያን ነገሥታት ሸሽተው በዋሻ ሲሸሸጉ የጀመሩት የቤተ መቅደስ አሠራር ነው፡፡ በሩ አንድ ሲሆን በውስጥ ያሉትን ክፍሎች በአብዛኛውን ጊዜ በመጋረጃ የተከፈሉ ናቸው፡፡ ፍልፍል አብያተክርስቲያናት ደግሞ ከአንድ ቋጥኝ ተፈልፍለው የተዘጋጁ ናቸው። የቅዱስ ላሊበላ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናትን እንደምሳሌ መጥቀስ ይቻላል። ሰቀልማ የሚባለው አሠራር ደግሞ ብዙውን ጉዜ አራት ማዕዘን ቅርጽ ያለው ሆኖ ሞላላ የሆነና ከፍ ብሎ የሚታነጽ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት ሕንፃ ሃሳቡ የተወሰደው ጠቢቡ ሰሎሞን ካሠራው ቤተ መቅደስ ነው::

ትኩረት የሚሹ ዐበይት ጉዳዮች
ሕንፃ ሥላሴን ማነጽ ይቅደም!

የክርስትና ሃይማኖት ወሳኙ ግብ ሕንፃ ሥላሴ የተባለ የሰውን ልጅ መንፈሳዊ ሕይወት በወንጌል መሠረትነት ላይ መገንባትና ለእግዚአብሔር መንግስት ማብቃት ነው። ከሁሉም ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው አገልግሎትም ይህ ነው። ሕንፃ ቤተ ክርስቲያንን መገንባት የዚህ መንፈሳዊ አገልግሎት አንድ አካል እንጂ የመጨረሻ ግብ አይደለም፡፡ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎትም መመዘን ካለበት መመዘን ያለበት የምሥጢራት ተሳታፊ የሆኑ ምዕመናንን በማፍራት መሆን ይኖርበታል እንጂ ሕንፃ በማነጽ ብቻ መሆን የለበትም።

መንፈሳዊ ሕይወቱ የታነጸ ክርስቲያን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያንን በራሱ ተነሳሽነት ያንፃል፣ በረከትም ያገኝበታል። ነገር ግን ሕንፃ ሥላሴ የተባለ ሰውን በመንፈሳዊ ሕይወት በሚገባ ሳንገነባ ታላላቅ ሕንፃ አብያተ ክርስቲያናትን ለመገንባት መሞከር ውጤታማነቱ አጠያያቂ ነው። ለሕንፃ ሥራውም ቢሆን መንፈሳዊ ሕይወቱ ያልታነፀን ሰው ለሕንፃ ግንባታ በየጊዜው ገንዘብ ማዋጣት ‘ዕዳ’ ይሆንበታል። የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴዎችን ሥራ ከባድ የሚያደርገው አንዱ ምክንያት ይህ ነው።

ከዚህም ባሻገር ዛሬ ሕንፃ ሥላሴን እየገነባን ካልሄድን የሚሠራው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ለማን ይሆናል? በተለይም በዝርወት ዓለም የሚሠሩት ሕንፃዎችን ተረክቦ የሚገለገልባቸው የወደፊት ትውልድ የመኖሩ ነገር አሳሳቢ ነው። ነገሮች በዚህ ከቀጠሉ የምዕራባውያን ሕንፃ አብያተ ክርስቲያናት ላይ የደረሰው የምዕመናን ማነስና ሕንፃዎቹ ለሌላ አገልግሎት መዋል በእኛም አብያተ ክርስቲያናት ላይ ሊደርስ ይችላል። ዛሬ ዛሬ ብዙዎች ይህን ስጋት ይጋራሉ። ይኹንና ተተኪ ሕፃናትና ወጣቶችን ጨምሮ በእምነትና ምግባር የጎለመሰ ምዕመን ለማፍራት የሚደረገው እንቅስቃሴ ትኩረት አይሰጠውም። በብዙ ቦታዎች የመምህራንና የካህናት ትኩረት የሚገነቡ ሕንፃዎች መሆናቸውን ታዝበናል። በመንፈሳዊ እይታ፣ በቅዱሳት መጻሕፍት እውቀት ላልታነፀ ምዕመን በድንጋይ ላይ ድንጋይ ደርቦ ሕንፃ መሥራት ትርጉም የለውም። ሕንፃ ለሰው እንጂ ሰው ለሕንፃ አልተፈጠረምና።

የሕንፃ ሥራው የምዕመናንን ብዛትና አቅም ያገናዘበ ይሁን!

ለእግዚአብሔር ከሁሉ የሚበልጠውን ማድረግ የበለጠ ዋጋ ያስገኛል። ይሁንና በየአካባቢው የሚሠሩ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን የምዕመኑን ኢኮኖሚያዊ አቅም ከግምት ውስጥ ያስገቡ መሆን ይኖርባቸዋል። ሰማይ ጠቀስ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያንን ከአቅም በላይ በሆነ ገንዘብ፣ ጉልበትና ጊዜ ለመገንባት ከምንደክም ለመንፈሳዊ አገልግሎቱ በቂ የሚሆን ሕንፃን በጥራት ገንብተን የቤተ ክርስቲያንን የወንጌል አገልግሎት የበለጠ ተደራሽ ማድረግ የተሻለ ይሆናል። በአንድ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ላይ ዘመናችንን ሙሉ ብዙ ገንዘብ ከምናወጣ ለአገልግሎቱ የሚበቃ ሕንፃ በአጭር ጊዜ ሠርተን ቀሪውን ጊዜ ገንዘብ፣ ዕውቀትና ጉልበት ሌሎች የቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ አገልግሎቶችን ለማጠናከር ብናውለው ቤተ ክርስቲያን (የምዕመናን ኅብረት) ትሰፋለች።

እያንዳንዱ ምዕመን በቅርብ ርቀት ላይ ሄዶ የሚገለገልበት ቤተ ክርስቲያን ያስፈልገዋል። በሌላ በኩል የቤተ ክርስቲያኑን አገልግሎት በቀጣይነት ለማከናወን ደግሞ የምዕመናን ብዛትም ወሳኝ ነው። በቅርብ ርቀት ላይ ቤተ ክርስቲያን ባለበትና መንፈሳዊ አገልግሎቱ ተደራሽ በሆነበት ሁኔታም ሌላ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ከመገንባት በፊት ቆም ብሎ ማሰብ ያስፈልጋል። በታላላቅ የሀገራችን ከተሞች አብያተ ክርስቲያናት በቅርብ ርቀት የታነጹት የምዕመናንን ቁጥር ባገናዘበ መልኩ ስለተሠሩ ነው። በዝርወት ዓለም ጥቂት ምዕመናንን ይዘው በአንድ አካባቢ (በቅርብ ርቀት) ሁለተኛ ወይም ሦስተኛ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ከመገንባት ተግባብቶ አብሮ መ(ማ)ገልገል የተሻለ ይሆን ነበር።

በተግባር የሚታየው ግን እድሜ ልካቸውን “አስተዳዳሪ” እየተባሉ በምዕመናን ሕይወት ላይ ሥጋዊ የበላይነትን በሚፈልጉ ካህናትና ከዓለም በቃረሙት የልዩነት ኮተት “የራሳቸው ቤተ ክርስቲያን” በሚፈልጉ ምዕመናን የተነሳ የሚፈጠር ማለቂያ የሌለው መከፋፈል ነው። በውጭ ሀገራት የሚገኘው ምዕመን በሀገር ቤት ያሉትን ለችግር የተጋለጡ ምእመናንና አብያተ ክርስቲያናት በገንዘብ ከመርዳት ይልቅ በቅርብ ርቀት የሚተከሉ የተከፋፈሉ አጥቢያዎችን ለ40 እና 50 ዓመታት የሚቆይ እዳ ሲከፍል እንዲኖር ማድረግ ለቤተ ክርስቲያን አይጠቅምም።

ጥቂት ምዕመናንን ይዞ የመከፋፈሉ አካሄድ ሕንፃ በመገንባትም ይሁን አገልግሎቱን ከማስቀጠል አንጻር ያለው ጥቂት ምዕመን ላይ ጫና እንደሚፈጥር ያየ ያውቀዋል። በአንዳንድ ቦታዎችም ለሕንፃ ቤተክርስቲያን ማሠሪያነት የሚውል ገንዘብ የሚሰጥ ምዕመን ቁጥር ከማነሱ የተነሳ እያንዳንዱ የአጥቢያው አባል የተወሰነ መጠን ገንዘብ እንዲከፍል ሲጠየቅ ይስተዋላል፡፡ ይህ የገንዘብ መጠን ለሕንፃው ሥራ ከሚያስፈልገው አንጻር ጥቂት መስሎ ቢታይም ወይም አንደንዶች በቀላሉ ሊከፍሉት የሚችሉ ቢሆንም የአካሄዱ አስገዳጅነት ግን ከቤተ ክርስቲያን መሠረታዊ አስተምህሮ ጋር የሚስማማ አይደለም፡፡ ጥቂት ለማይባሉ ምዕመናንም ከባድ ጫናን የሚፈጥርና ያልጸኑትን ከቤተ ክርስቲያን ሊያርቅ የሚችል አካሄድ ስለሆነ ሊታሰብበት ይገባል፡፡

የተዘጉትን፣ የተቸገሩትን፣ እየፈረሱ ያሉትን አብያተ ክርስቲያናትንም እናስብ!

በገጠርና በጠረፋማ አካባቢዎች ያሉት አብያተ ክርስቲያናት ዝናብ እያፈሰሰባቸው፣ ንዋየ ቅድሳቱ ብርድና ፀሐይ እየተፈራረቀባቸው፣ ምዕመናኑ የሚናዝዛቸውና ቀድሶ የሚያቆርባቸው ካህን አጥተው እያለቀሱ በታላላቅ ከተሞች ያሉትን በወርቅና በዕንቁ ማስጌጥ ለቤተ ክርስቲያን መስፋት ምን ያህል ይጠቅማል? ቢያንስ በጥቂቱም ቢሆን ያለ ከባድ ችግር አገልግሎታቸውን እንዲፈጽሙ መደገፍ የሁሉም ኃላፊነት ነው። እነዚያ አብያተ ክርስቲያናት ካህን አጥተው እየተዘጉ፣ ዕጣንና ጧፍ አጥተው ቅዳሴ እየታጎለ፣ አልባሳት አጥተው ካህናት ሲቸገሩ ዝም ብሎ ትኩረትን መንፈግ ከአብያተ ክርስቲያናት አይጠበቅም። ‘ቤተ ክርስቲያን አንዲት’ ናት ስንልም በአንድ ሀሳብና በአንድ ልብ ሆኖ መደጋገፍን ያካትታል።

ይልቁንም ከዕድሜ ብዛትና ከዕድሳት እጦት የተነሳ እየፈረሱ ያሉት ጥንታዊያን አብያተ ክርስቲያናት የበለጠ ትኩረትን ይሻሉ፡፡ እነዚህ ለዛሬዋ ቤተክርስቲያን ቅርስም መዝገብም ናቸው፡፡ ይህንንም ስንል በከተማ ያሉት ታላላቅ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያናትን መሠራት የለባቸውም ማለታችን ሳይሆን በገጠር ላሉት ማሰብንም ገንዘብ ያድርጉት ማለታችን ነው። ምዕመናንን ስለ አሥራት የሚያስተምሩ ለራሳቸው ግን ከገቢያቸው አሥራት የማያወጡ፣ ገቢ ባገኙ ቁጥርም እንደ ስስታም ነጋዴ ሌሎችን እየበደሉ ተጨማሪ ገቢ በመፈለግ የሚደክሙ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ምን ያደርጉልናል?!

በተጨማሪም ከቅርብ ዘመናት ወዲህም ጥቂት በማይባሉ አካባቢዎች በጽንፈኞች አማካኝነት በክርስቲያኖች ላይ ብዙ ግፍና መከራ እየደረሰ፣ ምዕመናን በአሰቃቂ ሁኔታ እየተገደሉ፣ ከፍተኛ የአካል ጉዳት እየደረሰባቸው፣ ንብረታቸው እየተቃጠለና እየተዘረፈ፣ አገልግሎት የሚያገኙባቸው አብያተ ክርስቲያናት እንደ ጧፍ በእሳት እየነደዱ ባሉበት ሁኔታ ከምንም በፊትና በላይ ለዚህ ቅድሚያ ለሰጠው ይገባል። በዚህም አስቸኳይ ድጋፍ ምዕመናንም አብያተ ክርስቲያናትም ዛሬም እንደ ጥንቱ ለቤተ ክርስቲያን ሕልውና በአንድነት ሊቆሙ ይገባል።

የሕንፃ ግንባታ ለልመናና ለሙስና አይዋል!

ምዕመናን ለሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ሥራ በሚያደርጉት አስተዋፅኦ ዋጋ ያገኙበታል። ሱታፌአቸውም እንዲጠናከር ማበርታት ይገባል። ነገር ግን ከቅርብ ዘመን ወዲህ የሕንፃ ሥራ እንደ አንድ የመለመኛ መንገድ እየተወሰደ መጥቷል። በየጉባኤው፣ በየበዓላቱ፣ በየሆቴሉ፣ በየመንገዱ ለሕንፃ ማሠሪያ እየተባለ ሲለመን ማየት የተለመደ ነው። ብዙ የንግድ ሥራዎችም ወደ ቤተ ክርስቲያን የገቡት “ሕንፃ ማሠሪያ” በሚል ምክንያት ነው። ይህ ዓይነቱ አሠራር ግን ቤተ ክርስቲያንን ለብዙ ችግሮች እያጋለጣት ይገኛል። በአንዳንድ ቦታዎች ሕንፃውን ሊያስጨርስ የሚችል ገንዘብ ከተገኘ በኋላም ለመለመኛነት ሲባል የሕንፃውን ሥራ የማጓተት ዝንባሌን አስተውለናል። በሌሎች ስፍራዎች ደግሞ ለሕንፃ ሥራ በሚል ከምእመናን የሚሰበሰበው ገንዘብ ለሙስና እየተጋለጠ መምጣቱ የአደባባይ ምስጢር ነው። ይህንን ችግር ከመሠረቱ የሚቀርፍ አሠራርን መዘርጋት ወሳኝ ነው። ለሕንፃ ሥራው ድጋፍ የሚያደርጉ ምዕመናን ድጋፋቸውን በቀጥታ የሕንፃውን ሥራ ገንዘብ ለሚያስተዳድረው አካል የሚያደርሱበትንና የተፈለገው ሥራ ላይ የሚውልበትን አሠራር መዘርጋት ይገባል።

ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን የክርክር ምክንያት አይሁን!

ሁላችን የምናውቀው ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔር ቤትና ምዕመናን ከፈጣሪያቸው ጋር የሚገናኙባት የጸሎት ቤት መሆኗን ነው። ሕንፃውን “ቤተ ክርስቲያን” የሚያደርገው በውጭ የሚታየው ውበት ሳይሆን በውስጡ የሚገኘው ሕይወት ነው። ያማሩና ለዓይን የሚማርኩ ሕንፃዎችን ሠርተን ውስጣቸው ጥልና ክርክር ከነገሠ ከቶ ምን እናተርፋለን? የራሳቸው ሕንፃ ሳይኖራቸው ወይም በመቃኞ ሲገለገሉ የነበሩ ምዕመናን ሕንፃ ከገነቡ በኋላ የቀደመ ፍቅራቸው ከቀዘቀዘ ትርፉ ምንድን ነው?  በተለይም በውጭው (በዝርወት) ዓለም ባለው የብሔርና የፖለቲካ አሰላለፍ ምክንያት የሚፈጠረው ክፍፍል፣ ንትርክና የፍርድ ቤት ክርክር የሚጀምረው ሕንፃ ከተሠራ በኋላ መሆኑና ማዕከልም የሚያደርገው “ሕንፃው የማን ይሁን?” የሚለው ሆኖ መመልከት ያሳፍራል፣ ያሳቅቃልም።

ትልቁ ጉዳይም የፍቅር መጥፋቱ ሳይሆን የሕንፃው ‘ባለቤትነት’ ሲሆን እያስተዋልን ነው። በልዩነትና በክፍፍል ምክንያት የምዕመናን መንፈሳዊ ሕይወት በእጅጉ መጎዳት ተረስቶ ትኩረቱ ሁሉ ሕንፃ ላይ እየሆነ ነው። በየቦታው የሚከሰቱትን ችግሮች ላስተዋለ ሰው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን የክርክር ማዕከል መሆኑ ያሳዝነዋል። የጸሎት፣ የምስጋናና የሰላም ማዕከል መሆን ያለበት ሕንፃ ‘የባለቤትነት’ ክርክር ሲነሳበት ማየት ክርስቲያናዊ ሕይወታችን ላይ ብዙ መሥራት እንዳለብን ያመለክታል። መንፈሳዊ ሕይወትን በሚገባ ያለማነጽ አንዱ ውጤትም ይኸው ነው።

ታላላቅ የኢትዮጵያ ሕንፃ አብያተ ክርስቲያናትን "ካቴድራል" ብሎ መሰየም አይገባም!

ከላይ እንደተገለፀው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ትውፊት ሕንፃ አብያተ ክርስቲያናት “ቤተ ክርስቲያን፣ ደብር ወይም ገዳም” ተብለው ሊጠሩ ይችላሉ። ይሁንና ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ተለቅ ብሎ የሚታየውን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ‘ካቴድራል’ እያሉ የመጥራት ልማድ መጥቷል። ካቴድራል የሚለውን የላቲን ስያሜ በሀገራችን መጠቀም የተጀመረው በ1924 ዓ.ም ነው። ይህም “ትልቅና በሦስት መንበር የሚቀደስበትንና ብዙ ምዕመናንን ማስተናገድ የሚችል በመሆኑ የተሰጠው ስያሜ ነው” የሚሉ አሉ። ነገር ግን ይህ አስተሳሰብ አስቀድሞ የበቀለ ፈረንጅ አምላኪነት የወለደውን አረም በአመክንዮ ለማቃናት የሚቀርብ መጠገኛ እንጂ ከቀደምት አባቶቻችን የተቀበልነው አይደለም።

አብያተ ክርስቲያናትን ካቴድራል በሚል ቅጽል መጥራት ከአፄ ኃይለስላሴ ዘመነ መንግስት የፈረንጅ ንጉሣውያን ቤተሰቦችን በብዙ መልኩ ለመኮረጅ ከነበረው ልማድ ጋር እንጂ ከኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት ጋር አይስማማም። ለዚህም ማሳያ የሚሆነን “ካቴድራል” የሚለው ስያሜ የመጣበት የታሪክ አጋጣሚ “በኦርጋን መዘመር፣ ያለ ቅዱስ ቁርባን ተክሊል መፈጸም፣ የመናፍቃንን አስተምህሮ የስልጣኔ ማሳያ አድርጎ ማየት” እና የመሳሰሉት የተስተዋለበት ጊዜ ነበር። እነዚህ ከትውፊታችንና ከታሪካችን የሚቃረኑ ልማዶች ሁሉም ሊባል በሚችል ሁኔታ በአመክንዮ ተሞግተው እንዲቀሩ ቢደረግም ለኢትዮጵያዊ አብያተ ክርስቲያናት “የፈረንጅ የዳቦ ስም” የመስጠቱ ልማድ ግን እየጨመረ ሄዷል።

ቀደምት አባቶቻችን ታላላቅ አብያተ ክርስቲያናትን ሲያንፁ “ካቴድራል” የላቲን ቅፅል መስጠት አላስፈለጋቸውም። ከ1920ዎቹ በኋላ፣ በተለይም ባለፉት አምስትና ስድስት ዐስርት ዓመታት ግን ፈረንጅ አምላኪነት በመስፋፋቱ የሚያምር (ተለቅ ያለ) ዛፍ እንኳ ሲገኝ “የፈረንጅ” እያሉ የመጥራት ልማድ አለ። በአብያተ ክርስቲያናት ስያሜ የሚንፀባረቀውም ይህ የቅኝ ተገዥነት አስተሳሰብ ይመስላል። ለዚህም ማሳያ የሚሆነን በየቦታው የምንሰማው “ይህን ቤተ ክርስቲያን አፍርሰን ትልቅ ካቴድራል እንገነባለን” የሚለው አላዋቂ ተናጋሪዎች የሚያደርጉት ንግግር ነው። ቤተ ክርስቲያን የሚለውን ቸርች፣ ደብር የሚለውን ማውንቴን፣ ገዳም የሚለውን ሞናስትሪ እያልን የራሳችንን ጥለን በተውሶ (ያውም አባቶቻችን ካቆዩልን ትውፊት በዘመንም በአመክንዮም በተለየ) ስያሜ መጥራት አሳፋሪ መሆኑን እንደምናውቀው ሁሉ በታሪክ አጋጣሚ የመጣን የፈረንጅ ስያሜ የታላቅነትና የክብር ማሳያ እያስመሰልን ራሳችንንም ታሪካችንንም ማዋረድ አይገባንም፡፡

በኢትዮጵያውያን ፕሮቴስታንቶች ዘንድ በአማርኛ እየተነጋገሩ ቤተ ክርስቲያን ከማለት ‘ቸርች’፣ ጉባኤ ከማለት ‘ኮንፈራንስ’፣ ንስሃ አባት ከማለት ‘ፓስተር’፣ የእግዚአብሔር ሰው ከማለት ‘ማን ኦፍ ጋድ’ ሲሉ የቃላት ምርጫው ጉዳይ አስተሳሰባቸውን በኢትዮጵያዊ ርዕዮት ያለመቃኘት ችግር እንደሆነ መረዳት ይቻላል፤ ከታሪካዊ ሂደታቸው አንፃር አያስገርምም። በኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ግን እንዲህ ዓይነት መርህ አልባ “ፈረንጅ አምላኪነት” ሲታይ ይገርማል፣ ያሳዝናል፡፡ ስለሆነም የሕንፃ አብያተ ክርስቲያናት አሰያየማችን ትውፊታችንና ታሪካችንን የተከተለ መሆን አለበት እንላለን።

የሕንፃ ቤተ ክርስቲያን አጠቃላይ አሠራር ሕግን፣ ሥርዓትንና ትውፊትን የተከተለ ይሁን!

የሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ዲዛይኑ ከውጫዊ ውበት ይልቅ ለቤተ ክርስቲያን አስተምህሮና ትውፊት መገላጫነት ትኩረት የሚሰጥ ሊሆን ይገባዋል፡፡ አሠራሩም ቢሆን በእያንዳንዱ ሂደት በሥራው የሚሳተፉት ሁሉ ለመንፈሳዊ ሕይወታቸው የሚሆን ትምህርትን እየቀሰሙ የሚሄዱበት ሊሆን ይገባዋል፡፡ በተለይም የክርስቲያኖች እምነትና ፍቅር የሚገለጥበት ታላቅ አገልግሎት ሊሆን ይገባል፡፡ ሁሉንም በመተሳሰብ በጸሎት ማከናወን ይጠበቃል፡፡ ሕግን በምታስተምር ቤተ ክርስቲያን ስም ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ለመሥራት ሲታሰብ አካሄዱ ከመጀመሪያው እስከመጨረሻው ሕጋዊ አሠራርንና የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት የተከተለ ሊሆን ይገባዋል።

በሕጋዊ መንገድ የተገኘ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን መሥሪያ ቦታ፣ ሕጋዊ ፈቃድና የቤተ ክርስቲያን ዕውቀት ያለው ባለሙያ የሠራው የሕንፃ ዲዛይን፣ ሥርዓቱን ተከትሎ የወጣ የግንባታ ፈቃድ፣ ሕጋዊ ፈቃድ ያለውና ሙያው የተመሰከረለት የሕንፃ ተቋራጭ፣ በግልፅና ሕጋዊ መንገድ የሚገኝ ሕንፃ ማሠሪያ ገንዘብ፣ ግልፅና ኦዲት የሚደረግ የግዢና የፋይናንስ አሠራር እጅግ አስፈላጊ ናቸው። በተጨማሪም የሚሠራው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያንም መጠኑ፣ ቅርፁ፣ የበሮቹና የመስኮቶቹ አቀማመጥ፣ የጉላቶቹ መስቀል መሆን፣ የስዕላቱ አሳሳልና አቀማመጥ፣ የውጭና የውስጥ ቀለሙ ወዘተ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የተከተለና ለሁሉም አስተማሪ ሊሆን ይገባዋል። በተለይም የቤተ ክርስቲያን መሠረት የሆነው የክርስቶስ መስቀል ከሁሉም በላይ ቀድሞ ሊታይ የሚገባ የቤተ ክርስቲያን መለያ ምልክት ስለሆነ በበሮችዋ፣ በግድግዳዋና በጉላልትዋ ጎልቶ ሊሳል/ሊሠራ ይገባዋል።

በአጠቃላይ የእግዚአብሔር ክብር የሚገለጥበት፣ ስሙ የሚቀደስበትና ምዕመናን ከፈጣሪያቸው ጋር የሚገናኙበት ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የቀደመውን አስተምህሮ፣ ሥርዓትና ትውፊት በጠበቀና የሚሠራበትን ሀገር ሕግ ባከበረ መልኩ ሊታነጽ ይገባል። የሕዝበ ክርስቲያኑም ትኩረት ከሚታየው የሕንፃ ውበት ይልቅ በውስጡ የሚገኘው ሕይወት ላይ፣ ከአካላዊ ግዝፈቱ ይልቅ በውስጡ የሚከናወነው ታላቅ መንፈሳዊ አገልግሎት ላይ ሊሆን ይገባል። ዋናው የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ግን ሕንፃ ሥላሴ የተባሉ የምዕመናንን ሕይወት ማነጽ፣ የክርስቲያኖች ኅብረት/ጉባኤ የሆነችውን ቤተ ክርስቲያንን ማስፋትና ማጽናት ናቸው። እነዚህን የሚሸረሽሩ ከሕንፃ ቤተ ክርስቲያን አሠራርም ይሁን አጠቃቀም ጋር የተያያዙ ልማዶች ተለይተው ሊታረሙ ይገባል እንላለን።

Leave a comment