በየቋንቋው ማ(መ)ገልገል: ሐዋርያዊነትን ከብሔርተኝነት እንለይ!

ምክንያተ ጽሕፈት

በዓለማችን ላይ ብዙ ቋንቋዎች ይነገራሉ። ቅዱስ ወንጌል ለሁሉም ይዳረስ ዘንድ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅዱሳን ሐዋርያትን አሰረ ፍኖት በመከተል ሰዎች በሚናገሯቸው ቋንቋዎች ሁሉ ስታስተምር ኖራለች፣ አሁንም እያስተማረች ትገኛለች። ይህም በሐዋርያት ዘመን መንፈስ ቅዱስ በገለጠላቸው ልሳናት (ቋንቋዎች) የተፈጸመ ሲሆን በዘመናችን ደግሞ የየቋንቋውን ተናጋሪ ካህናትና አገልጋዮችን በማፍራት እንዲሁም ሌሎች አገልጋዮችም ተጨማሪ ቋንቋን ተምረው እንዲያገለግሉ በማድረግ ሊፈጸም ይችላል። ይሁንና በተለያየ ቋንቋ የማስተማር ነገር በሰፊው ሊሠራበት የሚገባ ሆኖ ሳለ አንዳንድ ወገኖች ይህ አካሄድ “ብሔርተኝነትን በማስፋት ቤተ ክርስቲያንን ይከፋፍላል” የሚል ስጋት አላቸው።

በሌላም በኩል ቤተ ክርስቲያን በአንድ ቋንቋ አገልግሎት መስጠቷ “የሌላ ብሔርን ባሕል በማስፋፋት የባሕል ወረራ እያደረሰችብን ነው” የሚሉ ወገኖች አሉ። ለእነዚህ የተቃረኑ አመለካከቶች ምንጭ ከሆኑት ነገሮች ዋነኞቹ ብሔርና ብሔርተኝነት በሚባሉት አስተሳሰቦች ላይ ያለ አለመግባባትና የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ለፖለቲካዊ ዓላማ ለማስገዛት የሚደረግ እሽቅድምድም ናቸው ብለን እናምናለን። ስለሆነም እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ለቤተ ክርስቲያን የየብሔሩን (የየሀገሩን) ቋንቋ በጸጋ የገለጠበትን በዓለ ጰራቅሊጦስን በምናከብርበት ሳምንት፣ በዚህች የአስተምህሮ ጽሑፍ በየብሔሩ ቋንቋ ማስተማር/ማገልገልና ብሔርተኝነት ያላቸውን ልዩነት እንዳስሳለን።

‘ብሔር’ ምንድን ነው?

‘ብሔር’ የሚለው ቃል ‘ዓለም’ የሚለውን ትርጉም ሊይዝ ይችላል። ይህም እግዚአ-ብሔር የሚለው ቃል ‘የዓለም ጌታ’ ተብሎ በመተርጎሙ ይታወቃል። ‘ብሔረ ሕያዋን’ እና ‘ብሔረ ብፁዓን’ በመባል የሚታወቁት የስውራን ቅዱሳን መኖሪያ የሆኑት የዓለመ መሬት ክፍሎች ስያሜም ይህንኑ የሚያስረዳ ነው። ብሔር ‘ሀገር’ ተብሎ ሊተረጎምም ይችላል። ‘አይቴ ብሔራ ለጥበብ’ የሚለውን ‘የጥበብ ሀገሯ ወዴት ነው?’ እንዲል። እንዲሁም የራሱ የሆነ ቋንቋ፣ ባሕል፣ የሕዝብ አሰፋፈርና ሌሎች ማኅበራዊ እሴቶች ያለው ወገን/ማኅበረሰብ ‘ብሔር (Ethnic group)’ ይባላል። ከኖኅ ልጆች ጀምሮ፣ በባቢሎን ቋንቋ መደበላለቁን ይዞ፣ አሥራ ሁለቱን ነገደ እሥራኤል ጨምሮ፣ መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት ብዙ ልሳናትን መግለጡን ስንገነዘብ የብሔር ምንነትና ልዩነት መኖሩን ማንም ሊክደው የማይችልና በምድር ላይ የሚታይ ሐቅ መሆኑን እንረዳለን።

ብሔር የሚለው ቃል ለአንዳንዱ ሀገር ማለት ሲሆን፣ ለሌላው በቋንቋና በባሕል የተሳሰረ በአንድ ወይም ከዚያ በላይ ሀገራት ውስጥ የሚኖር (የግድ ራሱን የቻለ ፖለቲካዊ ድንበር ሊኖረው ይገባል የማይባል) የኅብረተሰብ ክፍል ማለት ነው። ብሔር ከሀገር ጋር የሚመሳሰልባቸው ሀገራት ያሉትን ያህል በሀገራት ውስጥ የየራሳቸው (ተወራራሽ) ባሕል፣ ቋንቋና ልዩ ልዩ ማኅበረሰባዊ አንድነቶች ያሏቸው ሕዝቦች በብዙ ሀገራት አሉ። “ብሔር የፖለቲካ ድንበርን መወሰን አለበት ወይስ የለበትም?” በሚለው ሀሳብ ላይ ፖለቲካዊና ርዕዮተ ዓለማዊ ልዩነት እንዳለ ይታወቃል። ይሁንና በቋንቋና በባሕል የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች በየሀገራቱ አሉ። እነዚህ ብሔሮችም የሚያመሳስሏቸው መገለጫዎች እንዳሏቸው ሁሉ፣ የሚለያዩአቸው መገለጫዎችም አሉ።

ከዚህም የተነሳ ለየራሳቸው መጠሪያና መገለጫ ያላቸው፣ በዘመናት ሂደት የዳበረ ተመሳሳይ ቋንቋና ባሕል የሚያንፀባርቁ የማኅበረሰብ ክፍሎች “ብሔር” ሊባሉ ይችላሉ፣ በተግባርም ይባላሉ። ብሔር የሰዎች ስብስብ እንደመሆኑ “ብሔር” የሚለውን ቃል “ብሔረሰብ” ከሚለው ተመሳሳይ ቃል ጋር በተለዋጭነት እንጠቀማለን። አንድ ክርስቲያን በቤተ ክርስቲያን ትምህርተ ወንጌልን እየተማረ እንደሚያድገው ሁሉ በማኅበረሰቡ ውስጥም ቋንቋን ባሕልንና የተለያዩ የማኅበረሰቡ መገለጫ የሚሆኑ እሴቶችን እየተማረ ያድጋል፡፡ በዚህም ሰው ካደገበት ማኅበረሰብ ወይም ከትውልድ ሐረጉ የተነሳ የራሱ ‘ብሔር (ባሕልና ቋንቋ) ይኖረዋል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስም ብዙ የብሔር ስም ተጠቅሷል። ክርስቲያንም እንዲሁ የማኅበረሰቡ አካል ስለሆነ የራሱ ‘ብሔር’ ይኖረዋል፡፡ 

ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊት ናት!

ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊት ናት፡፡ ይህም ማለት “በሐዋርያትና በነቢያት መሠረትነት ላይ ታንጻችኋል (ኤፌ 2:20)” እንደተባለ የሐዋርያትን አስተምህሮና ትውፊት የምትከተል፣ ሐዋርያት ባስተማሩበት መንገድ በተለያየ ቋንቋ ወንጌልን የምትሰብክ፣ ከሐዋርያት ቀጥታ የመጣ የሢመት ሐረግ ያላት ናት ማለት ነው፡፡ አገልጋዮችም እንዲሁ አገልግሎትን የሚፈጽሙት የሐዋርያትን ፈለግ ተከትለው ስለሆነ አገልግሎታቸው ሐዋርያዊ አገልግሎት ይባላል፡፡ ሐዋርያዊነት የምንለውም ለዚህ ዓላማ መታመንንና መቆምን ነው፡፡ የሐዋርያነት ዋናው ተግባርም ለሁሉም ሰው በሚናገረው ቋንቋ የክርስቶስ ወንጌልን መስበክ ነው፡፡

በማኅበራዊና በመደበኛ መገናኛ ብዙኃን በየብሔረሰቡ ቋንቋ ማስተማር እንዳለ ሆኖ በየአካባቢው የሚተከሉ አብያተ ክርስቲያናትም ሆኑ ሌሎች የቤተ ክርስቲያን ተቋማት የየአካባቢውን ማኅበረሰብ ቋንቋ የሚጠቀሙና የየማኅበረሰቡን የአኗኗር ባህል የዋጁ ሊሆኑ ይገባል፡፡ ይህ ማለት ግን በቤተ ክርስቲያን ወንጌል በሕዝቡ ቋንቋ ይሰበክ ማለት ነው እንጂ በቋንቋ በመ(ማ)ግልገል ሽፋን ከወንጌል ይልቅ ብሔርተኝነት ይሰበክ ማለት አይደለም፡፡ የተለያየ የብሔረሰብ ስብጥር ባለባቸው አካባቢዎችም አብዛኛው ማኅበረሰብ በሚረዳው ቋንቋ እያገለገሉ ቋንቋውን ለማይናገሩ ሰዎች ደግሞ የተለየ መርኃግብር ማዘጋጀት ይገባል፡፡ ከዚህ ውጭ ቤተ ክርስቲያን በአንድ ቋንቋ ብቻ አገልግሎት ትስጥ የሚል በሀሳብም ሆነ በተግባር የሚገለጥ አስተሳሰብ የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት በእጅጉ የሚገድብ ነው፡፡ አንዳንዶች ይህን አስተሳሰብ መያዛቸውን ሳያውቁ፣ ሌሎች ደግሞ በፖለቲካዊ ዓላማ የቤተ ክርስቲያንን በየቋንቋው የማስተማር ተልዕኮ ይቃወማሉ ወይም ለሚፈልጉት ፖለቲካዊ ዓላማ ግብዓት በሚሆን መልኩ “ከአንድ ቦታ እየተቆረሰ የሚሰጥ ምጽዋት” ያስመስሉታል።

ቤተ ክርስቲያን በየማኅበረሰቡ ቋንቋ ልታስተምር ይገባል ሲባል በመዋቅር፣ በመመሪያ እና በዕቅድ በተደገፈና ወጥነት ባለው መልኩ እንጂ አንዳንድ ጊዜ እንደምናየው የተወሰኑ ሰባክያን በሚዲያ ብቅ እያሉ በተለያየ ቋንቋ ስለሰበኩ ብቻ ወይም የተወሰኑ መምህራን አንዳንድ መጻሕፍትን በተለያየ ቋንቋ ስላሳተሙ ብቻ ቤተ ክርስቲያን በተሟላ ተቋማዊ አቅም ምዕመናንን በየቋንቋቸው እያስተማረች ነው ለማለት አያስደፍርም፡፡ ዓለማዊ መንግሥታት እንኳን ሕዝቡ ራሱን በራሱ እንዲያስተዳድርና በየቋንቋዉ አገልግሎት እንዲያገኝ ባደረጉበት በዚህ ወቅት ቤተ ክርስቲያን ምዕመናንን በቋንቋቸው ለማገልገል ሳትችል ስትቀር ማየት አሳዛኝ ነው፡፡ ይህ የሆነው የተለያየውን ቋንቋ የሚናገር አገልጋይ ጠፍቶ ሳይሆን በአስተዳደር ብልሽትና በዘረኝነት መሆኑ ሲታሰብ ደግሞ ገና ብዙ መሥራት እንደሚቀረን ያመለክታል፡፡ ከዚህም አልፎ በአንድ ቋንቋ መገልገልን (ማገልገልን) የመንፈሳዊ አንድነት ማሳያ በማስመሰል ምድራዊ ፍላጎታቸውን በሌሎች ላይ ለመጫን የሚሯሯጡትን ማየትም ያሳፍራል።  

የቋንቋ መለያየት ቤተ ክርስቲያንን የሚከፋፍላት አድርጎ ማሰብም ትልቅ ስህተት ነው፡፡ ይልቁንስ ቤተ ክርስቲያንን የሚከፋፍላት አንድ ቋንቋ ብቻ ለመጠቀም መሞከር ነው፡፡ አንድ ዓይነት ምድራዊ አስተሳሰብና ቋንቋ በቤተ ክርስቲያንን የበላይ ለመሆን ሲሞክር፣ ሌላው ደግሞ ‘በሥርዓት እንመራ’ በማለቱ ሲገለል ቤተ ክርስቲያን የሁሉም መሆኗ ይዘነጋና መከፋፈል ይፈጠራል፡፡ በተለይም የብሔር ብዙኅነት ባለበት ሀገር ሁሉም በቋንቋው መገልገል ይፈልጋል፣ ይገባዋልም፡፡ ምዕመናን በቋንቋቸው መገልገል እየፈለጉ ይህንን የማይፈጽም አስተዳደር ሲኖር ምዕመናን በቤተ ክርስቲያን ባይተዋርነት እንዲሰማቸው ያደርጋል፣ ያልጸኑትም እየተው ይሄዳሉ፡፡ ምክንያቱም አገልግሎቱ ለእነርሱ ተደራሽ አይደለምና፡፡

በአንድ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ከአንድ ቋንቋ በላይ ለመንፈሳዊ አገልግሎት መጠቀም የሚያመጣው ችግር የለም፡፡ በተለያዩ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት በተለያየ ቋንቋ ማገልገልም እንዲሁ የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ተደራሽነት ያሰፋዋል እንጂ ቤተ ክርስቲያንን አይከፋፍልም፡፡ ለምሳሌ በግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በአንድ አጥቢያ በሁለት መቅደስ በተለያየ ቋንቋ ይቀደሳል፡፡ በሁለት አጥቢያም በአንድ ጊዜ በተለያየ ቋንቋ ይቀደሳል፡፡ ምዕመናንም የተሻለ በሚሰሙት ቋንቋ የሚቀደሰው ጋር ሄደው ያስቀድሳሉ፡፡ ስብከተ ወንጌልና ሰንበት ትምህርት ቤትም እንዲሁ ነው። ይህ ቤተ ክርስቲያኗን አጠናክራት እንጂ አልከፋፈላትም፡፡ በሌሎችም አኃት አብያተ ክርስቲያናት ያለው አሠራር ተመሳሳይ ነው፡፡ ይህ ሐዋርያዊነት በእኛም አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ሊለመድ ይገባዋል፡፡

ብሔርተኝነት ፖለቲካዊ ርዕዮት ነው!

‘ብሔርተኝነት (nationalism)’ በቀጥታ ትርጉሙ ለአንድ ሀገር/ብሔር መብት መከበር መታገል፣ ለብሔር/ለዜጎች እኩልነትንና ራስን በራስ ለማስተዳደር ይችሉ ዘንድ (የሉዓላዊ ስልጣን ባለቤት እንዲሆኑ) የብሔረሰቡን አባላት በማደራጀት አብሮ መሥራት ነው። በዚህ ትርጉሙም ለብሔረሰቡ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ብልፅግና መቆምን ያመለክታል። ብሔርተኝነት በተለይም አንድ ሀገር/ብሔር ተፈጥሮአዊና ሰው ሠራሽ ችግሮች ሲጋረጡበት ተደራጅቶ ችግሮችን የሚፈታበትና በቀጣይም ተጠቃሚነቱን የሚያረጋግጥበት ፖለቲካዊ ርዕዮተ ዓለም (Political ideology) ነው። በጥቅሉ ብሔርተኝነት ለአንድ ብሔር/ሀገር በታማኝነት መቆምን ያመለክታል፣ አጠቃላይ ዓላማውም ምድራዊ ነው።

ከፖለቲካ ሳይንስ አንጻር ሁለት አይነት ብሔርተኝነት አለ ማለት ይቻላል። እነዚህም ሀገርን፣ ዜግነትን ወይም ሕገ መንግስትን መሠረት ያደረገ “ሀገራዊ ብሔርተኝነት” (Civic nationalism) እና ቋንቋን፣ ባሕልን እና የሕዝብ አሠፋፈርን መሠረት ያደረገ “ብሔር-ተኮር ብሔርተኝነት” (Ethnic nationalism) ናቸው። ምንም እንኳ “ከዶሮና ከእንቁላል ማን ይቀድማል?” እንደሚለው ውል አልባ አመለካከት ለመበየን የሚያስቸግር ቢሆንም በግርድፉ ስንመለከተው የመጀመሪያው ሀገርን የሚያስቀድም ሲሆን ሁለተኛው ብሔርን የሚያስቀድም ነው ሊባል ይችላል። የብሔርተኝነትንም ሆነ ሌላ ዓይነት ርዕዮተ ዓለም ጥቅሙንና ጉዳቱን አመዛዝኖና ተንትኖ ለመከተል ወይም ላለመከተል መወሰን የፖለቲካ መሪዎችና የሚመሩት ማኅበረሰብ ድርሻ ነው፡፡

በመሠረታዊ አስተሳሰቡ ብሔርተኝነት ከብዙ ፖለቲካዊ ርዕዮቶች አንዱ ነው። በቅርብ ጊዜ የጽሁፍ ታሪክ ምንጭነት ከተመለከትነው ብሔርተኝነት እንደ ፖለቲካዊ ርዕዮት የተጀመረው በአውሮፓ ሲሆን ኋላ ወደ አፍሪካና ኤስያ ሀገራት ተሰራጭቷል። ማንኛውም ፖለቲካዊ ርዕዮተ ዓለም የራሱ በጎና ደካማ ጎኖች እንዳለው ሁሉ ብሔርተኝነትም የራሱ የሆኑ በጎና ደካማ ጎኖች አሉት። በተለይም በአንድ ብሔርና በሌላው መካከል ለባህል፣ ለስልጣን ወይም ለሀብት ፉክክር ባለበት ሀገር የአንዱ ብሔር መጠናከር በሌላው ዘንድ በመልካም ላይታይ ይችላል። በተጨማሪም አንዱ የራሱን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በሚያደርገው ጥረት ሌላውን ሊጎዳ ይችላል። በዚህም የተነሳ ግጭቶች ሊፈጠሩ ይችላሉ።

ክርስትና ምድራዊ ‘ብሔር’ የለውም፣ ራሱን የቻለ ምድራዊ ‘ብሔርም’ አይደለም። ቤተ ክርስቲያንም ለሁሉም ብሔረሰብ በእኩልነት መንፈሳዊ አገልግሎት የምትሰጥ መንፈሳዊት ተቋም ናት፡፡ ከዚህም የተነሳ የክርስትና አስተምህሮ ሁለቱንም የብሔርተኝነትን ርዕዮቶች እንደ ማንኛውም ፖለቲካዊ ርዕዮተ ዓለም ሊመለከታቸው ይገባል። የክርስትና አስተምህሮ መሠረታዊ ዓላማው መንፈሳዊ/ሰማያዊ ስለሆነ አንዱን ፖለቲካዊ ርዕዮተ ዓለም የሚደግፍበት ሌላውን ደግሞ የሚቃወምበት አግባብ የለም። ይህ የመንግስት አስተዳደር እና የሚመሩት ሕዝብ ምርጫ እንጂ የቤተ ክርስቲያን ኃላፊነት አይደለምና። ይሁንና በማንኛውም ርዕዮተ ዓለም ተፈጥሮአዊ ጠባይም ይሁን በአፈፃፀም ችግር ምክንያት በሰው ልጆች ላይ በደል ሲደርስ ቤተ ክርስቲያን በደልን በቸልታ ማለፍ የለባትም። የዚህም ዋና ዓላማው የመንግሥትን ሥርዓት (ርዕዮተ ዓለም) ለማስቀየር ሳይሆን በሰው ልጆች ላይ የሚደርሰው ችግር እንዲቆምና የተበደለው እንዲካስ መሆኑ ሊሰመርበት ይገባል።

‘ኦርቶዶክሳዊ ብሔርተኝነት’

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አንዳንድ ግለሰቦችና ቡድኖች በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ የሚደርሰውን ፈተና እንደ ምክንያት በመጠቀም “ኦርቶዶክሳዊ ብሔርተኝነት” የሚል ሀሳብን ሲያነሱ አስተውለናል። በመሠረታዊ ባሕርይው ብሔርተኝነት ፖለቲካዊ ርዕዮት እንደሆነ ከላይ ተመልክተናል። ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ እምነት ደግሞ ሰማያዊት ስለሆነች ምድራዊ የሆነው ፖለቲካዊ ፍልስፍና ሊደረትባት አይገባም። በአጭር አገላለጽ ፖለቲካዊ ርዕዮት ለክርስትና አይስማማም። የብሔርተኝነት ግብ የአንድ ‘ብሔርን’ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ መብቶችን በማረጋገጥ ራሱን ሉዓላዊ የሥልጣን ባለቤት ማድረግ ነው። ይህ ደግሞ በግልጽ በብሔር የተደራጀ የፖለቲካ ፓርቲ ዓላማ ነው። ከዚህ አንፃር የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምዕመናንን በብሔርተኝነት አስተሳሰብ ለማንቀሳቀስ ማሰብም በሃይማኖት ካባ ፖለቲካን ማራመድ ነው፡፡

የኦርቶዶክሳዊ ብሔርተኝነት ዋናው መነሻ ሀሳቡ የቤተ ክርስቲያንን መብት ለማስከብር ከሆነ የሀገሪቷን ሕግ በመጠቀም ማስከበር ይገባል። ይህ የማያሰራ ከሆነ በጠራ አስተሳሰብ በግልም ይሁን በቡድን ለሁሉም ሰው ፍትህን ሊሰጥ የሚችል ፖለቲካዊ ፕሮግራም ያለው ፓርቲን በመፍጠር፣ በመደገፍ፣ ገብቶ በመሳተፍ መምረጥና/መመረጥ ይገባል እንጂ ቤተ ክርስቲያንን ተጠግቶ ፖለቲካዊ ርዕዮትን መጎተት ቤተ ክርስቲያንን ይጎዳታል፣ አንዳችም አይጠቅማትም። ስንዱ እመቤት የሆነችው ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንስ ምን ጎድሎባት ነው የብሔርተኝነት ፖለቲካዊ ፍልስፍናን የምትዋሰው? በምድራዊ የብሔርተኝነት ቁርቁስ በጥላቻ ተሞልተው፣ ብሔር ተኮር ፖለቲካዊ ቅስቀሳና ቀረርቶ በማቅረብ የሚታወቁ ሰዎች ሳይቀሩ እንደ “ባጣ ቆየኝ” ስሌት ቤተ ክርስቲያን የእነርሱን “ገዥ ያጣ ፖለቲካዊ ሸቀጥ” እንድትሸከም የሚፈልጉት አዝነውላት ሳይሆን ቤተ ክርስቲያንን ተጠግተው “ጠላት” ያሉትን ለመውጋት ነው። ይህ ደግሞ ሌላ በደል ነው።

ሐዋርያዊነት በብሔር አይወሰንም!

የክርስቶስ አካል የሆነችው ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምድራዊ ብሔር የላትም። እግዚአብሔር የዓለም ሁሉ ጌታ ስለሆነ የእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያንም ዓለም ዓቀፋዊትና የሁሉም ናት። በአገልግሎት ውስንነት ምክንያት በሁሉም ብሔረሰብ ዘንድ ቤተ ክርስቲያን ባትስፋፋ እንኳን ቤተ ክርስቲያን የብሔር ወሰን የላትም፣ በፖለቲካዊ አስተሳሰብም ሆነ በታሪክ ትንታኔ ልዩነት አትገደብም፡፡ ዶግማዋ፣ ሥርዓቷና አስተምህሮዋ መልክአ ምድራዊም ሆነ ማኅበራዊ ድንበር የለውም። ይህን መንፈሳዊ የአስተሳሰብ ልዕልና የሚያጠፉና ቤተ ክርስቲያንን የሚያስነቅፉትን አሰራሮችና ልማዶችን ለይቶ አውቆ ማረም ያስፈልጋል። ከእነዚህም ውስጥ በተወሰነ ቋንቋ ብቻ መጠቀም፣ ካህናትን ከተወሰኑ ብሔሮች ብቻ በብዛት ማፍራት፣ የተወሰኑ ብሔሮችን ባሕላዊ፣ ታሪካዊ፣ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ መገለጫዎች ብቻ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ማዘውተርና የቤተ ክርስቲያን እንደሆኑ አድርጎ ማቅረብ ቤተ ክርስቲያንን የተወሰነ ብሔር/ወገን የሆነች ሊያስመስሏት ይችላሉ።

ከውጭም ቢሆን አንዳንድ አካላት በሚያራምዱት ጽንፍ የረገጠ የብሔርተኝነት ፖለቲካ የቀድሞ ነገሥታት ወይም የቀድሞ ሥርዓቶች የፈጸሙትን ስህተት ለቤተ ክርስቲያን በመስጠት ቤተ ክርስቲያንን “የዚህ ወገን መገልገያ መሣርያ ናት” ብለው የፖለቲካ ነጥብ ሊያስቆጥሩ ይሞክራሉ። ይህ ፍጹም ስህተትና መታረም የሚያስፈልገው ነው። በተመሳሳይም ቀድሞ የነበሩት ክርስቲያን ነገሥታት የሠሩትን መልካም ነገር ሁሉ የቤተ ክርስቲያን አድርጎ ማቅረብ ቤተ ክርስቲያንን የነገሥታቱ ብቻ፣ ነገሥታቱም የቤተ ክርስቲያን ብቻ የነበሩ ያስመስልና ቤተ ክርስቲያን የተወሰነ ወገን ብቻ የነበረች ያስመስላታል። መታወቅ ያለበት እውነት ምንም እንኳን በጥንት ዘመን ቤተ ክህነትና ቤተ መንግሥት የተቆራኙ የነበሩ ቢሆንም የነገሥታቱ አገዛዝና የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ግን በመሰረተ ሀሳብ የተለያየ የነበረ መሆኑ ነው። ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን ነገሥታቱ ለሠሩት መልካም ነገር ሁሉ የምትወደስበት፣ ለበደሉት በደል የምትወቀስበት ሁኔታ መጤን ይኖርበታል። 

የሐዋርያዊነት ዓላማ ተስፋ መንግስተ ሰማያት ናት!

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “እኛስ ሀገራችን በሰማይ ያለችው ናት” (ፊልጵ 3:20) እንዳለው የእኛ ክርስቲያኖች ሀገራችን በሰማይ ነው። “ሀገራችን በሰማይ ነው” ማለት ከቁሳዊ እይታ፣ ከምድራዊ ደስታ በላይ የምንታመንለት እምነት፣ ከምንም በላይ ተስፋ የምናደርጋት መንግስተ ሰማያት አለችን ማለት እንጂ በምድር ኑሯችን ማኅበረሰባዊ ልዩነቶች የሉንም ማለት አይደለም። በተጨማሪም የተወደደ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ “አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና (ገላ 3:28)” ሲል ለገላቲያ ክርስቲያኖች የጻፈው በተለያዩ ማኅበራዊ ልዩነቶች የተነሳ እንዳይከፋፈሉ ነበር። ይህ ቃል ዛሬም ሕያው ነው።  ይህች ምድር በእንግድነት የምንቆይባት፣ ነገር ግን ለማያልፈው ሕይወታችን ቁም ነገር ሠርተን የምናልፍባት ሥፍራ ናት። ሀገራችን በሰማይ፣ አምላካችንም እግዚአብሔር፣ አንድነታችንም ከቅዱሳን ጋር ነው (ፊልጵ 3:20)።

በምድር ላይ ስንኖር ከማንኛውም ብሔር ጋር ብንመደብ፣ የትኛውንም ቋንቋ ብንናገር የመጨረሻው ዓላማችን በእምነታችን ጸንተን መንግስተ ሰማያትን መውረስ ነው። መጽሐፍ በግልፅ ከሁሉም ነገድ ወደ መንግስተ ሰማያት መግባት እንደሚችል ይነግረናል። ይህም ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ በራዕዩ (ራእይ 7:9-10) “ከዚህ በኋላ አየሁ፥ እነሆም፥ አንድ እንኳ ሊቆጥራቸው የማይችል ከሕዝብና ከነገድ ከወገንም ከቋንቋም ሁሉ እጅግ ብዙ ሰዎች ነበሩ፤ ነጭ ልብስም ለብሰው የዘንባባንም ዝንጣፊዎች በእጆቻቸው ይዘው በዙፋኑና በበጉ ፊት ቆሙ፤ በታላቅም ድምፅ እየጮሁ፡- በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለአምላካችንና ለበጉ ማዳን ነው፡ አሉ” በማለት ገልጾታል። በምድር ላይ ስንኖርም “ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ (ሮሜ 12:18)” እንደተባልን በሥላሴ አምሳል ከተፈጠረ ሰው ጋር ሁሉ በሰላም ልንኖር ይገባናል። የቋንቋና የባህል ልዩነትም ክርስትናችንን ሳይከፋፍለው ሁሉም በቋንቋው እየተማረና እየተገለገለ ለመንግስተ እግዚአብሔር ልንበቃ ያስፈልጋል።

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s