በሥራ መትጋት: ሊሠራ የማይወድ አይብላ!

መጽሐፍ ቅዱስ ገና ሲጀምር “በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ፈጠረ (ዘፍ 1:1)” በማለት የእግዚአብሔርን ሥራ ይናገራል። በዕቅዱ መሠረት ለስድስት ቀናት ከፈጠረ በኋላ  “እግዚአብሔርም የሠራውን ሥራ በሰባተኛው ቀን ፈጸመ፤ በሰባተኛውም ቀን ከሠራው ሥራ ሁሉ ዐረፈ (ዘፍ 2:2)” እንደተባለ ሥራውን ሲፈጽም ዐርፏል። ጌታችንም “አባቴ እስከ ዛሬ ይሠራል እኔም ደግሞ እሠራለሁ (ዮሐ 5:16)” ብሎ እንዳስተማረን እግዚአብሔር ድንቅ ነገርን ሲሠራ ይኖራል። በሥራ አንቀፅ የጀመረው መጽሐፍ ቅዱስ “እነሆ፥ በቶሎ እመጣለሁ፥ ለእያንዳንዱም እንደ ሥራው መጠን እከፍል ዘንድ ዋጋዬ ከእኔ ጋር አለ (ራዕ 22:12)” በማለት በመጨረሻው ቀን እግዚአብሔር ለሁሉም እንደ ሥራው ሊሰጠው እንደሚመጣ አበክሮ በመግለጽ መልእክቱን ያጠቃላል። ይሁንና በአንዳንድ ኦርቶዶክሳዊያን ዘንድ ለሥራ ያለው አመላካከት ከቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ጋር የማይስማማና ወገኖቻችንንም ለድህነት የሚዳርግ ነው፡፡ በዚህች የአስተምህሮ ጽሑፍ ሥራን የሚመለከተውን አስተምህሮ ቅዱሳት መጻሕፍትን ዋቢ በማድረግ እንዳስሳለን፡፡

ሰው የተፈጠረው ለሥራ ነው!

የሰው ልጅ ከተፈጠረበት ዓላማ ዋነኛው ሥራን ለመሥራት ነው። እግዚአብሔር አምላክ ሰውን ከፈጠረ በኋላ “እግዚአብሔርም ባረካቸው፥ እንዲህም አላቸው። ብዙ፥ ተባዙ፥ ምድርንም ሙሉአት፥ ግዙአትም፤ የባሕርን ዓሦችና የሰማይን ወፎች በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ግዙአቸው (ዘፍ 1:28)” ብሎ እንዳዘዘው የሰው ልጅ ለሥራ ነው የተፈጠረው። በዓለም የተፈጠረውን ሁሉ መግዛት (ማስተዳደር)  ለሰው ልጅ የተሰጠው የሥራ ድርሻ ነበር፡፡ እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከፈጠረው በኋላ ወስዶ ያበጃትም ይጠብቃትም ዘንድ በዔደን ገነት ያኖረውም (ዘፍ 2:15) ለሥራ መሆኑን ማስተዋል ይገባል። የሰው ልጅ ዕፀ በለስን በልቶ ከተሳሳተ በኋላ ግን ሥራ እንዲከብድበት ሆኗል። “አዳምንም አለው። የሚስትህን ቃል ሰምተሃልና፥ ከእርሱ እንዳትበላ ካዘዝሁህ ዛፍም በልተሃልና ምድር ከአንተ የተነሣ የተረገመች ትሁን፤ በሕይወት ዘመንህም ሁሉ በድካም ከእርስዋ ትበላለህእሾህንና አሜከላን ታበቅልብሃለች፤ የምድርንም ቡቃያ ትበላለህ።ወደ ወጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራን ትበላለህ፤ አፈር ነህና፥ ወደ አፈርም ትመለሳለህና (ዘፍ 3:17-19)” እንደተባለ በሥራ ደክሞ የላቡን ዋጋ እንዲበላ ተፈርዶበታል። በክርስቶስ ቤዛነት ወደ ቀደመው ክብሩ ቢመለስም በምድር ላይ እስካለ ድረስ ግን እየሠራ ይኖራል።

ሥራ የእግዚአብሔር ትዕዛዝ ነው!

ሥራን መሥራት እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ከሰጣቸው ትዕዛዛት መካከል አንዱ ነው። “ስድስት ቀን ሥራ ተግባርህንም ሁሉ አድርግ፤ ስድስት ቀን ትሠራለህ፥ በሰባተኛውም ቀን ታርፋለህ፤ በምታርስበትና በምታጭድበት ዘመን ታርፋለህ (ዘፍ 20:9 34:21)” እንዳለው የሰው ልጅ ስድስቱን ቀን ሠርቶ በሰባተኛው ቀን ሰንበትን ሊያከብር ይገባል። “ሰንበትን አክብር” የሚለውም ሰው በሰንበት ቀን በተለየ ሁኔታ ምስጋናን እንዲያቀርብና ትሩፋትን እንዲሰራባት እንጂ ተቀምጦ ወይም ተኝቶ እንዲውል አለመሆኑን ልብ ማለት ይገባል። የበዓል ቀናትም እንዲሁ መንፈሳዊ ሥራ የሚከናወንባቸው ናቸው፡፡ የበዓል ቀናት ማኅሌት፣ ኪዳን፣ ቅዳሴና የመሳሰሉት መንፈሳዊ አገልግሎቶች የሚከናወኑባቸው፣ እኛም ምስጋናን የምናቀርብበት፣ ወገኖቻችንን የምንጎበኝባቸው (የምናስብባቸው) እንጂ ሳንሠራ የምንውልባቸው የዕረፍት ቀናት አይደሉም፡፡

ይህንን የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ በማክበር በገዳም ያሉ አባቶችና እናቶች ከጸሎት ሰዓት በስተቀር ሙሉ ጊዜያቸውን በሥራ ተጠምደው ያሳልፋሉ፡፡ ይህም ትጋታቸው ገዳማቸውን ከመጥቀሙ ባሻገር የመንፈሳዊ ትጋታቸው አንዱ አካል መሆኑን የቅዱሳን ገድላትና በዘመናችን የምናውቃቸው ደገኛ ገዳማውያን ተጋድሎ ይመሰክራሉ፡፡ በገጠሪቱ የሀገራችን ክፍል ያሉ ካህናትም እንዲሁ የቤተ መቅደሱን አገልግሎት ከሚፈጽሙበት ሰዓት ውጭ ያለውን ጊዜ የግብርና ሥራቸውን በመሥራት ይተጋሉ፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ትጋት አንዳንድ በከተማዎች ለሚኖሩ ካህናትና አገልጋዮችም ትምህርት ሊሆናቸው ይገባል፡፡ ልበ አምላክ የተባለ ንጉስ ዳዊት “የድካምህንም ፍሬ ትመገባለህ፤ ምስጉን ነህ መልካምም ይሆንልሃል (መዝ 128:2)” እንዳለው ሁሉም መልካም እንዲሆንልን በሥራ ልንተጋ ይገባናል፡፡ በከተማና በውጭ ሀገራት ባሉ አጥቢያዎች መንፈሳዊ አገልግሎት ቁሳዊ ከሆነባቸው፣ አብያተ ክርስቲያናትም የግለሰቦችና የቡድኖች መነታረኪያ ከሆኑባቸው ምክንያቶች አንዱ ከስራ ይልቅ በአሉባልታ ጊዜያቸውን የሚያሳልፉ ምንደኛ ሰዎች አገልግሎትን እንደ ተራ ስራ መያዛቸውና በጥቅም መነፅር መመልከታቸው መሆኑን መታዘብ ይቻላል።

ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ክርስቲያኖች በጻፈው መልእክቱ “ደግሞ ከእናንተ ጋር ሳለን:- ሊሠራ የማይወድ አይብላ ብለን አዘናችሁ ነበርና:- ሥራ ከቶ ሳይሠሩ፥ በሰው ነገር እየገቡ፥ ያለ ሥርዓት ከእናንተ ዘንድ ስለሚሄዱ ስለ አንዳንዶች ሰምተናልና (ተሰሎ 3:10)” በማለት ሥራን የማይወዱትንና በማያገባቸው ነገር የሚገቡትን ገስጿቸዋል፡፡ ‘ሊሠራ የማይወድ አይብላ’ የሚል ታላቅ ትዕዛዝንም አስተላልፎ ነበር፡፡ ሰው የተፈጠረው ለመሥራት ነውና ሊሠራ የማይወድ ሰው አይብላ አለ፡፡ ሰው ሠርቶ የላቡን ዋጋ እንዲበላ ተፈርዶበታልና ሊሠራ የማይወድ አይብላ ማለቱም ለዚህ ነው፡፡ ነገር ግን ሐዋርያው የሰጣቸው ትዕዛዝ ‘የማይሠራ አይብላ’ ሳይሆን ‘ሊሠራ የማይወድ አይብላ’ ነው፡፡ ምክንያቱም ሰዎች መሥራት እየፈለጉ ነገር ግን መሥራት የማይችሉባቸው የተለያዩ ሁኔታዎች አሉና ነው፡፡ እነዚህ ወገኖች መሥራት እየወደዱ/እየፈለጉ መሥራት ባለመቻላቸው ልንረዳቸው ይገባል እንጂ አይሠሩም ተብለው ሊገለሉ አይገባም፡፡

ለመልካም ሥራ እንትጋ!

ሥራን ለመሥራት የተፈጠረው የሰው ልጅ ሥራውን ተግቶ መሥራት ይጠበቅበታል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ክርስቲያኖች በሥራ መትጋት እንዳለባቸው ሲያስተምር “ባንዝልም በጊዜው እናጭዳለንና መልካም ሥራን ለመሥራት አንታክት (ገላ 6:9)” በማለት ነበር ያሳሰባቸው፡፡ በሮሜ ይኖሩ ለነበሩ ክርስቲያኖችም በጻፈው መልእክቱ “ለሥራ ከመትጋት አትለግሙ፤ በመንፈስ የምትቃጠሉ ሁኑ፤ ለጌታ ተገዙ (ሮሜ 12:11)” በማለት በሥራ እንዳይለግሙ ጽፎላቸዋል፡፡ በሥራ መለገም፣ በሥራም የተነሳ ማንጎራጎር የሚያስነቅፍ ተግባር ነውና ስለዚህም ለፊልጵስዮስ ሰዎች ሲጽፍ “በመጥፎና በጠማማ ትውልድ መካከል ያለ ነቀፋ የዋሆችም ነውርም የሌለባቸው የእግዚአብሔር ልጆች እንድትሆኑ ሳታንጐራጉሩ ክፉም ሳታስቡ ሁሉን አድርጉ (ፊልጵ 2:14)” በማለት አስተምሯቸዋል፡፡

ይኸው የተወደደና ማኅቶተ ቤተ ክርስቲያን የሚባለው ሐዋርያ ለደቀ መዝሙሩ ለጢሞቴዎስም በምድር ላይ ያለውን አገልግሎትና ሥራ በትግል መስሎ ሲያስተምረው “ደግሞም በጨዋታ የሚታገል ማንም ቢሆን፥ እንደሚገባ አድርጎ ባይታገል፥ የድሉን አክሊል አያገኝም። የሚደክመው ገበሬ ፍሬውን ከሚበሉት መጀመሪያ እንዲሆን ይገባዋል (2 ጢሞ 2:6-7)” በማለት የሰው ልጅ በተሰማራበት ዘርፍ ጸንቶ መታገል (መሥራት) እንዳለበት በአጽንኦት መክሮታል፡፡ ራሱም በሰው ላይ ላለመክበድ እየሠራና እየደከመ ይኖር እንደነበር ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች “በገዛ እጃችን እየሠራን እንደክማለን፤ ሲሰድቡን እንመርቃለን፥ ሲያሳድዱን እንታገሣለን፥ ክፉ ሲናገሩን እንማልዳለን (1 ቆሮ 4:12-13)” በማለት ምሳሌ ሆኗቸዋል፡፡ ይህ አምደ ቤተ ክርስቲያን የተባለ ሐዋርያ ወንጌልን ከመስበክ ጎን ለጎን ድንኳን ይሰፋ እንደነበር ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ (ሐዋ 18፡1-4)፡፡

ስለዚህም ሲናገር “እነዚህ እጆቼ በሚያስፈልገኝ ነገር ለእኔና ከእኔ ጋር ላሉት እንዳገለገሉ እናንተ ታውቃላችሁ” (ሐዋ 20፡33-35) ብሏል፡፡ ሌሎችንም ማስቸገር እንደሌለበት ሲናገር “ከእናንተ ዘንድ በአንዱ ስንኳ እንዳንከብድበት፥ ሌሊትና ቀን በድካምና በጥረት እየሠራን እንኖር ነበር እንጂ፥ ከማንም እንጀራን እንዲያው አልበላንም” ( 2ኛ ተሰሎ 3፡8) በማለት አስገንዝቦናል፡፡ ለፊልጵስዮስ ቤተ ክርስቲያንም ያለ አንዳች ክፍያ እንዳገለገላቸው ሲናገር  “የፊልጵስዩስ ሰዎች ሆይ፥ ወንጌል በመጀመሪያ ሲሰበክ፥ ከመቄዶንያ በወጣሁ ጊዜ፥ ከእናንተ ብቻ በቀር ሌላ ቤተ ክርስቲያን በመስጠትና በመቀበል ስሌት ከእኔ ጋር እንዳልተካፈለች እናንተ ደግሞ ታውቃላችሁ” (ፊልጵ 4፡14-16) ብሏል፡፡ ይህም ለዘመናችን አገልጋዮች ሁሉ አርአያ ሊሆናቸው ይገባል፡፡ የእግዚአብሔር ምርጥ ዕቃ የተባለ ሐዋርያ ከሰፊው ስብከቱ በተጨማሪ ድንኳን ይሰፋ ከነበር የዘመናችን አገልጋዮችማ እንደምን ሥራቸውን በመደበኛነት አይሠሩ?!

በተለይም በዝርወት ዓለምና በታላላቅ ከተሞች ባሉ አብያተ ክርስቲያናት ያሉ ካህናትና ሌሎችም አገልጋዮች (አረጋውያኑን ሳይጨምር) ለሥራ የሚሆን በቂ ጊዜና ጥሩ የሥራ ዕድልም ስላላቸው ሠርተውበት ራሳቸውን፣ ቤተ ክርስቲያናቸውንና ሀገራቸውን በብዙ መጥቀም ይችላሉ። እንደሚታወቀው በአብዛኞቹ የውጭው ዓለም አብያተ ክርስቲያናት አብዛኛው (አንዳንዴም ሙሉው) መንፈሳዊ አገልግሎት የሚከናወነው በሰንበተ ክርስቲያን (እሁድ) ነው። ምንም እንኳን ከቤተ መቅደስ ውጭ የሚሰጡ ሌሎች መንፈሳዊ አገልግሎቶች ቢኖሩም እነዚህ አገልጋዮች ቢያንስ በከፊል (part-time) መሥራት ይችላሉ። ብዙዎቹም የመሥራት ፍላጎቱ ያላቸውና ቤተ ክርስቲያንንም ያለ ክፍያ ማገልገል የሚፈልጉ እንደሆኑ እንረዳለን። ምዕመናንንም ይህንን የማበረታታት፣ የሥራ ዕድሎችንም የማመቻቸት ኃላፊነት አለባቸው። ሥራ የማይሰራ አእምሮ የተንኮል፣ የክፋትና የአሉባልታ ተጠቂ ስለሚሆን ከአገልጋዮቹ ግላዊ ሕይወት አልፎ ቤተ ክርስቲያንንም እንደሚያውክ በየቦታው የምናየው እውነታ ነው።

በሌላ በኩል በ(ለ)ሥራ መትጋት ማለት ሥራ ቦታ በተመደበው ሰዓት መግባት፣ በተመደበው ሰዓት መውጣት ወይም ለተወሰነው ሰዓት ሥራ ላይ መቆየት ማለት ብቻ አይደለም። ለሥራ መትጋት ማለት ሙሉ አቅምን ተጠቅሞ መሠራት ያለበትን ሥራ በጊዜው ማከናወን ነው። ለሥራ መትጋትም የሚባለው አለቃን ለማስደሰት የሚደረግ ሳይሆን ለኅሊናና ለእግዚአብሔር ብሎ የሚገባውን በጥራት ማከናወን ነው። ለሥራ መትጋት የሚባለውም የሚከፈለንን ያህል ብቻ መሥራት አይደለም፣ ሊሠራ የሚገባውን ያህል መሥራት እንጂ። ለሥራ የሚተጋ ክርስቲያን ስለ ሠራ ይከፈለዋል እንጂ የሚከፈለውን ያህል ብቻ አይሠራም። ገንዘብ ለሥራ ከሚያተጉን ብዙ ምክንያቶች አንዱ ምክንያት እንጂ ብቸኛው ምክንያት አይደለም። ለገንዘብ ብቻ ብለን በሥራችን የምንተጋ ከሆነ ጉልበታችንን እየሸጥን እንጂ ለሥራ እየተጋን አይደለም፣ ገንዘብ ብቻውን የመንፈስም ሆነ የኅሊና ዕረፍትን አይሰጥምና። ይልቅስ የምንሠራው ሥራ ለማኅበረሰቡ ሕይወት ያለውን ጠቀሜታ እያየን ልንተጋ ይገባናል።

ታካችነትን እናስወግድ!

በሥራ ታካች መሆን በምድር ድህነትን ሲያስከትል በሰማይ ደግሞ ድኅነትን ያሳጣል፡፡ ታካችነት በሥጋም በነፍስም እንደሚጎዳ መጽሐፍ ያስተምረናል፡፡ ስለሥራ በልዩ ሁኔታ የተሰጠውን ሀብተ ጥበብ ተጠቅሞ የጻፈው ጠቢቡ ሰሎሞን ታካችነትን እናስወግድ ዘንድ በብዙ ምሳሌ አስተምሮናል፡፡ በመጽሐፈ ምሳሌ ታካቾችንና ታካችነትን ሲገስፅ “አንተ ታካች፥ እስከ መቼ ትተኛለህ? ከእንቅልፍህስ መቼ ትነሣለህ? ጥቂት ትተኛለህ፥ ጥቂት ታንቀላፋለህ፥ ትተኛም ዘንድ ጥቂት እጅህን ታጥፋለህ፤ እንግዲህ ድህነትህ እንደ ወንበዴ፥ ችጋርህም ሰይፍ እንደ ታጠቀ ሰው ይመጣብሃል (ምሳሌ 6:7-11)” እያለ ታካችነት ለድህነትና ለረሃብ እንደሚያጋልጥ በግልፅ ነግሮናል፡፡ ይኸው ጠቢብ ስለታካች እጅ ሲናገርም “የትጉ እጅ ትገዛለች፤ የታካች እጅ ግን ትገብራለች (ምሳሌ 12:24)” ይልና  “የታካች እጅ ችግረኛ ታደርጋለች፤ የትጉ እጅ ግን ባለጠጋ ታደርጋለች። በበጋ የሚያከማች ልጅ አስተዋይ ነው፤ በመከር የሚተኛ ግን እርሱ ራሱን ያስነውራል (ምሳሌ 10:4-5)” በማለት የታካችነትን አስከፊነት አጉልቶ ያስረዳል፡፡

ከእግዚአብሔር በተሰጠው ጥበብ ድንቅ ምሳሌዎችን እየመሰለ ነገረ ሃይማኖትን ያስተማረው ይህ ጠቢቡ ሰሎሞን ስለታካችነትና አስከፊነቱ ብዙ ተናግሯል፡፡ በተለይም ሥራን የማይወዱና በምኞት ብቻ የሚፈልጉትን የሚያገኙ ሰለሚመስላቸው ሰነፎች ሲናገር “ታካችን ምኞቱ ትገድለዋለች፥ እጆቹ ይሠሩ ዘንድ አይፈቅዱምና (ምሳሌ 21:25)” በማለት ታካችን ክፉ ምኞቱ እንደምትገድለው በመጽሐፈ ምሳሌ ተናግሯል፡፡ በተጨማሪም “የታካች ሰው ነፍስ ትመኛለች፤ አንዳችም አታገኝም፤ የትጉ ነፍስ ግን ትጠግባለች (ምሳሌ 13:4)” በማለት ጠንክሮ መሥራትን ወደጎን በመተው ምኞታቸውን በአቋራጭ ለማግኘት የሚያስቡ ይህ ምኞታቸው እንደሚያጠፋቸው በማያወላዳ መልኩ አስረድቶናል፡፡በሌላም አገላለጽ ሥራን ለመሥራት የሚሰንፍ ሰውን ሲገስፅ “በሥራው ታካች የሚሆን የሀብት አጥፊ ወንድም ነው (ምሳሌ 18:9-10)” በማለት ታካችነት ከሀብት አጥፊነት ተርታ እንደሚቆጠር በግልጽ አስተምሯል፡፡ ይህንንም ያለው ታካችነት በሥራ ለወደፊት ሊገኝ የሚችል ሀብትን ማምከን ስለሆነ ነው፡፡ አጥፊነት ደግሞ አሁን ያለውን ሀብት ማጥፋት ስለሆነ ሁለቱን ወንድማማች አድርጎ በምሳሌ አስተምሮናል፡፡

ክርስቲያን በሥራ መትጋትን በምንም ሊተካው አይችልም፡፡ ምድራዊ ሀብትም ይሁን ሰማያዊ ጽድቅ በመትጋት እንጂ በመታከትና በመተኛት አይገኝም፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን “በድካም ሁሉ ልምላሜ ይገኛል፤ ብዙ ነገር በሚናገር ከንፈር ግን ድህነት ብቻ አለ (ምሳሌ 14:23-24)” በማለት ልምላሜ (ትርፍ) በድካም (በመሥራት) እንጂ በከንፈር (በማውራት) እንደማይገኝ አስገንዝቦናል፡፡ በተጨማሪም “ምድሩን የሚያርስ እንጀራ ይጠግባል፤ ምናምንቴዎችን የሚከተል ግን ድህነት ይሞላበታል። የታመነ ሰው እጅግ ይባረካል፤ ባለጠጋ ለመሆን የሚቸኵል ግን ሳይቀጣ አይቀርም (ምሳሌ 28: 19-20)” ብሎ መትጋትን ገንዘብ እንድናደርግ አስተምሮናል፡፡ እንቅልፍን መውደድም እንዲሁ ለድህነት እንደሚዳርግ ሲናገር “ድሀ እንዳትሆን እንቅልፍን አትውደድ (ምሳሌ 20:13)” ብሏል፡፡

በሥራችን እግዚአብሔርን እናስቀድም!

ሥራም ሆነ ለሥራ የሚያስፈልጉን ዕውቀትና ክህሎት የእግዚአብሔር ስጦታዎች ናቸው። የሰው ልጅ የሚሠራውን ሥራ በዕውቀቱና በጉልበቱ የሚያከናውነው ቢሆንም ዕውቀትን እና ጤነትን የሠጠውን እግዚአብሔርን በሥራው ሁሉ ሊያስቀድም ይገባል። ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ስለዚህ ሲናገር “እግዚአብሔር አብን በእርሱ እያመሰገናችሁ፥ በቃል ቢሆን ወይም በሥራ የምታደርጉትን ሁሉ በጌታ በኢየሱስ ስም አድርጉት (ቊላ 3:17)” ብሏል። በተጨማሪም ክርስቲያን ሥራን ሲሠራ በትጋትና ያለ አንዳች ልግመት መሆን እንዳለበት ሲያስተምር “ለሰው ሳይሆን ለጌታ እንደምታደርጉ፥ የምታደርጉትን ሁሉ በትጋት አድርጉት (ቆላ 3:23)” በማለት አስተምሯል። ጠቢቡ ሰሎሞንም ሥራችንን ሁሉ በእግዚአብሔር ፈቃድ ማከናወን እንዳለብን ሲነግረን “ሥራህን ለእግዚአብሔር አደራ ስጥ፥ አሳብህም ትጸናለች (ምሳሌ 16:3)” ብሏል።

የእግዚአብሔር ፈቃድ ከሌለበት የሰዎች ድካም ብቻውን ፍሬ ሊያፈራ አይችልም፡፡ ያለ እግዚአብሔር ፈቃድ የሠራተኞች ድካምም ከንቱ ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ክቡር ዳዊት ስለዚህ “እግዚአብሔር ቤትን ካልሠራ፥ ሠራተኞች በከንቱ ይደክማሉ፤ እግዚአብሔር ከተማን ካልጠበቀ፥ ጠባቂ በከንቱ ይተጋል። በማለዳ መገሥገሣችሁም ከንቱ ነው። ለወዳጆቹ እንቅልፍን በሰጠ ጊዜ፥ እናንተ የመከራን እንጀራ የምትበሉ፥ ከተቀመጣችሁበት ተነሡ (መዝ 127:1-2)” በማለት በሥራችን ሁሉ እግዚአብሔርን እንድናስቀድም በመዝሙሩ አስተምሮናል፡፡   ይህንንም ዘወትር በጸሎታችን እግዚአብሔርን “የአምላካችን የእግዚአብሔር ብርሃን በላያችን ይሁን። የእጆቻችንንም ሥራ በላያችን አቅና (መዝ 90:17)” እያልን ልንለምንና ሥራችንም ሲከናወንልን ምስጋናን ልናቀርብ ይገባናል፡፡

ክርስትናን በሥራ እንመስክር!

ለሥራ ስንተጋ በሥራ ቦታ ሊኖረን የሚገባው መንፈሳዊነት (ክርስትና) በብዙዎች ዘንድ አነጋጋሪ ሲሆን ይታያል። አንዳንዶችም ክርስትናን በሥራና በእውነት ከመግለፅ ይልቅ የማስመሰል ሕይወት ውስጥ በመግባት ራሳቸውንም ሌሎችንም ይጎዳሉ። ሃይማኖታዊ ግብ በሌላቸው ተቋማት ውስጥ ማንኛውም ዓይነት እምነት ያለው (እምነት የሌለውም ጭምር) በሙያው ሊሠራ ይችላል፡፡ እነዚህ ተቋማትም የሚመሩት በየራሳቸው የሥራ ቦታ መመሪያ ነው፡፡ በቅጥርም ሂደት ሰውን በእምነቱ ምክንያት ማግለልና አድልኦ መፈጸም እንደሌለባቸው ይታመናል፡፡ በሥራ ቦታም የየራሳቸው የአለባበስ ሥርዓት ይኖራቸዋል፡፡ በመሠረታዊነት እነዚህ ተቋማት የእምነት መገለጫ (እምነትን መግለጫ) ቦታዎች ስላልሆኑ ሁሉም ሠራተኛ አለባበሱም ሆነ አነጋገሩ የየተቋማቱን ሥርዓትና መመሪያ ያከበረ ሊሆን ይገባዋል፡፡ እውነተኛ የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተከታይ እምነቱን የሚገልጸው በመልካም ስነ-ምግባሩ ነው፡፡ በእነዚህ ተቋማትም በሥራ በመትጋት፣ የተቋሙን መመሪያ በማክበር፣ ከሌሎች ሠራተኞች ጋር መልካም ግንኙነትን በመፍጠር፣ ተቋሙ የቆመለትን ዓላማ እንዲያሳካ የሚችለውን ሁሉ በማድረግና ለሌሎችም መልካም አርአያ በመሆን ነው ክርስትናውን የሚገልጠው፡፡ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማትም ያለው እንዲሁ ነው፡፡ ክርስትናችን የሚገለጠው በአስተሳሰባችን፣ በአነጋገራችንና በምግባራችን መልካምነት ሊሆን ይገባል፡፡

ከዚህ ጋር በተያያዘ በአንዳንዶች ዘንድ ነጠላ ለብሶ ወደ መሥሪያ ቤት ወይም ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት መግባት መከልከሉ ትልቅ መነጋገሪያ ጉዳይ ሲሆን አስተውለናል፡፡ መሥሪያ ቤቶችና ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ሴኩዩላር እስከሆኑ ድረስ የራሳቸው የአለባበስ ደንብ ሊኖራቸው ይችላል፡፡ ይህም ለማንኛውም ወገን የማያዳላ፣ ማንንም የማያገልል ሊሆን ይገባዋል፡፡ ይህንን ወደጎን ትተን እኛ እምነታችንን የሚገልጽ ነገር እንልበስ የምንል ከሆነ መመሪያውን እንተላለፋለን፡፡ ይሁንና ብዙ ተቋማት አካታች ስለሆኑ እንደሁኔታው ለሠራተኞቻቸው የሚጸልዩበት ቦታና ሰዓት ሁሉ እስከመፍቀድ ሲደርሱ አስተውለናል፡፡ በተቋም ውስጥ ነጠላ መልበስ የሚከለከል ከሆነ አለመልበስ ይመረጣል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም በሌሎች ተቋማት ውስጥ ነጠላ ልበሱ የሚል ትዕዛዝ የላትም፡፡ ሌሎች እምነትን የሚገልጡ ነገሮችንም ሴኪዩላር በሆኑ ተቋማት ውስጥ አጉልቶ ማሳየት እንዲሁ ተቋማቱን የሃይማኖታዊ ምልክቶች መፎካከሪያ ዐውድ በማድረግ ከቆሙለት ዓላማ ያዘናጋቸዋል፡፡ ይህንን በማድረግ ከምናተርፈው ይልቅ የምናጠፋው ይበልጣልና ጥንቃቄ ማድረጉ አይከፋም፡፡ የሌላ እምነት ተከታዮች ይህንን ሲያደርጉ ብናይ ህግን እንጂ ህግ ተላላፊዎችን መከተል የለብንም፡፡

የማዕተብ ጉዳይ ግን ከዚህ የተለየ ነው። ማዕተብ የሥላሴ ልጅነትን ስናገኝ የተሰጠን የክርስትናችን ምልክት ነው። በአንገታችን የምናስረው ስለሆነ ብዙውን ጊዜ በግልፅ ከሩቅ የሚታይ ምልክት አይደለም። ዓላማውም የእምነት (የጥምቀት) ምልክት እንጂ ለጌጥ፣ ለታይታ ወይም ለፉክክር የሚደረግ አይደለም። በሴኪዩላር ተቋማትም ቢሆን ከአብዛኛው የአለባበስ ሥርዓት ጋር የሚስማማ ነው። ይልቁንም የተለያዩ ጌጣጌጦችን በአንገት ላይ ማሰር የተለመደ ነገር በሆነበት ዘመን በመመሪያውም ሆነ በአመራሩ ‘ማዕተብ አትሠሩ’ የሚል ተቋም ካለ ልንሞግተው ይገባል። በተጨማሪም የሌሎች እምነት ተከታዮች የሚመሯቸው ሴኪዩላር ተቋማት በእምነት ምክንያት በግልፅ አድሎና ማግለል የሚፈፀምበት ሁኔታ ሲያጋጥም ችግሩ በህግ አግባብ እንዲታይ ማድረግ ይኖርብናል። በራሳችን የክህሎትና የአፈፃጸም ማነስ ወይም በተቋማቱ ሌሎች ሁኔታዎች ምክንያት ሳንቀጠር ስንቀር ወይም ተቋማቱን ስንለቅ ‘ማዕተብ በማድረጌ ነው’ ወይም ‘ኦርቶዶክስ ስለሆንኩ ነው’ ማለት ግን በምድራዊም በሰማያዊም ህግ ያስጠይቃል።

ማጠቃለያ

ሥራን በመሥራት የምናገኛቸው ብዙ ትሩፋቶች አሉ፡፡ ተግተን ስንሠራ ለራሳችን ሕይወት የሚያስፈልገንን ማሟላት እንችላለን፣ ለሌሎችም አንከብድባቸውም፡፡ በመሥራታችን ለማኅበረሰባችንና ለሀገራችን ዕድገትና ልማት የበኩላችንን ድርሻ ማበርከት እንችላለን፡፡ ጠንክረን ስንሠራ አዕምሮአችን በሙሉ አቅሙ ሥራ ላይ ስከሚያተኩር ኃጢአትን ከምትወልድና ለሞት ከምታደርስ ክፉ ሀሳብ እንርቃለን፣ ኃጢአትንም አንሠራም፡፡ በሥራ ስንተጋ ከሥራችን በምናገኘው ገንዘብ፣ እውቀትና ልምድ ሌሎች ወገኖቻችንን መርዳት እንችላለን፣ ለእነርሱና ለቀጣዩ ትውልድም መልካም አርአያና ምሳሌ መሆን እንችላለን፡፡ በርትተን ስንሠራ ለቤተ ክርስቲያንም በገንዘብ፣ በዕውቀት/በልምድ፣ በምሳሌነት አለኝታ እንሆናታለን፡፡ የቀደሙት ቅዱሳንም ለመንፈሳዊውም ለምድራዊውም ሥራ በመትጋታቸው ነው ለሁላችንም አብነት ሆነው ያለፉት፡፡ በሥራ ከመትጋት ውጭ ለሰው ልጅ ሌላ የሚበጀው ነገር እንደሌለም ለማንም የተሰወረ አይደለም፡፡

ስለዚህም የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምዕመናንና አገልጋዮች የሚያምኑት እውነተኛ እምነት በሥራ የሚገለጥ መሆኑን በማስተዋል ለሥራ መትጋትን ገንዘብ ሊያደርጉ ይገባል፡፡ በአንዳንዶች ዘንድ እንደሚታየውም “በአቋራጭ የመክበርን” አስተሳሰብ ከልባቸውና ከህሊናቸው ማራቅ አለባቸው። እውነተኛ እምነት ጭብጥ በሌለው ልፍለፋና በየቀኑ በሚቀያየር የፋሽን ልብስ፣ በሰው ዘንድ ልታይ ልታይ በማለት ሳይሆን በፍጹም ነፍስ፣ በፍጹም ሀሳብና በፍጹም ልብ ውስጥ ተዋሕዶ በመንፈሳዊና በምድራዊ ሥራ የሚገለጥ ስለሆነ ለሥራ መትጋትን ሁሉም ገንዘብ ሊያደርገው ይገባል እንላለን፡፡

 

1 thought on “በሥራ መትጋት: ሊሠራ የማይወድ አይብላ!

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s