የነነዌ ከተማ አስቀድሞ በአሦር አማካይነት ከጤግሮስ ወንዝ በስተምሥራቅ (በአሁኗ ኢራቅ ሞሱል ከተማ አቅራቢያ) ተመሠረተች (ዘፍ 10፡11-12)፡፡ ›› ከብዙ ዘመናት በኋላ የንጉሥ ሰናክሬም መቀመጫ ሆነች (2ኛ ነገ 19፡36)፡፡ በዚያን ዘመን ነነዌ በአካባቢው ካሉት ታላላቅ ከተሞች አንዷ ነበረች፡፡ በዚህች ከተማ ታሪክ መሠረት ከ786-746 ዓ.ዓ ባለው ጊዜ ውስጥ ነቢዩ ዮናስ የነበረበት ዘመን ነበር (2ኛ ነገ 14፡25)፡፡ በነቢዩ ዮናስም እንደተነገረው በዚያን ዘመን ነነዌ የሦስት ቀን መንገድ ያህል እጅግ የምትሰፋና አንድ መቶ ሀያ ሺህ ሕዝብ ይኖርባት የነበረ ከተማ ነበረች (ዮናስ 3፡3 ዮናስ 4፡11)፡፡
በዚያን ዘመን የነበሩ የነነዌ ሰዎች ክፋታቸው ከእግዚብሔር ዘንድ ደርሶ ስለነበር እግዚአብሔር ነቢዩ ዮናስን ወደዚያ ላከው፡፡ ‹‹ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፥ ክፉታቸውም ወደ ፊቴ ወጥቶአልና በእርስዋ ላይ ስበክ። ›› ብሎ ላከው፡፡ ዮናስ ግን ወደ ተርሴስ ለመኮብለል ቢሞክርም እግዚአብሔር በድንቅ ተአምራቱ ወደ ነነነዌ መልሶታል፡፡ እንደገናም እግዚአብሄር ለዮናስ ‹‹ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፥ የምነግርህንም ስብከት ስበክላት አለው።›› ዮናስም ሄዶ ‹‹ነነዌ በሦስት ቀን ውስጥ ነነዌ ትገለበጣለች!›› ብሎ ጮኸ፡፡
የነነዌ ሰዎችም ፈጥነው ንስሐ ገቡ፡፡ ‹‹ የነነዌም ሰዎች እግዚአብሔርን አመኑ፤ ለጾም አዋጅ ነገሩ፥ ከታላቁም ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ። ወሬውም ወደ ነነዌ ንጉሥ ደረሰ፤ እርሱም ከዙፋኑ ተነሥቶ መጐናጸፊያውን አወለቀ ማቅም ለበሰ፥ በአመድም ላይ ተቀመጠ።›› እግዚአብሔርም ምህረቱን ላከላቸው፡፡ ‹‹እግዚአብሔርም ከክፉ መንገዳቸው እንደተመለሱ ሥራቸውን አየ፤ እግዚአብሔርም ያደርግባቸው ዘንድ በተናገረው ክፉ ነገር ተጸጽቶ አላደረገውም።›› በዚህ ዘመን ፈጥነው ንስሐ በመግባታቸው ከጥፋት ድነዋል፡፡ ነገር ግን ከአንድ መቶ ኃምሳ አመት በኋላ ይህች ከተማ በነቢዩ ናሆምና ነቢዩ ሶፎንያስ አስቀድመው እንደተናገሩት በ612 ዓ.ዓ ጠፍታለች (ናሆም 1፡8 3፡13 ሶፎ 2፡13-15)፡፡
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በመዋዕለ ስብከቱ ስለ ነነዌ ሰዎች ‹‹የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነሥተው ይፈርዱበታል፤ በዮናስ ስብከት ንስሐ ገብተዋልና፥ እነሆም፥ ከዮናስ የሚበልጥ ከዚህ አለ›› ሲል ተናግሯል (ማቴ 12፡41 ሉቃ 11፡32)፡፡ ይህ አስደናቂ ቃል ነው፡፡ ለመሆኑ እነዚህ የነነዌ ሰዎች ስለምንድን ነው ‹‹በዚህ ትውልድ ላይ ይፈርዱበታል›› የተባለው? ይህ የሚሆነው ስለሚከተሉት አራት ምክንያቶች ነው፡፡
1) የነነዌ ሰዎች በአንድ ነቢይ ስብከት ብቻ አመኑ፤ አይሁድ ግን ብዙ ነቢያትና ሕግጋት እያላቸው አላመኑም፡፡
አይሁድ አስቀድሞ በሙሴ አማካይነት የኦሪት ሕግ ተሰጥታቸዋለች፡፡ ቀጥሎም ብዙ ዐበይትና ደቂቅ ነቢያት አስተምረዋቸዋል፡፡ኋላም መጥምቁ ዮሐንስ ስለ ጌታ አስተምሯቸዋል፡፡ ነገር ግን በጌታ ለማመን ልባቸው ደነደነ፡፡ የነነዌ ሰዎች ግን እንደ አይሁድ ብዙ ነቢያት ሳይላኩላቸው ለሀገሩ እንግዳ በሆነውና ከእነርሱ መዳን ይልቅ ሐሰተኛ ነቢይ እባላለሁ ብሎ ይሰጋ በነበረው በአንዱ በዮናስ ስብከት ብቻ አምነዋል፡፡ እንደ እናንተ ብዙ ነቢያት ሳይላኩልን በአንድ ነቢይ ስብከት ብቻ አምነን ንስሐ ገብተናል ሲሉ የነነዌ ሰዎች በአይሁድ ላይ ይመሰክሩባቸዋል፡፡
2) የነነዌ ሰዎች የነቢዩ ስበከት አምነው ንስሐ ገቡ፤ አይሁድ ግን በነቢያት ጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ስብከት እንኳን አላመኑም፡፡
የነነዌ ሰዎች እግዚአብሔር በላከው በእግዚአብሔር ነቢይ በዮናስ ስብከት አምነው ንስሐ ገብተዋል፡፡ አይሁድ ግን ነቢዩ ዮናስን የላከው የነቢያት ጌታ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ በአካል መጥቶ በምድር ተመላልሶ ቢሰብክላቸውም አልተቀበሉትም፡፡ የነነዌ ሰዎች መልእክተኛውን ተቀበሉ፤ አይሁድ ግን መልእክተኞችን የላከውን አልተቀበሉትም፡፡አይሁድ ግን ለሰው ልጅ ሁሉ ቤዛ ሊሆን በመጣው በእግዚአብሔር ልጅ አላመኑምና የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ይመሰክሩባቸዋል፡፡ እኛ መልእክተኛውን ተቀብለን ንስሐ ስንገባ እናንተ ግን የመልእክተኛውን ጌታ አልተቀበላችሁም ሲሉ የነነዌ ሰዎች በአይሁድ ላይ ይመሰክሩባቸዋል፡፡
3) የነነዌ ሰዎች ምንም ተአምራትን ሳያዩ ንስሐ ገቡ፤ አይሁድ ግን እጅግ ብዙ ተአምራትን እያዩ ልባቸው ደነደነ፡፡
የነነዌ ሰዎች ከዮናስ ስብከት በስተቀር አንድም ተአምር ሳያዩ አመነዋል፡፡ አይሁድ ግን አስቀድሞ ነቢያት ከዚያም ጌታ ራሱ እጅግ ብዙ ድንቅ ተአምራትን ቢያሳዩአቸውም አልተቀበሉትም፡፡ ይህም አልበቃ ብሏቸው ሌላ ምልክት እንዲያሳያቸው ይሹ ነበር፡፡ የነነዌ ሰዎች እኛ አንድ ተአምር እንኳን ሳናይ አምነን ንስሐ ገብተናል፤ እናንተ ግን እጅግ ብዙ ተአምራት በፊታችሁ ሲደረግ እያያችሁ አምናችሁ ንስሐ አልገባችሁም ብለው ይመሰክሩባቸዋል፡፡ “ክፉና አመንዝራ ትውልድ ምልክትን ትሻለች፣ ምልክት ግን ከነቢዩ ዮናስ ምልክት በቀር አይሰጣትም” ማቴ. 16፡4 ብሎ ጌታችን የተናገረው ብዙ ተአምራትን አይተው ለማያምኑ ለእንደዚህ አይነቱ ትውልድ ነው፡፡
4) የነነዌ ስዎች በጥቂት ቀናት ስብከት ብቻ ንስሐ ገቡ፤ አይሁድ ግን በብዙ ዓመታት ስበከት ንስሐ አልገቡም፡፡
የነነዌ ሰዎች በነቢዩ ዮናስ የተሰበከላቸው ለጥቂት ቀናት ብቻ ነበር፡፡ በዚያም የአጭር ቀናት ስብከት አምነው ንስሐ ገብተው ሊመጣባቸው ከነበረ ጥፋት ድነዋል፡፡ አይሁድ ግን ጌታ ብቻ ከሦስት አመት በላይ ብዙ ድንቅ ተአምራትን እያደረገ አስተምሯቸው አልተቀበሉትም፡፡ ስለዚህ የነነዌ ሰዎች እኛ በጥቂት ቀናትና በአንድ ነቢይ ስብከት ብቻ አምነናል ንስሐም ገብተናል እናንተ ግን ለብዙ ዘመናት ብዙ ነቢያት ኋላም ጌታ ራሱ ለዓመታት ቢያስተምሯችሁም አምናችሁ ንስሐ አልገባችሁም ሲሉ ይመሰክሩባቸዋል፡፡
በፍርድ ቀን የነነዌ ሰዎች እንዳይፈርዱብን ምን እናድርግ?
ጌታችን የሚበዙ ተአምራት የተደረገባቸውን ከተማዎች ንስሐ ስላልገቡ ሲነቅፋቸው ‹‹ወዮልሽ ኮራዚ፤ ወዮልሽ ቤተ ሳይዳ፤ በእናንተ የተደረገው ተአምራት በጢሮስና በሲዶና ተደርጎ ቢሆን፥ ማቅ ለብሰው አመድም ነስንሰው ከብዙ ጊዜ በፊት ንስሐ በገቡ ነበርና። ነገር ግን እላችኋለሁ፥ በፍርድ ቀን ከእናንተ ይልቅ ለጢሮስና ለሲዶና ይቀልላቸዋል። አንቺም ቅፍርናሆም፥ እስከ ሰማይ ከፍ አልሽን? ወደ ሲኦል ትወርጃለሽ፤ በአንቺ የተደረገው ተአምራት በሰዶም ተደርጎ ቢሆን፥ እስከ ዛሬ በኖረች ነበርና። ነገር ግን እላችኋለሁ፥ በፍርድ ቀን ከአንቺ ይልቅ ለሰዶም አገር ይቀልላታል (ማቴ 11፡20-24)።›› ያለው ባየነውና በሰማነው ተምረን ንስሐ እንገባ ዘንድ ነው፡፡
በነነዌ ፆም የንስሐ ምስክሮች የሆኑትን የነነዌን ሰዎች ስናስብ ራሳችንን መጠየቅ ያለብን መሠረታዊ ጥያቄ ይህ ነው፡፡ እነርሱ በአንድ ነቢይ ስብከት ብቻ አምነው ንስሐ ገቡ፡፡ እኛ ግን ብዙ መምህራን መክረውን፣ አስተምረውን፣ ብዙ ጉባዔያትን ተሳትፈን፣ ብዙ መጻሕፍት እያሉልን ንስሐ ገብተናል ወይ? እነርሱ በጥቂት ቀናት ስብከት ብቻ አምነው ንስሐ ገብተዋል፡፡ እኛ ግን ከሕፃንነት ጀምሮ የእግዚአብሔርን ቃል እየተማርን አድገናል፡፡ በዚህ ለዘመናት የተማርነውን ቃል በሕይወታችን ኖረነዋል ወይ? የነነዌ ሰዎች አንድም ተአምር ሳያዩ አምነው ንስሐ ገብተዋል፡፡ ለእኛ ግን ብዙ ተአምራት በጌታና በቅዱሳኑ ተደርገው እየሰማንና እያየን ልባችን ተሰብሯል ወይ? እንግዲህ የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን እንዳይመሰክሩብን “ለጠቢብ ሰው አንድ ቃል ትበቃዋለች” እንደተባለ በተማርነውና ባወቅነው አምነን ንስሐ ልንገባ፣ እንደ ቅዱስ ቃሉም ህይወታችንን ልንመራ ይገባል፡፡