ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ቤተክርስቲያንን በተለያዩ ስያሜዎች በተለያዩ ዘመናት ሲገልጿት ኖረዋል፡፡ እነዚህ ሊቃውንት ያስቀመጧቸው የቤተክርስቲያን ስያሜዎች በመጻሕፍት የተገለፀውን እውነትና በትውፊት የተቀበሉትን ሥርዓተ ቤተክርስቲያን መሠረት በማድረግ የተሰጡ ስያሜዎች ናቸው፡፡ ዓላማቸውም የቤተክርስቲያኒቱን ምንነታና ማንነት በአጭር ቃላት በገላጭ ቋንቋ ለማስተማርና ለማስረዳት ነው፡፡ እነዚህም ስያሜዎች ከትውልድ ትውልድ በቤተክርስቲያን አስተምህሮ ሲተላለፉ ቆይተው ከእኛ ዘመን ደርሰዋል፡፡
አንዳንድ ወገኖች እነዚህ ስያሜዎች በመጽሐፍ ቅዱስ የተቀመጡ አይደሉም በማለት ይከራከራሉ፡፡ ነገር ግን እነዚህን ስያሜዎች ያስቀመጡልን ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን መጽሐፍ ቅዱስን በሚገባ የተማሩ፣ የክርስቶስን ወንጌል በጥልቀት ያወቁ፣ ሥርዓተ ቤተክርስቲያንንም የጠነቀቁ፣ ከማወቅም በላይ በሕይወታቸው የኖሩ ናቸው፡፡ ያስቀመጡልን ስያሜዎችም መጽሀፍ ቅዱስን መሠረት ያደረጉ ናቸው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሩአችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ፥ የኑሮአቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነታቸው ምሰሉአቸው።›› እንዳለ እኛ እነርሱን አብነት አድርገን የምንኖር ክርስቲያኖች እነርስ ያስቀመጧቸውን ስያሜዎች ተጠቅመን ስለ ቤተክርስቲያን እናስተምራለን፡፡
የበተክርስቲያን አስተምህሮና ምሥጢር ጥልቅ ከመሆኑ የተነሳ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ብዙ ስያሜዎችን ለቤተክርስቲያን ሰጥተው አስተምረዋል፡፡ የሚከተሉትን ለምሳሌ ያህል አቀረብን እንጂ ሌሎችም ስያሜዎች ይኖራሉ፡፡ የቤተክርስቲያንን ስያሜዎና መነሻቸውን ለመረዳት ያህን ግን የሚከተሉትን ዋና ዋና ስያሜዎች ከአጭር ማብራሪያ ጋር እንደሚከተለው ቀርበዋል፡፡ ከዚህ በታች የቀረበው ዝርዝሩ ሁሉንም ስያሜዎች የሚያጠቃልል እንዳልሆነ ግን አንባቢው ከግምት ውስጥ ማስገባት ይኖርበታል፡፡
- እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን “የክርስቶስ ሙሽራ” ትባላለች፡፡
እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን የዓለምን ኃጢአት በቤዛነቱ ያስወገደ የእግዚአብሔር በግ፣ በተዋህዶ የከበረ ወልደ አብ፣ ወልደ ማርያም ኢየሱስ ክርስቶስ ሙሽራ ትባላለች፡፡ ይህም በቅዱሳት መጻሕፍት በግልፅና በጥልቀት የተቀመጠ ነው፡፡«ሙሽራ ያለችው እርሱ ሙሽራ ነው፤ ድምፁን ለመስማት አጠገቡ የሚቆሙ ሚዜ ግን የሙሽራውን ድምፅ ሲሰማ እጅግ ደስ ይለዋል፤ ያ ደስታ የእኔ ነው፡፡ እርሱም አሁን ተፈጽሟል፡፡ እርሱ ሊልቅ፣ እኔ ላንስ ይገባል፡፡»/ዮሐ 3. / ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ በሙሽራ በሙሽሪት እና በሚዜ መስሎ የተናገረው የክርስቶስን፣ የቤተክርስቲያንን እና እንደ ራሱ ያሉ አገልጋዮችን ነገር ነው፡፡ በክርስቶስ እና በቤተክርስቲያን መካከል ያለውን ግንኙነት በሙሽራ እና በሙሽሪት /በባል እና በሚስት/ መካከል ካለው ግንኙነት ጋር የሚያመሳስሉት በርካታ ነገሮች አሉ፡፡
- ሙሽሪትን /ሚስቱን/ የሚመርጣት፣ የሚያጫት ሙሽራው /ባል/ ነው፡፡ ቤተክርስቲያንንም የመረጣትና ሙሽራው እንድትሆን ያደረጋት ራሱ ክርስቶስ ነው፡፡
- ባል ሚስቱን መጠበቅ፣ መንከባከብ ራሱን አሳልፎ እስኪሰጥ ድረስ መውደድ ይጠበቅበታል፤ ክርስቶስም ስለ ቤተክርስቲያን ይህንን አድርጓል፡፡ ሚስት ራሷን ለባሏ ራሷን ማስገዛት አለባት፡፡ ቤተክርስቲያንም ለክርስቶስ እንዲሁ ማድረግ አለባት፡፡
- ሙሽሪት በሰርጓ ቀን ራሷን አስውባ ትቀርባለች፤ ክርስቶስም ቤተክርስቲያንን ወደ ራሱ ያቀረባት ሙሽራው ያደረጋት በሥጋውና በደሙ አንጽቶ፤ ነውሯን አስወግዶና አስውቦ ነው፡፡
በዚህም ምክንያት የእግዚአብሔርን እና የሰው ልጆችን ግንኙነት በሙሽራና በሙሽሪት /በባልና በሚስት/ እየመሰሉ በብሉይ ኪዳንም በሐዲስ ኪዳንም ብዙዎች አስተምረዋል፡፡ በብሉይ ኪዳን ከነበሩት መካከል በፍቅር ግጥም መልክ የተጻፈው መኅልየ መኅልይ ዘሰሎሞን፣ ትንቢተ ሕዝቅኤል /ምዕራፍ 16/፣ ትንቢተ ሆሴዕ /ምዕ.1/ ተጠቃሸ ናቸው፡፡
በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ቅዱስ ጳዉሎስ በሁለተኛው የቆሮንቶስ መልእክቱ «እናንተ እንደ ንጽሕት ድንግል ለክርስቶስ ለማቅረብ ለአንድ ወንድ አጭቻችኋለሁ» /11-2/ ብሎ ጽፏል፡፡ ለኤፌሶን ሰዎች በላከው መልእክቱም እንዲህ ይላል፤ «ሚስቶች ሆይ ለጌታ እንደምትገዙ ለባሎቻችሁም ተገዙ ክርስቶስ አካሉ ለሆነችው አዳኟ ለሆናት ቤተ ክርስቲያን ራስ እንደሆነው ሁሉ ባልም የሚስቱ ራስ ነው፡፡ ባሎች ሆይ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንን እንደወደዳትና ራሱንም ስለ እርሷ አሳልፎ እንደሰጠ እናንተም ሚስቶቻችሁን ውደዱ በቃሉ አማካኝነት በማንፃት እንድትቀደስ. . . አንዳች እንከን ሳይገኝባት ቅድስትና ነውር አልባ የሆነች ክብርት ቤተክርስቲያን አድርጎ ሊያቀርባት ነው. . . ይህ ምስጢር ታላቅ ነው፤ እኔም ይኽንን ስለ ክርስቶስና ስለ ቤተክርስቲያን እናገራለሁ፡፡» /5-22-32/፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ ነባቤ መለኮትም በራእይ መጽሐፉ ሰማያዊት ቤተክርስቲያን የሆነች አዲሲቷን ኢየሩሳሌምን የበጉ ሙሽራ ይላታል፡፡ «ቅድሰቲቱ ከተማ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም ለባሏ እንደተዋበች ሙሽራ ተዘጋጅታ ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስትወርድ አየሁ» /21-1-9/፡፡ ከዚህም አንፃር ቤተክርስቲያን የክርስቶስ ሙሽራ እንደሆነች አባቶቻችን ያስተማሩት በምድር የምናያት ቤተክርስቲያን በሰማይ ያለችው የቅድስት ኢየሩሳሌም ምሳሌ ናትና ነው፡፡
- እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን “ስንዱ እመቤት” ትባላለች፡፡
ቤተክርስቲያናችን ስንዱ እመቤት በመሆኗ መንፈሳዊ ምስጢርን፣ ታሪክንና ትውፊትን በማስተባበር ልዩና እንደ እንቁ የሚያበራ ሥርዓትን ሠርታለች፡፡በረከት ያለበት የትምህርት ቤት ገበታ፣ ከነፍስ የሚያጣምር፣ በጥቂት ጊዚያዊ መቸገር ውስጥ የብዙ ዘመን ሀብታም የሚያደርግ፣ ከራስ አልፎ ትውልድ የሚታነጽበት፣ ዘመንን የሚሻገር/የሚያሻግር ይሄ ይቀረዋል የማይባል የሊቃውንት ዐውድማ የሆኑ አብነት ትምህርት ቤቶችን በማቋቋም ስንዱ እመቤትነቷን ታሳያለች፡፡ እነዚህ አብነት ትምህርት ቤቶች ቅዱሳን ኒቢያትና ሐዋርያት የሰበኩትን የጌታችንን ቅዱስ ቃል ከነትርጓሜው ሳይፋለስና ሳይዛነፍ በዘመናት መካከል እንዲሻገር በማድረግ ቤተክርስቲያን በእግዚአብሔር ቅዱስ ቃል አጋዥነት የዓለምን ፈተና፣ የመናፍቃንን ክህደት እያሸነፈች እስከ ምጽዓተ ክርስቶስ ድረስ እንድትቆይ ያግዟታልን።
በዚህ መልክ ቤተክርስቲያን ሁሉን በአግባቡና ለሰው ልጅ መዳን እንዲሆን አድርጋ አዘጋጅታለች፡፡ ለህፃናትና ለወጣቶች ለጎልማሶችና ለአረጋውያን የሚሆን የወንጌል ትምህርትና የምስጋና አገልግሎት አዘጋጅታለች፡፡ ለእህቶችና ለወንድሞች እንዲሆን አድርጋ ሥርዓትን ሠርታለች፡፡ አሁን ላለው ብቻ ሳይሆን ለወደፊትም ለሚኖረው ትውልድ መንፈሳዊ መጻሕፍትንና የተለያዩ ቅርሶችን አበርክታለች፡፡ ለአስተዳደር ለሥርዓተ ትምህርት ለሕንፃ ወዘተ ጥበብ መጎልበት የራስዋን ድርሻ አበርክታለች፡፡ ለዚህም ነው የጎደለባት የሌላት ስንዱ እመቤት የምትባለው፡፡
ከዚህ ውጭ ሁሉን ነገር የተሟላላትንና ስንዱ የሆነችውን ቤተክርስቲያን ብዙ ነገር የጎደላትና ኋላ ቀር አድርጎ ማቅረብ የዕውቀት ማነስ ነው፡፡ የቤተክርስቲያኒቱን አስተምህሮ እኛ አላወቅነው ይሆናል እንጂ ሁሉን ነገር የጠነቀቀች ቤተክርስቲያን ነው አባቶቻቸን ያስረከቡን፡፡ የእኛ የቤተክርስቲያንን አስተምህሮና ሥርዓት መሠረቱንና ጥልቀቱን አለማወቅ ራሳችንን አላዋቂ ያደርገናል እነጂ ቤተክርስቲያንን ስንዱ እመቤት ከመባል አያስቀራትም፡፡ ስለዚህ የቤተክርስቲያን አስተምህሮ በካህናቱ፣ በመምህራኑና በምዕመናኑ የእውቀት ልክ መለካት የለበትም፡፡
- እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን “የጸጋው ግምጃ ቤት” ትባላለች፡፡
ቤተክርስቲያን የክርስቶስ የጸጋው ግምጃ ቤት ናት፡፡ ይህም የክርስቶስ ጸጋ በሰፊው የሚገኝባትና የሚታደልባት ናት ለማለት ነው፡፡ የሐዲስ ኪዳን ዘመን በክርስቶስ ቤዛነት ያመኑ፣ ቅዱሣት መጻሕፍትን በተግባር የሚኖሩ ምዕመናንና ምዕመናት የእግዚአብሔርን የጸጋ ስጦታ ያለመከልከል የሚቀበሉበት ዘመን ነው፡፡ ከጸጋ ስጦታዎች ዋና ዋናዎቹ በጥምቀት ከእግዚአብሔር በጸጋ መወለድ፣ በቅብዓ ሜሮን ልጅነትን ማጽናት፣ የክርስቶስ ቅዱስ ስጋና ክቡር ደም በንስሓ በተዘጋጀ ልቦና ቀርቦ በመቀበል ከክርስቶስ ህያውነት የተነሳ ለዘለዓለም ህያው ሆኖ መኖር ናቸው፡፡ እነዚህ ሁሉ ጸጋዎች በእምነት ለቀረቡ ሰዎች የሚታደሉት በቤተክርስቲያን አማካኝነት ነውና ቅድስት ቤተክርስቲያን የጸጋ ሁሉ ምንጭ የእግዚአብሔር የጸጋው ግምጃ ቤት ትባላለች፡፡ ድል ያደረጉ ቅዱሳን በእርስዋ ኖረው የቅድስናን ጸጋ አግኝተዋል፤ ካህናት በእርስዋ ተምረው የምስጋናን ጸጋ ለብሰዋል፤ ሊቃውንት በእርስዋ ኖረው መጻሕፍትን የማወቅና የማስተማር ጸጋ ተቀብለዋል፡፡ በቤተክርስቲያን ያለው ጸጋ ምንጩ አንድ ቢሆንም እርሱ ግን የተለያየ ነው፡፡ የጸጋ ስጦታን በሚመለከት ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡-
“ነገር ግን መንፈስ ቅዱስን መግለጥ ለእያንዳንዱ ለጥቅም ይሰጠዋል። ለአንዱ ጥበብን መናገር በመንፈስ ይሰጠዋልና፥ ለአንዱም በዚያው መንፈስ እውቀትን መናገር ይሰጠዋል፥ ለአንዱም በዚያው መንፈስ እምነት፥ ለአንዱም በአንዱ መንፈስ የመፈወስ ስጦታ፥ ለአንዱም ተአምራትን ማድረግ፥ ለአንዱም ትንቢትን መናገር፥ ለአንዱም መናፍስትን መለየት፥ ለአንዱም በልዩ ዓይነት ልሳን መናገር፥ ለአንዱም በልሳኖች የተነገረውን መተርጎም ይሰጠዋል፤ ይህን ሁሉ ግን ያ አንዱ መንፈስ እንደሚፈቅድ ለእያንዳንዱ ለብቻው እያካፈለ ያደርጋል።” ይላል፡፡ ይህ ሁሉ ጸጋ በቤተክርስቲያን አማካኝነት የባህርይ አምላክ ከሆነው ከክርስቶስ ይገኛልና ቤተክርስቲያን የጸጋ ግምጃ ቤት ናት፡፡
በሌላም ስፍራ ሐዋርያው “እንደ ተሰጠንም ጸጋ ልዩ ልዩ ስጦታ አለን፤ ትንቢት ቢሆን እንደ እምነታችን መጠን ትንቢት እንናገር፤ አገልግሎት ቢሆን በአገልግሎታችን እንትጋ፤ የሚያስተምርም ቢሆን በማስተማሩ ይትጋ፤ የሚመክርም ቢሆን በመምከሩ ይትጋ፤ የሚሰጥ በልግስና ይስጥ፤ የሚገዛ በትጋት ይግዛ፤ የሚምር በደስታ ይማር።” ይላል፡፡ ሮሜ 12፡6-8 ሰው በቤተክርስቲያን ሲኖር በእነዚህ ጸጋዎች ተጠቅሞ ያገለግል ዘንድ ቤተክርስቲያን የጸጋ ግምጃ ቤት ተብላለች፡፡
ቅዱስ ኤራቅሊስ “ፍጹም ልጅነትን ድኅነትን የተመላች የቅድስት ቤተክርስቲያንን የክብሯን ብዛት አንደበት ሊናገረው አይችልም፤ በዚህ ምድራውያን ሀብታት አሉ፤ ግን ስለምድራውያን ፈንታ ሰማያውያን ሀብታትን ሰጠን፡፡” በማለት የቤተክርስቲያን ጸጋና ክብር ተነግሮ የማያልቅ መሆኑን ጽፏል፡፡ ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ኤራቅሊስ ምዕራፍ 49፡16
- እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን “አካለ ክርስቶስ” ትባላለች፡፡
ቤተክርስቲያን አካለ ክርስቶስ (የክርስቶስ አካል) ትባላለች፡፡ ለምን የክርስቶስ አካል ተባለች ቢባል ይህ በቅዱሳት መጻሕፍት የተረጋገጠ እውነት ስለሆነ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹እናንተም የክርስቶስ አካል ናችሁ እያንዳንዳችሁም ብልቶች ናችሁ። እግዚአብሔርም በቤተ ክርስቲያን አንዳንዶቹን አስቀድሞ ሐዋርያትን፥ ሁለተኛም ነቢያትን፥ ሦስተኛም አስተማሪዎችን፥ ቀጥሎም ተአምራት ማድረግን፥ ቀጥሎም የመፈወስን ስጦታ፥ እርዳታንም፥ አገዛዝንም፥ የልዩ ልዩ ዓይነት ልሳኖችንም አድርጎአል።›› ብሎ እያንዳንዱ ክርስቲያን የክርስቲያኖችም ኅብረት የክርስቶስ አካል መሆኑን አስተምሯል፡፡ 1ኛ ቆሮ 12፡27-28
በተጨማሪም ‹‹አሁን በመከራዬ ስለ እናንተ ደስ ይለኛል፥ ስለ አካሉም ማለት ስለ ቤተ ክርስቲያን በሥጋዬ በክርስቶስ መከራ የጐደለውን እፈጽማለሁ። ስለ እናንተ እንደ ተሰጠኝ እንደ እግዚአብሔር መጋቢነት፥ የእግዚአብሔርን ቃል ፈጽሜ እንድሰብክ እኔ የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ሆንሁ። እርሱም የአካሉ ማለት የቤተ ክርስቲያን ራስ ነው። እርሱም በሁሉ ፊተኛ ይሆን ዘንድ፥ መጀመሪያ ከሙታንም በኵር ነው።›› በማለት ቤተክርስቲያን የክርስቶስ አካል መሆኗን አስረግጦ ጽፏል፡፡ ቆላ 1፡ 18 24-25
እንዲሁም ‹‹ክርስቶስ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ራስ እንደ ሆነ እርሱም አካሉን የሚያድን እንደ ሆነ ባል የሚስት ራስ ነውና።ማንም የገዛ ሥጋውን የሚጠላ ከቶ የለምና፥ ነገር ግን የአካሉ ብልቶች ስለሆንን፥ ክርስቶስ ደግሞ ለቤተ ክርስቲያን እንዳደረገላት፥ ይመግበዋል ይከባከበውማል።›› ሲል አካሉን ቤተክርስቲያንን የሚጠብቃት ራስ የሆናት ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን በሰፊው አብራርቷል፡፡ ኤፌ 5፡23 30
- እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን “ባህረ ጥበባት” ትባላለች፡፡
ባሕረ ጥበባትና ስንዱ እመቤት የሆነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ልዩ ከሚያደርጓት ነገሮች መካከል አንዱ የሒሳብ ስሌት ሰርታ የዘመን መቁጠሪያ ሳይንስን (ባሕረ ሐሳብን) ቀምራ አበቅቴና መጥቅን ለይታ የአጿማትና የበዓላትን ዕለታት ወስና ለትውልድ ማስተለለፏ ነው፡፡ በመሆኑ ዘወትር በየዓመቱ ሰባቱን የአዋጅ አጽዋማት ታውጃለች፣
ጠቢቡ ሰሎሞን ‹‹የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ ሰነፎች ግን ጥበብንና ተግሣጽን ይንቃሉ። ምሳሌ 1፡7›› እንደተባለ ቤተክርስቲያን እግዚአብሔርን መፍራትን በማስተማር የሰው ልጆች ወደ ጥበብ እንዲደርሱ ታደርጋለችና ባህረ ጥበባት ተብላለች፡፡ አንዳንዶች ቤተክርስቲያንን ባለማወቅ ኋላ ቀር አድርገው ቢስሏትም ቤተክርስቲያን ግን የጥበብ ማዕከል ናት፡፡
ልበ አምላክ ዳዊትም በመዝሙር ‹‹የጻድቅ አፍ ጥበብን ያስተምራል፥ አንደበቱም ፍርድን ይናገራል። መዝ 37፡30›› እንዳለ የጽድቅና የጻድቃን መገኛ ቤተክርስቲያን ናትን ባህረ ጥበባበት (የጥበባበት ባህር) ተብላለች፡፡ ከቤተክርስቲያን ውጭ ጥበብ የለም፡፡ ካለም መንፈሳዊ ሳይሆን ዓለማዊ ጥበብ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ወደ ሕይወት የሚያደርስ ጥበብ አይደለም፡፡
ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብም በመልክቱ ‹‹ከእናንተ ግን ማንም ጥበብ ቢጎድለው፥ ሳይነቅፍ በልግስና ለሁሉ የሚሰጠውን እግዚአብሔርን ይለምን፥ ለእርሱም ይሰጠዋል። ላይኛይቱ ጥበብ ግን በመጀመሪያ ንጽሕት ናት፥ በኋላም ታራቂ፥ ገር፥ እሺ ባይ ምሕረትና በጎ ፍሬ የሞላባት፥ ጥርጥርና ግብዝነት የሌለባት ናት። ያዕ 1፡5 3፡17›› እንዳለ ይህች ጥበብና የጥበብ ባለቤት የሚገኙባት ቤተክርስቲያን የጥባብ መገኛ ትባላለች፡፡
‹‹ጥበብ ቤትዋን ሠራች፥ ሰባቱንም ምሰሶችዋን አቆመች። ፍሪዳዋን አረደች፥ የወይን ጠጅዋን ደባለቀች፥ ማዕድዋን አዘጋጀች። ባሪያዎችዋን ልካ በከተማይቱ ከፍተኛ ስፍራ ላይ ጠራች። አላዋቂ የሆነ ወደዚህ ፈቀቅ ይበል፤ አእምሮ የጐደላቸውንም እንዲህ አለች። ኑ፥ እንጀራዬን ብሉ፥ የደባለቅሁትንም የወይን ጠጅ ጠጡ። አላዋቂነትን ትታችሁ በሕይወት ኑሩ፥ በማስተዋልም መንገድ ሂዱ። ምሳሌ 9፡1-6›› በዚህ አስተምህሮ ጥበብ የተባለች ባህረ ጥባበት የክርስቶስ ቤተክርስቲያን ናት፡፡ ክርስቶስ በዚች ቤተክርስቲያን ሆኖ ይህንን ያደርጋልና፡፡
- እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን “መዝገበ ምሥጢር” ትባላለች፡፡
እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን የማትመረመርና ጥልቅ የሆነች ‹‹መዝገበ ምሥጢር›› ትባላለች፡፡ ይህም የምሥጢር መዝገብ ማለት ነው፡፡ ቤተክርስቲያን አንብበው የማይጨርስዋት የምሥጢር መዝገብ ናት፡፡የሰማዩ አምላክ ምሥጢር የሚነገርባት፣ የድኅነት ምሥጢር የሚከናወንባት ስለሆነች መዝገበ ምሥጢር ትባላለች፡፡ ለዚህም የእምነት መሠረት በሆኑት አምስቱ አዕማደ ምሥጢር (ምሥጢረ ሥላሴ፡ ምሥጢረ ሥጋዌ፡ ምሥጢረ ጥምቀት፡ ምሥጢረ ቁርባንና ምሥጢረ ትንሳኤ ሙታን) የጸናች ናትና የምሥጢር መዝገብ መባሏ ተገቢ የሆነ ስያሜ ነው፡፡
ከነዚህ በተጨማሪ ደግሞ ሰባት ምሥጢራት በቤተክርስቲያን ይፈጸማሉ፡፡ እነዚህም ሰባቱ ምሥጢራተ ቤተክርስቲያን ናቸው፡፡ምሥጢራቱም ምሥጢረ ጥምቀት፣ ምሥጢረ ሜሮን፣ ምሥጢረ ቁርባን፣ ምሥጢረ ንስሐ፣ ምሥጢረ ክህነት፣ ምሥጢረ ተክሊልና ምሥጢረ ቀንዲል ናቸው፡፡ እነዚህ ሰባቱ ምሥጢራተ ቤተክርስቲያን በዓይን የማይታዩ በእጅ የማይዳሰሱ ቅዱስ የሆነው የእግዚአብሔር መንፈስ ጸጋ ለምዕመናን የሚታደልባቸው የሚፈጸምባቸው ናቸው፡፡
እነዚህና እነዚህን የመሰሉ ሌሎች ምሥጢራት እያንዳንዳቸው እጅግ ጥልቅ የሆኑ ናቸው፡፡ እነዚህን ምሥጢራት ጠብቃና አስጠብቃ፣ አስተምራና አሳውቃ፣ ፈጽማና ተካፋይ አድርጋ የሰውን ልጅ ለዘላለም ሕይወት የምታበቃ ቤተክርስቲያን መዝገበ ምሥጢር ብትባል ያንስባት ይሆናል እንጂ አይበዛባትም፡፡
- እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን “የድሆች መጠጊያ” ትባላለች፡፡
በቃል ብቻ ያይደለ በተግባር በተገለጠ እውነት እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን የድሆች መጠጊያ ናት፡፡ በዚህ ረገድ ድህነት ብዙ ዘርፍ ሊኖረው ይችላል፡፡ ለማስረጃ ያህል ግን የሚከተሉትን እንመልከት፡፡
የእውቀት ድህነት፡- መንፈሳዊ እውቀትን የተራቡ ወደ ቤተክርስቲያን መጥተው ቃለ እግዚአብሔርን ተምረው ከድህነት ይወጣሉና ቤተክርስቲያን የድሆች መጠጊያ ናት፡፡ እነዚህ ድሆችን መመገብ የመምህራን ድርሻ ነው፡፡
የምግባር ድህነት፡- መልካም ምግባርን የናፈቁና በኃጢአት የተዘፈቁ ወደ ቤተክርስቲያን መጥተው ከእስዋ ተጠግተውና ንስሐ ገብተው ከኃጢአታቸውና ከምግባር ድህነት ይላቀቃሉና ቤተክርስቲያን የድሆች መጠጊያ ናት፡፡ ይህንን አይነት ድህነት መዋጋት የካህናት ድርሻ ነው፡፡
የመንፈስ ድህነት፡- ያላቸውን ትተው ራሳቸውን በመንፈስ ድሀ ያደረጉ ሰዎች በቤተክርስቲያን ሆነው ‹‹በመንፈስ ድሆች የሆኑ ብፁዓን ናቸው፥ መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና።›› እንደተባለ መንግስተ ሰማያትን ይወርሳሉና ቤተክርስቲያን የድሆች መጠጊያ ናት፡፡
ሥጋዊ ድህነት፡- በዚች ምድር ላይ ሲኖሩ ምግበ ሥጋን የተራቡ፣ ቀዝቃዛ ውኃ አጥተው የተጠሙ፣ እራፊ ጨርቅ አጥተው የታረዙ ሰዎች ወደ ቤተክርስቲያን ተጠግተው ጊዜያዊና ዘላቂ ድጋፍ ያገኛሉና ቤተክርስቲያን የድሆች መጠጊያ ናት፡፡ እነዚህን መርዳት የሁሉም ሕዘበ ክርስቲያን ድርሻ ነው፡፡ ነገር ግን ቤተክርስቲያን የድሆች እንጂ የድህነት መጠጊያ አይደለችም፡፡
- እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን “ተጋዳይዋና ድል አድራጊዋ” ትባላለች፡፡
ቤተ ክርስቲያን ስንል የዚህ ዓለም ተጋድሏቸውን በድል አጠናቅቀው ወደ እግዚአብሔር የሄዱ ቅዱሳን (ሐዋርያት፣ ሰማዕታት፣ ሊቃውንት፣ …) እና ገና በዚህ ዓለም በተጋድሎ ላይ ያሉት የምእመናን አንድነት (ጉባኤ) ናት፡፡ በሰማይ ያለችው ቤተክርስቲያን (ጉባኤ) የዚህን ዓለም ውጣ ውረድ ጨርሰው የሄዱ፣ ድል አድርገው የድል አክሊላቸውን ለመቀበል እርሱ የወሰነውን ጊዜ የሚጠባበቁ ቅዱሳን ኅብረት ስለሆነች አትናወጽም፤ ስለሆነም ሊቃውንት ይህችን ቤተ ክርስቲያን ድል አድራጊዋ ቤተክርስቲያን (Church Triumphant) ይሏታል፡፡ ገና በዚህ ዓለም በጉዞና በፈተና ላይ ያለችውን የአንዲቷ ቤተክርስቲያን አካል የሆነችውን ጉባኤ (ቤተ ክርስቲያን) ደግሞ ገና በተጋድሎ ላይ ያለች ቤተክርስቲያን (Church Militant) ይሏታል፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ «ሰውን ብትታገል ብትዋጋ ታሸንፈዋለህ ወይም ያሸንፍሃል ቤተክርስቲያንን ግን ለማሸነፍ አይቻልም ቤተክርስቱያን ሁል ጊዜ ትዋጋለች ተሸንፋ ግን አታውቅም ዲያብሎስ ዝናሩን አራገፈ ቀስቱን ጨረሰ፡፡ ቤተክርስቲያንን ግን አልጎዳትም» እንዳለው በዚህ ዓለም ያለችው ቤተክርስቲያን ሐዋርያት በባሕር ላይ በታንኳ እየሄዱ ሳለ ጌታችን አብሯቸው በመካከላቸውና በታንኳው ውስጥ እያለ፣ ነገር ግን በኃይለኛ ማዕበል ትናወጥ እንደ ነበረችው ታንኳ በተለያዩ ፈተናዎች ትናወጻለች፡፡ አንዳንድ ጊዜም በውስጧ ያለው ጌታ የማይሰማና የተዋት፣ መከራዋን እያየ ዝም ያላት፣ ባለቤት የሌላት እስክትመስል ድረስ በውስጧ ያሉና በተለያዩ ነገሮች ተጨንቀው የሚያማርሩና የሚያዝኑ ልጆቿም ሰሚ የሌላቸው የሙት ልጆች እስኪመስሉ ድረስ ባለቤቷ ኢየሱስ ክርስቶስ ዝም ይላል፡፡ ሐዋርያትንም “ስንጠፋ አይገድህምን?” እስኪሉ ያደረሳቸው ይህ ነበር፡፡ ማቴ. 8፡23-27
ቅድስት ቤተክርስቲያን የባለቤቷ የኢየሱስ ክርስቶስ ሙሽራ ስለሆነች ጠባቂዋና ተንከባካቢዋ እርሱ ራሱ ነው፡፡ ምንም እንኳ እርሱ በሚያውቀውና በተለያዩ ምክንያቶች እንድትፈተን ቢፈቅድም እንድትጠፋ ግን አይተዋትም፡፡ ይህ ማለት ግን በውስጧ ያሉ አባላት በጥርጥርና በልዩ ልዩ ፈተናዎች አይሰናከሉም ማለት ግን አይደለም፡፡ ምንም ቢሆን ግን ቤተ ክርስቲያን የራሱ የክርስቶስ አካሉ እንደ መሆኗ ራሷ የሆነ እርሱ ለአካሉ ለምእመናን የሚያስፈልገውን ያውቃል፣ ያዘጋጃል፣ ይሰጣል፡፡
ቃለ ሂዎት ያሰማልን፣ተስፋመንግስተ ሰማያትን ያውርስልን።
LikeLike