በዲ/ን ብሩክ ደሳለኝ
“መመካት ቢያስፈልግ ዓለምን የሚያስደምመው የያሬዳዊ ዜማ ለኢትዮጵያውያን ትምክህት ነው፡፡”
መንፈሳዊ መዝሙር ቤተክርስቲያን ለልጆቿ ከምታወርሳቸው ሀብታት አንዱ ሲሆን ለአምልኮትም ታላቅ ድርሻ ያለው ነው:: መዝሙር ቅዱሳን ሊቃነ መላእክትና ሰራዊቶቻቸው ፈጣሪያቸው እግዚአብሔርን ያለዕረፍት የሚያመሰግኑበት ነው (ኢሳ ፮:፩-፭ ኢዮ ፴፰:፮):: መዝሙር ሰውና መላእክት ዘወትር ቀንና ሌሊት እግዚአብሔርን ለማመስገን እንደተፈጠሩ እንዲያመሰግኑበትም የተሰጣቸው ልዩ ሀብት፣ ሰማያዊ ዜማ ነው:: አስተምህሮ ባለፉት ሳምንታት ወቅቱን አገናዝባ ለሐዋርያት የተሰጣቸውን ጸጋ መንፈስ ቅዱስ እንዳስገነዘበችን በዚህ ዓምድ ደግሞ ለኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የተሰጣትን ሰማያዊ የምስጋና ስጦታ የሆነውን የመዝሙር ሥርዓትን ኦርቶዶክሳዊያን ምእመናንና እና አገልጋዮች እንዲረዱት በጥቂቱ እናቀርባለን::
እስራኤላውያን ከጥንት ጀምሮ ከጸሎትና መጽሐፍትን ከማንበብ ጋር መዝሙር በመዘመር እግዚአብሔርን እንደሚያመልኩ እንዲሁም በመከራቸው ጊዜና ከድል በኋላ እግዚአብሔር ያደረገላቸውን አስበው በመዝሙር ምስጋናን ያቀርቡ እንደነበር ቅዱሳት መጻሕፍት ይነግሩናል (ዘጸ ፲፭:፩-፳ ዘዳ ፴:፲፱ ፴፩:፲፬ ኢሳ ፩:፪ መሳ ፬:፩ መሳ ፭:፫):: በሐዲስ ኪዳንም በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ከነበሩት ድንቅ መንፈሳዊ ገጽታዎች ቀዳሚውና ዋናው በምስጋና ለዘመናት ተለያይተው የነበሩ ሰውና መላእክት “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ሥምረቱ:- ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ” በሚል በአንድነት ባቀረቡት የምስጋና መዝሙር ነው (ሉቃ ፪:፲፪):: መምህራችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሐዋርያቱ ጋር ወደ ደብረዘይት ከመውጣታቸው በፊት መዝሙርን አስተምሯቸዋል፤ ዘምረዋልም (ማር ፲፬:፳፮):: ስለዚህም የመዝሙር አገልግሎት በቤተ ክርስቲያን ከጸሎት ከስግደት ከጾም ጋር በሥርዓተ አምልኮታችን ውስጥ ትልቅ ድርሻ አለው::
፩.መንፈሳዊ መዝሙር ምንነቱና ጥቅሙ
መዝሙር ‘ዘመረ’ ‘አመሰገነ’ ከሚለው የግእዝ ቃል የወጣ ሲሆን ትርጉሙም ምስጋና፣ ልመና፣ ማዜም ማለት ነው፡፡ መዝሙር በግልና በኅብረት የሚዘመር፤ ጌታችን ሰውና መላእክት በአንድነት እንደዘመሩ ታናሽ ታላቅ ሳይል ሁሉንም የሚያሳትፍ፤ ዝማሬውም በልዑል እግዚአብሔር ፊት ቆመን አምላካችንን የምናመሰግንበት የምናወድስበት በቁመታችንም ከቅዱሳን መላእክት ጋር የሚያመሳስለን መንፈሳዊ ተግባር ነው (ራዕ ፲፱:፭፣ ፩ቆሮ ፲፬:፪፮):: መዝሙር ለክርስቲያን የዘወትር ተግባር እንደመሆኑ ከቅዱሳት መጻሕፍት መሠረትነት ጥቂቶችን ምሳሌ አድርገን እንማራለን::
መንፈሳዊ መዝሙር እግዚአብሔርን በቅኔ በሚያምር ዜማ የምናመሰግንበት ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለኤፌሶን ሰዎች በላከው መልእክቱ “በመዝሙርና በዝማሬ በመንፈሳዊም ቅኔ እርስ በርሳችሁ ተነጋገሩ፤ ለጌታ በልባችሁ ተቀኙና ዘምሩ” እንዳለ በዚህ የመንፈሳዊ ተግባር እግዚአብሔርን በቅኔ በሚያምር ዜማ እናመሰግነዋለን፤ እናወድሰዋለን (ኤፌ ፭:፲፰-፳):: ቅዱሳን መላእክትም በቤተልሔም በጌታችን ልደት በደስታ እንዳመሰገኑ፣ ትንሣኤውን በምስጋና እንዳበሰሩ፣ ዕርገቱን በምስጋና እንዳጀቡ፣ ዳግም ምጽአቱንም በምስጋና እንደሚያውጁ ሁሉ የክርስቶስ አካል የሆነችውን ቤተክርስቲያንን ያለማቋረጥ ያገለግሏታል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ክቡር ዳዊት “ዘምሩ ለአምላካችን ዘምሩ: ዘምሩ ለንጉሣችን ዘምሩ እግዚአብሔር ለምድር ሁሉ ንጉሥ ነውና” እንዳለ እኛም እንደቀደሙት አባቶች እግዚአብሔር ለኛ ያደረገውን እያሰብን ዘወትር ቀንና ሌሊት በመዝሙር እናመሰግነዋለን:: (መዝ ፵፮:፮-፯)::
መንፈሳዊ መዝሙር የሚያበረታንና የሚያጸናን መንፈሳዊ ኃይል ነው፡፡ መዝሙር በሃይማኖት መከራ ድካም ሲገጥመን ከድካማችን የሚያበረታን፣ መከራን እንዳንሰቀቅ እንዳንፈራ የሚያጸናን የሚያበረታን መንፈሳዊ ኃይል ነው:: ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስና ሲላስ በእስር ሳሉ በጸሎት ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔርን በዝማሬም ያመሰግኑ ነበር (የሐዋ ሥራ ፲፮:፳፭):: ዛሬ ላይ በሕይወታችን፣ በቤተክርስቲያን አገልግሎት ፈተና ሲገጥም በራሳችን ጥበብ በመታለል ሳይሆን ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን ትግላችን ከሥጋና ከደም ጋር ሳይሆን ከሰይጣንና ከሠራዊቱ ጋር ስለሆነ ምድራዊ የሆነ የእግዚአብሔር ሰልፍ በማድረግ በዝማሬ የእግዚአብሔርን ኃያልነት በመግለጥ ሊሆን ይገባል:: በመዝሙር “በተጨነቅሁ ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ጮኽሁ፥ ሰማኝም።” (መዝ ፻፲፱:፩) እንደሚል፥ ረሃብ ቸነፈር ጦርነት የተፈጥሮ አደጋዎች መንግስት በመንግስት ሕዝብም በሕዝብ ላይ ክፋትን ሲያደርግ በማመስገን የእግዚአብሔር የመከራው ጊዜ እንዲያበቃ እንዲያጥር እንደ ነቢያትና ሐዋርያት ሕይወትም በመዝሙር ወደ እግዚአብሔር መጮህ ለክርስትያኖች የእግዚአብሔርን ኃያልነት የመመስከር እንዲሁም ሐዋርያትን የመምሰልም መገለጫ ነው::
መንፈሳዊ መዝሙር እግዚአብሔር ለእኛ ስላደረገው ሁሉ ደስታችንን የምንገልጽበት ነው:: ‘ደስ የሚለውም ማንም ቢኖር እርሱ ይዘምር’ እንዲል (ያዕ ፭: ፲፫):: በመከራና በችግራችን ወቅት ስሙን ጠርተን የለመነውን አምላክ በድልና በደስታችን ጊዜ አብዝተን ልንዘምር እንጂ ልንዘነጋ አይገባም:: እስራኤል በግብፅ ከነበረው መከራ ሲወጡ የአምላክን ታዳጊነት የእስራኤልን ድኅነት በመመልከት ሙሴና ተከታዮቹ በተለይም እኀቱ ማርያም በከበሮ ድምፅ እየታጀቡ በጣዕመ ዜማ “ንሴብሆ ለእግዚአብሔር ስቡሐ ዘተሰብሐ:-በክብር ከፍ ከፍ ብሎአልና ለእግዚአብሔር እዘምራለሁ ፈረሱንና ፈረሰኛውን በባሕር ጣለ” በማለት ዝማሬን አቅርበዋል (ዘጸ ፪:፩-፲):: ዛሬም በሰርግ በበዓላት በድል ወቅት የቅዱሳንን ተጋድሎና ህይወታቸውን እያሰቡ እግዚአብሔር ለእኛ ያደረገውን እያደነቅን በሚያምር ለምስጋና በተለየ የዜማ ስልት መዘመር ይገባል::
፪. ኦርቶዶክሳዊ መዝሙርና መገለጫዎቹ
ቅዱሳን አባቶቻችን የሕይወት መስዋዕትን ከከፈሉባቸው አንዱ ትልቁ ርስት ዜማና የዜማ ሥርዓት ነው፡፡ የቀደሙት አባቶች እኛ ኦርቶዶክሳውያን እንድናከብረው የወሰኑልንን የዝማሬ ሥርዓት ድንበር ሳናፈርስ መንፈሳዊ ዜማና ሥርዓቱን አባቶቻችን ከእግዚአብሔር እንደተቀበሉ በዚህም ምስጋና ከእርሱ ጋር እንደተገናኙ እኛም “በነቢያትና በሐዋርያ መሠረት ላይ ታንጻችኋል” እንደተባልን ከቀደምት አባቶች መሰረት ሳንለቅ ሠርተው ባስረከቡን ወደ ሰማያዊው ኅብረት በምንነጠቅበት የዜማ ሥርዓት ልንጸና ይገባል (ኤፌ ፪:፳ ምሳ ፳፪:፳፰)፡፡
ከቀድሞ ጀምሮ እግዚአብሔር አምላክ እውነተኛይቱን ሃይማኖት ባጸኑ በነቢያት በሐዋርያት ላይ እያደረ ምስጢርን ገልጾላቸዋል:: በአስተምህሮ ባለፉት ሳምንታት መልዕክት እንደተማርነው ሐዋርያት የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ከተቀበሉ በኋላ የተሰወረው ተገልጦላቸው ፍጹም የሆነውን አገልግሎት ጀምረዋል:: የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያንም ይህንን ሐዋርያዊ አስተምህሮ ትውፊትና ባህል ተቀብላ በታላቁ ሊቅ በቅዱስ ያሬድ አማካኝነት ከእግዚአብሔር በተሰጣት ልዩ የዝማሬ ጸጋ ታመሰግናለች::
ቅዱስ ያሬድ ይህን ታላቅ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ከመቀበሉ በፊት በትምህርቱ ተስፋ ቆርጦ፤ እግዚአብሔርም ከስነ ፍጥረት እንዲማር አድርጎት፤ ቅዱስ ያሬድም ራሱን ገስጾ ድካምን እንዲታገስ እውቀትንና ጥበብን እንዲገልጽለት ወደ እግዚአብሔር ከጸለየ በኋላ፤ ጌታችን “የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል” (ዮሐ ፲፮:፲፫) ብሎ እንዳስተማረን በሰው ጥበብ መረዳት የማይቻለውን በአንድ ቀን መዝሙረ ዳዊትን የጸሎት መጻሕፍትንና ትርጓሜ መጻሕፍት ብሉያትና ሐዲሳትን ማወቅ ተሰጠው:: የእግዚአብሔርን የጸጋ ስጦታ ለመቀበል የሰው ልጅ በአቅሙ መጣር እንዳለበት ከሚያስተምሩን ህያው ምስክሮች አንዱ አባታችን ቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ ሰማያዊ ዜማ የተገለጠለት ሳይጥር፣ ሳይደክም አልነበረም፡፡ ሰባት ጊዜ እየወደቀ እየተነሳ፣ በእግዚአብሔር ኃይል እየታገዘ ለበለጠው የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ የተገባ ሆነ እንጂ፡፡ ቅዱስ ያሬድ እግዚአብሔር ፈቃዱ ሁኖ ካህናተ ሰማይ መላእክት በተቀደሰ ዙፋኑ ዙሪያ ከፍ ባለ ዜማ የሚያመሰግኑበትን የዜማ ሀብት የተሰጠው የቤተክርስቲያን ዓምድ ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ በተመስጦ ማኅሌተ እግዚአብሔርን ሲያደርስ ንጉሥ ገብረ መስቀል በጣዕመ ዜማው ስለተሳቡ የብረት ዘንጉን በቅዱስ ያሬድ እግር ላይ መትከላቸውና ቅዱስ ያሬድም ከእግሩም ደም መፍሰሱን ማሕሌቱ እስከሚፈጽም ድረስ አልተሰማውም ነበር፡፡ ይህም ጣዕም ያለው ሰማያዊ የዜማ ስልት ቤተክርስቲያን ዘወትር ጧትና ማታ በስብሐትና በማኅሌት በቅኔ በሰርክ የምታመሰግንበት ነው::
ሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ (ሱራፌል) የብርሃን መስቀልና ማዕጠንተ ወርቅ ይዘው በመንበሩ ፊት ቆመው እንደሚያመሰግኑት ቅዱስ ያሬድ በምስጋናው ልዑል እግዚአብሔርን ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እያለ በማመስገኑ ምስጋናውንም የተማረው ከመላእክት መሆኑን በድርሰቱ መስክሯል፡፡ በዚሁም ቤተ ክርስቲያን “አምሳሊሆሙ ለሱራፌል”:- የሱራፌል አምሳላቸው ትለዋለች፡፡ ቅዱስ ያሬድ ሃልዎተ እግዚአብሔርን ፍጥረተ ዓለምን በአጠቃላይ መሠረተ ሃይማኖትን ነገረ ድኅነትን ክብረ ቅዱሳንን መሠረት አድርጐ በሦስት የዜማ ስልቶች (ግዕዝ፣ዕዝልና አራራይ) ላይ ተመሥርቶ ዘምሯል:: ምድራውያን ካህናት ሰማያውያኑን መስለው ማዕጠንትና መስቀል ይዘው በምስጋና በመንበሩ ፊት ቆመው ማመስገናቸው ይህን መንፈሳዊ ጸጋ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ከእግዚአብሔር እንደተቀበለችና ይህንንም ስጦታ በክብር እንደጠበቀችው ያስገነዝበናል:: የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ተለይታ ከምትታወቅባቸው እና ለኢትዮጵያም ካበረከተቻቸው እሴቶች አንዱ ይህ የዜማ ስጦታ ነው። መመካት ቢያስፈልግ ዓለምን የሚያስደምመው የያሬዳዊ ዜማ ለኢትዮጵያውያን ትምክህት ነው፡፡
አንድን መዝሙር ኦርቶዶክሳዊ ነው የሚያሰኙት የመዝሙሩ መልእክት ፣ የዜማ ስልቱ፣ የዜማው መሳሪያ፣ እንዲሁም ዝማሬውን የምናቀርብበት መልክ ሥርዓቱን ጠብቆ መንፈሳዊነትን ተላብሶ የተገኘ ሲሆን ነው::
፪.፩. የመዝሙሩ መልዕክት
የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን አስተምህሮ የጠበቀ መሆን ይኖርበታል፡፡
አንድን መዝሙር ኦርቶዶክሳዊና ልብን የሚመስጥ ነው የምንለው ሌላው እይታ የመዝሙሩ ግጥም መሠረተ ሃይማኖትንና ምስጢርን የጠነቀቀ፤ የቤተክርስቲያንን ሥርዓት ትውፊትና ባህል የጠበቀ ሲሆን ነው፡፡ ለእግዚአብሔር የሚቀርበውን የምስጋና መስዋዕት በተዋጣለት ድርሰትና ዜማ በነግስና በመልክ ጸሎት እንዳለው በግጥም መልክ መልእክቱንም የተከተለ በምስጢርም የጠለቀ እንዲሆንና ይበልጥ ደግሞ በቅኔ መንገድ ቢቀርብ የበለጠ ይስማማል:: እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነታችን ሁላችን የመዝሙርን መልእክት መመርመር ይገባናል፡፡ መዝሙር ምስጋና ብቻ ሳይሆን ትምህርትም ስለሆነ ትርጉሙም ከቤተክርስቲያን ትምህርት ጋር የማይቃረን እንዲሁም ግጥሙ እንደ ሰምና ወርቅ ምስጢርን ጠብቆ የተቀመመ መሆኑን ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡ ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ያሬድ በቅዱሳት መጻሕፍት የብሉያትንና ሐዲሳትን ምስጢር ጠንቅቆ የተረዳ ስለነበር በዜማ ድርሰቱም ቤተክርስቲያንን በምስጋና ያስጌጠ ዛሬም ላይ ላለው አገልግሎት መንፈሳዊ ተመስጦን የሚያላብስ እንዲሁም ሲሰሙት አጥንትን የሚያለመልም ነው::
በተጨማሪም ቤተክርስቲያናችን እምነቷን የምትገልጽበት ስያሜዎችን የምትሰጥበት በዘመን የማይተኩ መሰረቷን የሚያስገነዝቡ ዕንቁ የሆኑ ቃላትና አገላለጽ አላት:: ዛሬ ላይ በካሴት ተቀርጸው መዝሙር ተብለው በሚወጡ ነገር ግን ፈር የለቀቁ ከቤተክርስቲያን አገላለጽ የወጡ ሥም አጠራሩ የከበረ አምላካችንንና ያከበራቸው ቅዱሳንን ክብር የሚነኩ ወይም የሚያሳንሱ መዝሙሮች ይሰማሉ:: ለምሳሌ በዘወትር ጸሎት መግቢያ ላይ እንደምናየው ቤተክርስቲያን ለጌታችን መጠሪያ እንደቀደምት አበው “የአምላኮች አምላክ የጌቶች ጌታ የንጉሦች ንጉሥ” እንላለን እንጂ ይህን ኦርቶዶክሳዊ አጠራርን ትተን ክብርን በሚያሳንስ አጠራር አትጠራውም፡፡ በሌላውም የዝማሬው መልእክት ተስፋ መቁረጥን፤ ምድራዊ ተስፋን፤ ሥጋዊ ድልን በማሰብ የሚደርሱ ናቸው:: እነዚህ ድርሰቶች አስተማሪነት የሌላቸውና የክርስትናን ዓላማ ፈጽሞ ካለመረዳት የቀረቡ ናቸው:: ንዋየ ኅሩይ ቅዱስ ጳውሎስም “ፊደል ይገድላል መንፈስ ግን ሕይወትን ይሰጣል” ብሎ እንዳስተማረን የዝማሬያችን መልእክት ምስጢርን የጠነቀቀ እንጂ በጥሬ ንባብ ብቻ የቀረበ እንዳይሆን ማጤን ያስፈልጋል (፪ቆሮ ፫:፮)::
፪.፪. የዜማው ስልት
የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ያሬዳዊ የዜማ ስልት የተከተለ መሆን ይጠበቅበታል፡፡
በየጊዜው የተነሡ የቅድስት ቤተክርስቲያናችን አባቶች ለመዝሙር ይገለገሉበት የነበረው የዜማ ስልት የቅዱስ ያሬድ ዜማ ነው፡፡ ለምሳሌ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫን ድርሰት ብንመለከት ሰዓታቱን እግዚአብሔር ወዶ ፈቅዶ የሰጠንን ስጦታ በመጠቀም በያሬዳዊ ዜማ ዘመሩት እንጂ ሌላ ዜማ ለመፍጠር አላስፈለገም:: በመሰረታዊው የጸሎት ስርዓት ቤተክርስቲያን ወቅቱን ያገናዘበ የዜማ ስልት ተከትላ እግዚአብሔርን ታመሰግናለች:: በቅዳሴ ሥርዓት በጾም ወራት በግእዝ የዜማ ስልት እንዲሁም በበዓላት ጊዜ በዕዝል የዜማ ስልት ይከናወናል፡፡ በዚሁም መሠረትነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ለሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ባወጣው ደንብ መሰረት መዝሙራት እግዚአብሔር ለቤተክርስቲያን በቅዱስ ያሬድ አማካኝነት የሰጣትን የዜማ ስልት የተከተሉ እንዲሆን ደንግጓል፡፡ በአጠቃላይ የያሬድ ዜማዎች በምንዘምረው መዝሙር ላይ እንዲውል እንደ አባቶቻችን የድርሻችንን ልንወጣ ይገባል::
፪.፫. የዜማ መሳሪያዎች:
በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የተፈቀዱ የዜማ መሣሪያዎችን የሚጠቀም መሆን ይጠበቅበታል፡፡
እግዚአብሔር ልዩ መስዋዕትን ይፈልጋል፡፡ መዝሙርም ከልብ የሚቀርብ መስዋዕት እንጂ በቁሳቁስ የሚገለጥ አይደለም፡፡ ይሁንና መንፈሳዊ አገልግሎትን ለማስፋት የዜማ መሳሪያዎችን መጠቀም ዓላማውን እስከጠበቀ ድረስ ከመንፈሳዊ መስመር አያስወጣንም፣ በቅዱሳት መጻሕፍት መሰረትነትም የተመሰከረ ነው፡፡ ለኦርቶዶክሳዊ መዝሙር የምንጠቀምባቸው መሳሪያዎች መንፈሳዊ ትርጉም ያላቸው፣ ለመንፈስ ቅዱስ አገልግሎት የተመረጡ ናቸው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት በመዝሙሩ (መዝ ፹፩:፪) “ዝማሬውን አንሡ ከበሮንም ስጡ፥ ደስ የሚያሰኘውን በገና ከመሰንቆ ጋር” በማለት ለምስጋና የሚስማሙ የዜማ መሣሪያዎች እንዳሉ ያስረዳናል:: ቅዱስ ያሬድ ዜማን ከመላእክት እንደተማረ እንዲሁም በርካታ ሊቃውንትም ይህንን ሰማያዊ ዝማሬ መሰረት ያደረገ የዜማ መሣሪያዎች እንደተጠቀሙ የቤተክርስቲያን ትውፊት ያስተምረናል:: እነዚህም የመዝሙር መሳሪያዎች ኢትዮጵያዊ መልክ ያላቸውና መጽሐፍ ቅዱስን መሰረት ያደረጉ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ከበሮ መቋሚያ እና ጸናጽል የማህሌት መሳርያዎች ናቸው:: ቅዱስ ሲኖዶስ በ ፲፱፻፹፮ ዓ.ም በግንቦት ወር ላይ ባደረገው ጉባዔ መዝሙር በዋሽንት በከበሮ በጸናጽል በመሰንቆ በበገና በእምቢልታ እንድንገለገል አዟል::
እነዚህ የዜማ መሳሪያዎች ገድል የተሰራባቸው ገቢረ ተአምር የተፈጸሙባቸው ስለሆኑ የተቀደሱ ንዋያተ ማህሌት መሆናቸውን አውቀን በክብር በንጽህና ልንጠብቃቸው ይገባል:: ይህም የምስጋና የማህሌት መሳሪያ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረትነት ያለው ነው:: “መዘምራንም የነበሩት ሌዋውያን ሁሉ አሳፍና ኤማን ኤዶታምም ልጆቻቸውም ወንድሞቻቸውም ጥሩ በፍታ ለብሰው ጸናጽልና በገና መሰንቆም እየመቱ በመሠዊያው አጠገብ በምሥራቅ በኩል ቆመው ነበር ከእነርሱም ጋር መቶ ሀያ ካህናት መለከት ይነፉ ነበር። ካህናቱም ከመቅደሱ በወጡ ጊዜ መለከቱንም የሚነፉ መዘምራኑም በአንድነት ሆነው እግዚአብሔርን እያመሰገኑና እያከበሩ እግዚአብሔር ቸር ነውና ምሕረቱም ለዘላለም ነውና እግዚአብሔርን አመስግኑ እያሉ በአንድ ቃል ድምፃቸውን ወደ ላይ ከፍ አድገው በመለከትና በጸናጽል በዜማም ዕቃ ሁሉ እግዚአብሔርን ባመሰገኑ ጊዜ ደመናው የእግዚአብሔርን ቤት ሞላው” (፪ዜና ፭:፲፪-፲፬ ፪ዜና ፳:፩-፴)። ስለዚህ ይህን መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሰረት ያለውን የዜማ መሣሪያዎች ወደ ውጭ አውጥቶ ለሥጋዊ ጥቅም ማዋል ስለሚያስነቅፍ በተለያዩ መድረኮችም እነዚህን የቤተክርስቲያን የሆኑትን ንዋያት ቦታው በሚፈቅደው ሕግ ልናስከብር ይገባል /ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፩ ረስጣ ፳፰/::
፪.፬. የአዘማመር ሥርዓት
የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ሥርዓትና ትውፊት የጠበቀ መሆን ይኖርበታል፡፡
እግዚአብሔር ትሁትና የዋህ በሆነ በተሰበረ ልብ የሚቀርብን የምስጋና መስዋዕት ይመለከታል:: ቃየልና አቤል በእግዚአብሔር ፊት መስዋዕትን እንዳቀረቡ እግዚአብሔርም ወደ አቤልና መስዋዕቱ እንደተመለከተ ይነግረናል እንጂ መስዋዕቱን ብቻ አላለንም እኛም የከንፈራችንን ፍሬ በመዝሙር በተመስጦ በተሰበረ ልብ ሆነን ከማን ፊት ለማን ምስጋና እንደምናቀርብ በመገንዘብ በመዘመር ወቅት መዘመራችንን ብቻ ሳይሆን የእኛን ልብ የሚመረምር አምላክ ፊት እንደቆምን ልናስተውል ይገባል (ዘፍ ፬:፬):: ክቡር ዳዊት ‘እዘምራለሁ ንጹሕ መንገዱንም አስተውላለሁ” (መዝ ፻:፪) እንዳለ እግዚአብሔር ከዜማው በፊት የሚያዜመውን ሰው ሕይወት ይፈልጋልና እንዲሁም ቅዱስ ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ በላከው መልእክት “በስፍራ ሁሉ አለ ቍጣና አለ ክፉ አሳብ የተቀደሱትን እጆች እያነሱ እንዲጸልዩ እፈቅዳለሁ” (፩ጢሞ ፪:፰) በማለት የእግዚአብሔርን ፈቃድ ያስተምረናል::
ስንዘምርም የምንዘምረውን አውቀን ዜማውን ብቻ ሳይሆን ቃሉን በማስተዋል የመዝሙሩን ባለቤት ልዑል እግዚአብሔር መዝሙሩን በአንደበታችን እንዳኖረልን ተገንዝበን ራሳችንን ልንመክርበት ልንገስጽበት መሆን አለበት:: መዝሙሩም የምእመናንን ልብ በዝማሬው ለቃለ እግዚአብሔር የለሰለሰ እንዲሆን የሚያዘጋጅ መሆን አለበት:: ዝማሬያችን በአንዳንድ ቦታዎች እንደሚታየው ከቤተ ክርስቲያን ባልተለመደ ሥርዓት ዓይንን ጨፍኖ እጅን ያለሥርዓት በማወዛወዝ በሥጋዊ ስሜት የሚቀርብ ወይም ባህላዊ ዘፈንን በሚመስል መልኩ ሳይሆን ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት እንደተናገረው ‘አቤቱ አይኖቻችንን ወደ አንተ አቀናን’ እንዳለው አሰላለፋችንና እንቅስቃሴያችን እግዚአብሔር የሥርዓት አምላክ መሆኑን በመረዳት ወንጌልን የሚሰብክ በአገባብና በሥርዓት ሊሆን ይገባል (መዝ ፻፵፪:፮ መዝ ፭:፫ ፩ቆሮ ፲፬:፵)::
ከዚህ በተጨማሪም የዘማርያንም ሕይወት የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን እምነትና ምግባር የሚሰብክ መሆን ይኖርበታል፡፡ ከመዝሙሩ መልእክት፣ የዜማ ስልት፣ የዜማ መሣርያና የአዘማመር ሥርዓቱ ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ፣ ሥርዓትና ትውፊትን የጠበቀ ከመሆኑ ተጨማሪ የዘማርያኑ ሕይወትም እንዲሁ የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን እምነትና ምግባር የሚሰብክ መሆን ይጠበቅበታል፡፡ መዝሙር የተወደደ መስዋዕት ስለሆነ መስዋዕቱን ከማቅረብ አስቀድሞ ራስን ማዘጋጀት ይገባል መስዋዕቱም እንዲሰምር ከዝማሬ መስዋዕት በፊት የራስን ሕይወት በመመርመር የምስጋናው ባለቤት በልዑል እግዚአብሔር ፊት እንደሚቀርብ አውቆ በትህትና በመልካም ሕይወት ማቅረብ ያስመሰግናል፡፡
ማጠቃለያ
አምልኮተ እግዚአብሔርን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለመፈጸም የቤተክርስቲያንን ሥርዓት መማር ማወቅ ይኖርብናል:: መንፈሳዊ ዜማ ከእግዚአብሔር የተሰጠን ይህም በመላእክቱ የሚደርስ ከሥጋዊ ስሜት ያልሆነ ልዩ የዜማ ስልት ያለው ማለት ነው:: ለኢትዮጵያውያን ይህ መንፈሳዊ ስጦታ በታላቁ ሊቅ በቅዱስ ያሬድ አማካኝነት የተሰጠንና ይህም ስጦታችን ልዩ የዜማ ስልትና ምልክት ያለው ዜማ ነው፡፡ በዚህ ዜማ ልብን በሚማርከው መንፈስን በሚቀድሰው ዜማ እግዚአብሔርን እናመሰግናለን እናወድሳለን፡፡ ከዚህ ጋር አያይዘን የምንማረው ለኢይዝራኤላዊው ናቡቴ ንጉሡ አክዓብ የአባቶቹን ርስት ወስዶ ሌላ ርስት ልስጥህ የሚል ጥያቄን አቅርቦለት ነበር:: ናቡቴ ግን የአባቶቹን ርስት ከመሸጥ ሞትን ነበር የመረጠው:: ናቡቴ ለዚህ ምድራዊ ርስት ይህን መስዋዕት ከከፈለ ዛሬ ላይ ሰማያዊ የሆነውን ስጦታ ቀደምት አባቶች መስዋዕት የሆኑለትን ይህን ሥርዓት ምድራዊ በሆነ አመክንዮ ዜማን ከንግድ ጋር ማያያዝ ለሥጋ በሚመች ስልት በሚቀርብ ፍጹም ኦርቶዶክሳዊ ባህል ካልሆነ አገልግሎት ተጠብቀን አባቶቻችን እንደተቀደሱበት ከመላእክቱ ጋር በምስጋና እንደተባበሩ እኛም ተባብረን በምስጋና ሥርዓታችን ከኦርቶዶክሳዊ አገልግሎት ሳንወጣ ዋጋ የምናገኝበት ሊሆን ይገባል:: የምንዘምረው መዝሙር በቤተክርስቲያኒቱ ሊቃውንት አባቶች እንዲሁም መምህራን የታረመ ሊሆን ይገባል:: የቤተክርስቲያን መዝሙር የዜማው ባሕልና መሣሪያዎቹ ፍፁም መንፈሳዊ መልእክት ያለው ነውና ይህንንም ታላቅ የሃይማኖት አደራ ጠብቀን ለቀጣዩ ትውልድ ማስረከብ ይጠበቅብናል፡፡
ማኅበረ መላእክት ያለማቋረጥ በትጋት እግዚአብሔርን ያለእረፍት በደስታ እንደሚያመሰግኑ እኛም ረድዔታቸውን እየተማጸንን ሰማያዊ በሆነው የዝማሬ ምስጋና እንድንተጋ ልዑል እግዚአብሔር ይርዳን።
ክፍል ፪ ይቀጥላል፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
Pingback: ዘማሪ ማስመጣት፡ በሐዋርያዊ ጉዞ ላይ የዘማርያን ሚና – አስተምህሮ