ኦርቶዶክሳዊ መዝሙር፡ ርስታችንን አጥብቀን እንያዝ (ክፍል ፪)

Digua

በዲ/ን ብሩክ ደሳለኝ

በመጀመሪያው የኦርቶዶክሳዊ መዝሙር ጦማር ስለ ኦርቶዶክሳዊ መዝሙር ምንነት፣ ጥቅምና ሥርዓት አይተናል፡፡ በዚያም ክፍል  በተለይም የኦርቶዶክሳዊ መዝሙር መልእክት (ግጥም)፣ የዜማ ስልት፣ የዜማ መሣርያ አጠቃቀምና የአዘማመር ሥርዓት ምን መምሰል እንዳለበት በሰፊው አቅርበናል፡፡ የዚሁ ርዕስ  ቀጣይና ሁለተኛው ክፍል በሆነው ጦማር ደግሞ  ምእመናን የኦርቶዶክሳዊ መዝሙር ሥርዓትን ለመጠበቅ የድርሻቸውን እንዲወጡ ይረዳ ዘንድ በወቅቱ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ስም በካሴት የሚቀረጹ እና የሚዘመሩ በአማርኛ ቋንቋ የሚቀርቡ  መዝሙራትን እየቃኘን  ከመዝሙር ግጥም (መልእክት)ጋር የተያያዙ ችግሮችንና መፍትሔዎቻቸውን በአጭሩ ለማየት እንሞክራለን፡፡

ባለፉት ሦስት አሰርት ዓመታት ውስጥ የአማርኛ መዝሙራት መልካም ዕድገትን ቢያሳዩም ከዕድገታቸው ጋር ተያይዘው የመጡና ትኩረትን የሚሹ አንዳንድ ችግሮች መኖራቸው ግን የአደባባይ ሐቅ ነው፡፡ ከመዝሙር መልእክት (ግጥም) አንጻር በአንዳንድ መዝሙራት የሚታየው ችግር ብዙ መልክ ቢኖረውም በሁለት ከፍሎ ማየት ይቻላል፡፡ የመጀመሪያው ችግር የግጥሙ መልእክት መዛባት (ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮን፣ ሥርዓትንና ትውፉትን አለመጠበቅ) ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የኪነ-ጥበባዊ ይዘት ደካማ መሆን ናቸው፡፡

የግጥሙ መልእክት መዛባት

የዚህ አይነቱ ችግር የኦርቶዶክሳዊ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን አስተምህሮና የመጻሕፍት ትርጓሜ ጠንቅቆ ካለማወቅ፣ በግል ሕይወት ላይ ብቻ ከመመስረት ወይም ከኑፋቄ ትምህርት የተወሰደ መልእክትን ከመጠቀም የሚመነጭ ነው፡፡ እንዲሁም የመዝሙር ካሴቱን ሊገዙ ይችላሉ የሚባሉትን ምድራዊ የኑሮ ሁኔታ ብቻ ያገናዘበ “ገበያ መር” መልክት ላይ ማተኮር የዚህ ችግር አንዱ መሰረት ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የመዝሙሩ ግጥም የሚያንጸባቀው መልእክት የኦርቶዶክሳዊ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን አስተምህሮ የማይገልጽ ወይም የሚቃረን ሲሆን ይታያል፡፡ እንዲሁም የመዝሙሩ ዓላማ በዝማሬ ሰዎችን በልዕልና ለክርስቲያናዊ ሕይወት (ለንስሐ እንዲሁም ለሥጋ ወደሙ) የሚያበቃ መሆን ሲገባው በምድራዊ ሕይወትና ስኬት ላይ መሰረት ያደረገ ሲሆን ይታያል፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትን መሰረት አድርገን ትርጉማቸው የተዛቡትን ለምሳሌ ያህል ጠቅሰን ለማስረጃነት ያህል ለማሳየት እንሞከራለን፡፡

በአንዳንድ መዝሙራት ላይ “ክርስቶስ ድንጋዩን በኃይሉ ፈነቃቅሎ ተነሳ” የሚል ሀሳብ የያዘን ግጥም እናያለን፡፡ ይህን ከቤተ ክርስቲያን ትምህርት እንጻር ስናየው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሦስተኛይቱ ቀን መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል እንደተነሳ ነው:: ገጣሚው መጽሐፍ ቅዱስን በቀጥታ ትርጉም እያነበበ ስለጻፈው ማስረጃ የሚያደርገው “ድንጋዩንም ከመቃብሩ ተንከባሎ አገኙት” ሉቃ ፳፬:፪ የሚለውን ነው:: በማቴዎስ ወንጌል (፳፰:፪) ላይ ግን ድንጋዩን ማን እንዳንከባለለው በግልጽ ተጽፎአል “እነሆም፥ የጌታ መልአክ ከሰማይ ስለ ወረደ ታላቅ የምድር መናወጥ ሆነ፤ ቀርቦም ድንጋዩን አንከባሎ በላዩ ተቀመጠ። እንዲሁም “በቅዳሴ ዲዮስቆሮስ (፩፥፱-፴፩) “በሦስተኛው ቀን መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ወዳሉበት በዝግ ቤት ገብቶ በጽርሐ ጽዮን ታያቸው”:: በቅዳሴ ያዕቆብ ዘሥሩግ (፩፥፳፬) “ሰውን ስለ መውደድህ ይህን ሁሉ አደረግህ፤ ከሙታን ተለይተህ ‹መቃብር ክፈቱልኝ፤ መግነዝ ፍቱልኝ› ሳትል ተነሣህ፡፡ ከእግረ መስቀል ሙታንን አስነሣህ ነፍሳትን ከሲኦል ማርከህ ለአባትህ አቀረብህ” እንዲል::

ሌሎች ተጨማሪ ምሳሌዎችን ለማንሳት ያህል ቅዱስ ጊዮርጊስን በተመለከተ “ሰባት ጊዜ ሞቶ ሰባት ጊዜ ተነሳ” የሚል መልእክትን የያዘ መዝሙር በገድለ ቅዱስ ጊዮርጊስ ላይ ያለውን እውነት አያንጸባርቅም፡፡ “አንዱ ሀገር ስትሄድ ኢየሱስ፣ ሌላ ሀገር ስትሄድ ደግሞ አማኑኤል አለችው” የሚለውም እንዲሁ ቅድስት ድንግል ማርያም ያላደገረችውን እንዳደረገች አድርጎ ማቅረብ ነው፡፡ “ሁሉ ነገር ከእርሱ የማይወጣ…” የሚለውም እንዲሁ አሻሚ ትርጉም የሚይዝ ስለሆነ አንዳንዶችን ለትችት ይጋብዛል፡፡ “ሰው አድርገኝና ሰው ይግረመው” የሚለውም መልእክት እንዲሁ የሰው ንስሐ መግባት ዓለማው ሌላውን ሰው ለማስገረም የሆነ ዓይነት ያስመስላል፡፡ ፍጽምት የሆነች ሃይማኖትን ይዘን “ርትዕት ሃይማኖት አለን” እያልን መዘመር ስንችል ወደታች ወርደን “አልተሳሳትንም” እያልን መዘመርም እንዲሁ ደካማ መልእክትን ነው የሚያስተላልፈው፡፡ “ትክክለኛነት” እና “አለመሳሳት” ይለያያሉና፡፡ በተመሳሳይ “ለነፍሴ ነፍሷ ነሽ” የሚለው አባባልም ግልጽነት ያስፈልገዋል፡፡ አንዳንዶች ይህንን ባልተፈለገ መንገድ ሊተረጉሙት ይችላሉና፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞ በተለይ በዚህ ዘመን እየሰፋ የመጣው ሌላው ችግር “የግለሰብ ሕይወትን” ብቻ የሚያንጸባርቅ መልእክትን ለመዝሙር መጠቀም ነው፡፡ በኃጢአት ይኖር የነበረ ሰው በንስሐ ወደ ቅድስና ሥራ ሲመለስ የሰማይ መላእክት ሳይቀሩ ይደሰታሉ (ሉቃ ፲፭:፯)፡፡ ተነሳሂውም እግዚአብሔርን በመዝሙር ማመስገኑ ተገቢ ነው፡፡ ነገር ግን የሚዘምራቸው መዝሙሮች መልእክታቸው በእርሱ ምድራዊ ሕይወት ላይ ብቻ ያተኮሩ ከሆኑና ጥሪውም መንፈሳዊ መሆኑን የዘነጋ ሲሆን የቤተ ክርስቲያንን ዓላማ መዘንጋት ያሆናል:: ይህም ዓላማ የሰውን ልጅ ለድኀነት ማብቃት እንዲሁም አምኖ ሲፈጽም በአመነበት እምነት ጸንቶ ከኃጢአት በመጠበቅ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “የተፈተነውን ራስህን ለእግዚአብሔር ልታቀርብ ትጋ” እንዳለ የቤተ ክርስቲያንን ጥሪ ካለማወቅ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እንዳይማሩ ሥርዓቷን አውቀው እንዳይገዙ ይከለክላቸዋል፤ በአንጻሩ ፈቃዳቸውን (ስሜታቸውን) የሚከተሉ ምእመናን እንዲበዙ ምክንያት ይሆናል፡፡

በተለይም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተለያዩ “ዘማርያን” ከዘፋኞች በተኮረጀ አሰራር መዝሙርን ከገበያ አንጻር የመቃኘት አካሄድ በግልጽ ይታያል፡፡ ዘፋኞች ከቅጅ መብት አከባበር ጋር በተያያዙና በሌሎችም ምክንያቶች ዘፈኖቻቸውን ለዘፈን ዝግጅት (Concert) ለመጋበዝ በሚያመቻቸው መልኩ እንደሚቃኙ ይታወቃል፡፡ በተለይም ከንግድ እይታ አንፃር የተሻለ ገንዘብ የሚከፈላቸው በዝርወት ምድር በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን (Ethiopian Diaspora communities) በመሆኑ ዘፈኖቻቸውን ከዚህ ማኅበረሰብ ጋር የማያያዝ አካሄድ አለ፡፡ በተመሳሳይ ራሳቸውን መንፈሳዊ አድርገው የሚያቀርቡ ዘማርያንም ይህንኑ አካሄድ ይከተላሉ፡፡ በዝርወት ምድር በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናትና ምዕመናን ተራ ተወዳጅነት ለማግኘትና በወንጌልና በዝማሬ በመነገድ የገንዘብ ትርፍ ለማግኜት ሲሉ የመዝሙሮቻቸውን ግጥሞች በዚያው መልኩ ይቃኛሉ፡፡

መዝሙርን ስጋዊ ስሜትን ለማንጸባረቅ፣ ለንግድና ለታዋቂነት መጠቀም ዝማሬውንም የማኅበር ከመሆን ይልቅ “የግል” እንዲሆን ያበረታታል፡፡ በሃይማኖታቸው በነበራቸው ተጋድሎና ጽናት እግዚአብሔር ለነሱ ያደረገላቸውን አስበው ምስጋናን ያቀረቡትን ህዝበ እስራእኤልን፣ ሠለስቱ ደቂቅን፣ በእስር ላይ የነበሩትን ሐዋርያትንም ምሳሌ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ለምሳሌ ህዝበ እስራእኤል እግዚአብሔር ከግብጽ ባርነት ስላወጣቸው የምስጋናን መዝሙር በኅብረት አቅርበዋል (ዘፀ ፲፮:፩):: በብሉይ ያለው ታሪክን ምሳሌነቱን በምስጢር ከዲያብሎስ ባርነት ነጻ የወጣንበትን የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማዳንን ትንሣኤውን እያሰብን በኅብረት ሆነን በቅኔ ስናመሰግን ዝማሬውም ሁሉን የሰው ልጅ የሚያሳትፍና ዘመንም የማይሽረው ኦርቶዶክሳዊ ዝማሬ ይሆናል:: መዝሙሮችን ግለሰባዊ ማድረግ የንግድ እንጂ የመንፈሳዊነት ውጤት አይደለም፡፡

የኪነ-ጥበባዊ ይዘት ደካማ መሆን

ሁለተኛው ችግር የመዝሙሩ ግጥም ወይም ኪነ-ጥበባዊ ይዘቱ ደካማ መሆን ነው፡፡ ለግጥም የሚውሉት ቃላት መንፈሳዊ ገጽታ የሌላቸው ተርታ፣ እንግዳ ወይም ጸያፍ ቃላት ሲሆኑ፣ የግጥሙም መልእክት ፍሰቱን ያልጠበቀና እና መደበላለቅ ሲኖርበት፣ በማኅበረሰቡም ዘንድ ብዙ ጊዜ የተለመዱ ቃላትን ለቤት መምቻነት የሚጠቀም ግጥም፣ ቃላትንና ሐረጎችን በግድ ተጎትቶ ቤት የሚመታ ወይም ጭራሹንም የማይመታ ግጥም መጠቀም፣ እንዲሁም ለዜማ የሚቆረቁሩ ቃላት/ፊደላት ድንገት መጥተው የሚደነቀሩበት ግጥም ያለው መዝሙር ኪነ-ጥበባዊ ይዘቱ ችግር ያለበት ነው፡፡ ለምሳሌ ብንመለከት በአንዳንድ በቤተ ክርስቲያን ስም እየታተሙ የሚወጡ የካሴት መዝሙሮች ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ድፍረት ባለበት ቃል “ፍቅሬ” “ውዴ” በማለት የሚጠሩ አሉ:: አባቶቻችን ግን በአነጋገራቸው በጸሎታቸው እጅጉን ተጠንቅቀው ሲጠሩትም ማንም በማይጠራበት (‘ጠ’ ጠብቆ ይነበብ) ልዩ በሆነ አጠራር “ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለስም አጠራሩ ክብርና ምስጋና ይግባውና” እያሉ ነው::

የመጀመሪያው ስንኝ “…የሠራዊት ጌታ” ካለ ሁል ጊዜ ሁለተኛው ስንኝ “…ጠዋት ማታ” የሆነ ዓይነት ድግግሞሽ የግጥምን ኪነ-ጥበባዊ ይዘት ያደበዝዛል፡፡ እንዲሁም “ታሪኬን ቀያሪ፣ ከፍ ከፍ በል፣ እንደ ዋርካ ሰፋን፣ ምድርን ከደንናት…ወዘተ” የሚሉ እንደፋሽን በየግጥሙ ደጋግሞ መጠቀምም የመልእክት ድርቀትን ያሳያል፡፡ በምድር የሚኖሩ የተለየ ሀሳብ ያላቸውን ወንድሞችና እህቶችን እንደጠላት በመቁጠር “ጠላቴ ሆይ…፣ …ጠላቶቼ” ማለትም መንፈሳዊነት አይደለም፡፡ የሥጋዊ ሀብት መሻሻልን ብቻ ከግምት ውስጥ በማስገባት “ያከበርከኝ…” የሚል አስተሳሰብም እንዲሁ ሥጋዊ እንጂ መንፈሳዊ አይደለም፡፡ በምድር ላይ ያሉ ፖለቲካዊ ክስተቶችንም መነሻ በማድረግ ምድራዊ አስተሳሰብን ብቻ የሚያንጸባርቅ ግጥምም እንዲሁ ሊታሰብበት ይገባል፡፡

ምድራዊ ሰዎችን ስንጠራ የምናደርገውን ጥንቃቄ ያህለ እንኳን ያልተጠነቀቅን ከሆነ ፍጹም መንፈሳዊውን ነገር እንዳልተገነዘብንና እንዴት በሃይማኖት መመላለስ እንደሚገባንም አለመረዳታችንን ያስረዳል:: በማቴዎስ ወንጌል ፰:፲ ካለው ታሪክ እንደምንማረው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቅፍርናሆም በገባ ጊዜ የመቶ አለቃ ወደ እርሱ ቀርቦ ከለመነውም ጥያቄ የምንማረው ትህትናውን ሃይማኖቱን እንዲሁም ጥበብን ነው:: ጌታችንም ሰምቶ እንደተደነቀና ለተከተሉትም “እውነት እላችኋለሁ፥ በእስራኤል እንኳ እንዲህ ያለ ትልቅ እምነት አላገኘሁም።” ነበር ያላቸው:: የመቶ አለቃው ጥበብ ከራሱ ማዕረግ ጋር በማነጻጸር ወታደሮችን የሚያዝ ገዢ ብዙ ሰዎችን የሚያስተዳድር እንዳለውና እሱ ይህን ማድረግ ሲቻለው የሰማይና የምድር ፈጣሪ መድኃኔዓለም ሁሉ የሚገዛልህ አንተን የማይታዘዝህ ማን አለ የሚል ነበር:: ዛሬም ለአምላካችን ለቅዱሳን ያለን ግንዛቤና አጠራር ለዓለም ከምንሰጠው አጠራርና ክብር ለይተን  በሃይማኖት ዓይን ተመልክተን ሊሆን ይገባል::

የመፍትሔ አስተያየት

ኦርቶዶክሳዊ መዝሙር ገንዘብና ዝናን ዓላማ በማድረግ መዘጋጀት የለበትም፡፡ እነዚህን ዓላማ አድርጎ የሚነሳ ማንኛውም ሰው ለጊዜው በተጥባበ ስጋ መልካም የሚመስል ስራ ቢሰራ እንኳ ፍፃሜው ሊያምር አይችልም፡፡ መንፈሳዊ አገልግሎትን በስጋዊ ዓላማ መፈጸም አይቻልምና፡፡ ከዚያ ባሻገር ከኦርቶዶክሳዊ የመዝሙር ግጥም (መልእክት)ጋር ለተያያዙ ችግሮች  ዋነኛ መፍትሔ የሚሆነው የመዝሙሩን ዓላማ ከምድራዊ ጥቅም ይልቅ መንፈሳዊው ላይ እንዲያተኩር ማድረግ፣ የግጥሙን ሥራ የሚሰራው ሰው የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን አስተምህሮ፣ ሥርዓትና ትውፊት የሚያውቅና (ቢያንስ ለሚጽፈው ክፍል ያለውን) የቅኔ የኪነ-ጥበብም ተሰጥኦ ወይም ልምድ ያለው ቢሆን መልካም ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ አስተማሪነቱ እንዲጎላ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያንና ትምህርቷን ጠንቅቀው የተረዱ የቤተክርስቲያኒቱ ልጆች የመዝሙሩን ግጥም አይተው እርማት ቢያደርጉበት ይበልጥ ይጠቅማል፡፡ እንዲሁም ኦርቶዶክሳዊ ለዛውን እንዲጠብቅ ያደርገዋል፡፡ ጠንከር ያለ የይዘትና የአገላለጽ የስነ-ጽሑፍ አርትኦት (editing) የመዝሙሮችን መልእክት ትክክለኛነት ለማረጋገጥና ኪነጥበባዊ ደረጃውን ለመጠበቅ ይረዳልና ኦርቶዶክሳውያን የመዝሙር ግጥም “ደራሲዎችም” በአግባቡ ቢጠቀሙበት መልካም ነው፡፡

1 thought on “ኦርቶዶክሳዊ መዝሙር፡ ርስታችንን አጥብቀን እንያዝ (ክፍል ፪)

  1. Pingback: ዘማሪ ማስመጣት፡ በሐዋርያዊ ጉዞ ላይ የዘማርያን ሚና – አስተምህሮ

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s