የእውቀት እምነትና የእውነት እምነት

እምነት ማለት እግዚአብሔር ታማኝ አምላክ በመሆኑ የተናገረውን በፍጹም ልብ ተቀብሎ በእግዚአብሔር የተስፋ ቃል ላይ ማረፍ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረው ‹‹እምነትም ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ፥ የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ ነው።›› ዕብ 11፡1 በመጽሐፍ ቅዱስ አገላለጥ እምነት ሁለት ነገሮችን ሊያመለክት ይችላል፡፡ አንደኛው የእውቀት እምነት (የአጋንንት እምነት፣ የሞተ እምነት) ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ እውነተኛ እምነት (የተስፋ እምነት፣ በሥራ የተገለጠ እምነት) ነው፡፡ በእነዚህ ሁለት የእምነት ዓይነቶች መካከል ያሉት ዋና ዋና ልዩነቶች እንደሚከተለው ቀርበዋል፡፡

እግዚአብሔርን ማወቅ አንጻር

የእውቀት እምነት ብቻ ያላቸው አጋንንት እግዚአብሔርን ያውቃሉ፡፡ ይህንን ዓለም እንደፈጠረ እነርሱንም እንደፈጠረ ያውቃሉ፡፡ ሰውም እርሱን አምኖ እንደሚድን ያውቃሉ፡፡ ነገር ግን እውቀታቸው ከእውቀትነት አያልፍም፡፡ እውቀታቸው ወደ መልካም ምግባር አይቀየርም፡፡ እግዚአብሔርን ማወቅ ብቻ እውነተኛ እምነት አይሆንምና እነርሱ በእውቀታቸው አይድኑበትም፡፡ ስለዚህ ነው የአጋንንት እምነት የእውቀት እምነት የሚባለው፡፡ በሐዋርያት ዘመን ክፉ መንፈስ ለማውጣት የሞከሩት ያገኙት ምላሽ ‹‹ኢየሱስንስ አውቀዋለሁ ጳውሎስንም አውቀዋለሁ፤ እናንተሳ እነማን ናችሁ?›› የሚል ነበር። ሐዋ 19፡13-16 አጋንንት ኢየሱስን አውቀዋለሁ ከማለት አልፈው ‹‹የእግዚአብሔር ልጅ›› እና ‹‹የእግዚአብሔር ቅዱሱ›› ብለው ተናግረዋል፡፡

በአንጻሩ እውነተኛ እምነት ያለው ሰው እግዚአብሔርን ያውቃል፡፡ እውቀቱም ተስፋ ያለበት ስለሆነ እውነተኛ እምነት ይሆንለታል፡፡ በእግዚአብሔር ላይ ተስፋ አለውና፡፡ ብበድለውም እንኳን አምላኬ ይቅርባይ ስለሆነ በንስሐ ብመለስ ይቅር ይለኛል፣ ልጁም ያደርገኛል ብሎ ያምናል፡፡ ስለ እግዚአብሔር ያለው እውቀት ፍቅር ስላለበት አይታበይበትምና፡፡ 1ኛቆሮ 8፡1 እውቀቱን ለጽድቅ ዓላማ ይጠቀምበታል፡፡

እምነትን በሥራ መግለጥ አንጻር

የእውቀት እምነት ብቻ ያላቸው አጋንንት እግዚአብሔርን ያምናሉ፡፡ ይህም ማለት እርሱ አምላክ እንደሆነ ያውቃሉ፡፡ ስለዚህም ነው ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ ‹‹እግዚአብሔር አንድ እንደ ሆነ አንተ ታምናለህ፤ መልካም ታደርጋለህ፤ አጋንንት ደግሞ ያምናሉ ይንቀጠቀጡማል። አንተ ከንቱ ሰው፥ እምነት ከሥራ ተለይቶ የሞተ መሆኑን ልታውቅ ትወዳለህን?›› ያዕ 2፡19-20 ያለው፡፡ የእነርሱ እምነት መልካም ሥራ የሌለበት በክፋት የተመላና የእውቀት ብቻ ነውና፡፡ እንደዚሁም የእውነተኞች ማኅበራት፣ ጽዋና ማዕድ እንዳለ የአጋንንትም አለ፡፡ ይህም ሐዋርያው ጳውሎስ ‹‹ከአጋንንትም ጋር ማኅበረተኞች እንድትሆኑ አልወድም። የጌታን ጽዋና የአጋንንትን ጽዋ ልትጠጡ አትችሉም፤ ከጌታ ማዕድና ከአጋንንት ማዕድ ልትካፈሉ አትችሉም። 1ኛ ቆሮ 10፡20-21›› ብሎ ባስተማረው ይታወቃል፡፡

እውነተኛ እምነት ያለው ሰው ግን እምነቱ በሥራ (በተግባር) የተገለጠ ነው፡፡ እምነቱን በሥራ (ትዕዛዛትን በመፈጸም) ያሳያል፡፡ ላመነው አምላክ ሕጉን በመፈፀም ይታመናል፡፡ ከሚያምኑትም ጋር ማኅበር ይመሠርታል፣ ጽዋንም ይጠጣል፣ በማዕድም ይካፈላል፡፡ ከአጋንንት ማኅበር ግን ይርቃል፡፡ ከማያምኑ ጋር በማይመች አካሄድ አይጠመድም፡፡

እግዚአብሔርን መፍራት አንጻር

የእውቀት እምነት ብቻ ያላቸው አጋንንት እግዚአብሔርን ይፈራሉ፡፡ የሚፈሩትም ያጠፋናል፣ ያቃጥለናል፣ ይቀጣናል ብለው ነው፡፡ በማቴዎስ ወንጌል ‹‹ወደ ማዶም ወደ ጌርጋሴኖን አገር በመጣ ጊዜ፥ አጋንንት ያደሩባቸው ሁለት ሰዎች ኢየሱስ ሆይ፥ የእግዚአብሔር ልጅ፥ ከአንተ ጋር ምን አለን? ጊዜው ሳይደርስ ልትሣቅየን ወደዚህ መጣህን? እያሉ ጮኹ። ማቴ 8፡28-34›› እና በማርቆስ ወንጌል ‹‹በዚያን ጊዜም በምኩራባቸው ርኵስ መንፈስ ያለው ሰው የናዝሬቱ ኢየሱስ ሆይ፥ ከአንተ ጋር ምን አለን? ልታጠፋን መጣህን? ማን እንደ ሆንህ አውቄአለሁ፥ የእግዚአብሔር ቅዱሱ ብሎ ጮኸ። ማር 1፡23-25›› የተጠቀሱት የአጋንንት እግዚአብሔርን መፍራት ያሰቃየናል/ያጠፋናል ከሚል የመነጨ ነው፡፡

እውነተኛ እምነት ያለው ሰውም እግዚአብሔርን ይፈራል፡፡ የሚፈራው ግን ከፍቅር የተነሳ ነው እንጂ ያሰቃየኛል/ያጠፋኛል ከሚል አስተሳሰብ  አይደለም፡፡ አምላኩን ስለሚወደው ከማክበር የተነሳ ይፈራዋል፡፡ ትዕዛዙንም ከፍቅር የተነሳ ይጠብቃል፡፡ ‹‹ከወደዳችሁኝስ ትዕዛዜን ጠብቁ›› (ዮሐ. 14፡15) እንደተባለ፡፡ እግዚአብሔርንም መፍራት የጥበብ ሁሉ መጀመሪያ ስለሆነ በእውነተኛ እምነት ያለ ሰው እግዚአብሔርን ይፈራል፡፡ ክቡር ዳዊት በመዝሙሩ “ለእግዚአብሔር በፍርሃት ተገዙ፣ በረዓድም ደስ ይበላችሁ” (መዝ. 2፡11) እንዳለ እውነተኛ እምነት ያለው ሰው እግዚአብሔርን መፍራቱ በደስታ የሚፈጸም ነው፡፡

የእግዚአብሔርን ቃል መጥቀስ አንጻር

ጌታችንን ዲያብሎስ በገዳመ ቆሮንቶስ በፈተነው ጊዜ ካቀረበለት ፈተናዎች መካከል አንዱ ‹‹መላእክቱን ስለ አንተ ያዝልሃል እግርህንም በድንጋይ ከቶ እንዳትሰናከል በእጃቸው ያነሡሃል ተብሎ ተጽፎአልና የእግዚአብሔር ልጅስ ከሆንህ፥ ወደ ታች ራስህን ወርውር›› የሚል ነበር ማቴ 4፡6 ይህም አስቀድሞ በነቢዩ ዳዊት በመዝሙር የተነገረ ቃል ነው፡፡ እንዲሁም ሐዋርያው ጳውሎስ ለልጁ ጢሞቴዎስ በጻፈው መልእክቱ ‹‹መንፈስ ግን በግልጥ፡- በኋለኞች ዘመናት አንዳንዶች የሚያስቱ መናፍስትንና በውሸተኞች ግብዝነት የተሰጠውን የአጋንንትን ትምህርት እያደመጡ፥ ሃይማኖትን ይክዳሉ ይላል፡፡ 1ኛ ጢሞ 4፡1-2›› ሲል አስጠንቅቆታል፡፡ ይህም ማለት የእውቀት እምነት ብቻ ያላቸው አጋንንት የእግዚአብሔርን ቃል ለጥፋት ዓላማ እያጣመሙ ይጠቅሱታል ማለቱ ነው፡፡

እውነተኛ እምነት ያለው ሰውም መጽሐፍ ቅዱስን ያነባል፣ ይጠቅሳል፣ ያስተምራል፡፡ የሚጠቅስው ግን ለትክክለኛው ዓላማ በትክክለኛው መንገድ (ባለማጣመም) ነው፡፡ ይህም የእግዚአብሔርን ቃል የሚጠቅሰው ሕይወት ስለሆነ ሕይወትን ለማግኘትና ሐዋርያት ባስተማሩት መሠረት ነው፡፡ መጽሐፍ ‹‹በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል›› (ኤፌ. 2፡20) እንዳለ በእውነተኛ እምነት ያለ ሰው በዚህ መሠረት ላይ ታንጾ የመጽሐፍን ቃል ለድኅነት ዓላማ ይጠቀምበታል፡፡

ተአምራትን ማድረግ አንጻር

የእግዚአብሔር ምርጦች ተአምራትን እንደሚያደርጉ ሁሉ የእውቀት እምነት ብቻ ያላቸው አጋንንትም በሰው ላይ አድረው ተአምራትን ያደርጋሉ፡፡ ለዚህም ሙሴና አሮን በፈርኦን ፊት ምልክትን ሲያሳዩ ጠንቋዮችም በአስማታቸው እንደዚያው አድርገው ነበር፡፡ ‹‹ አሮንም በትሩን በፈርዖንና በባሮቹ ፊት ጣለ፥ እባብም ሆነች። የግብፅም ጠንቋዮች በአስማታቸው በትራቸውን ጣሉ፥ እባቦችም ሆኑ፤ የአሮን በትር ግን በትራቸውን ዋጠች። ዘፀ 7፡ 9-10›› በሁለተኛውም ተአምር ‹‹አሮን በትሩንም አነሣ፥ በፈርዖንና በባሪያዎቹም ፊት የወንዙን ውኃ መታ፤ የወንዙም ውኃ ሁሉ ተለውጦ ደም ሆነ። የግብፅም ጠንቋዮች በአስማታቸው እንዲሁ አደረጉ፡፡ ዘፀ 7፡20-22›› በሦስተኛውም ‹‹አሮንም በግብፅ ውኆች ላይ እጁን ዘረጋ፤ ጓጕንቸሮቹም ወጡ። ጠንቋዮችም በአስማታቸው በግብፅም አገር ላይ ጓጕንቸሮችን አወጡ። ዘፀ 8፡6-7›› ነገር ግን የአጋንንት ተአምር ከዚህ በላይ መዝለቅ አልቻለም፡፡ የሙሴና የአሮን ግን እስራኤልን ወደ ከነዓን እስከማድረስ ድረስ ነበር፡፡

እውነተኛ እምነት ያለው ሰውም ተአምራትን ሊያደርግ ይችላል፡፡ ብዙ ቅዱሳን ብዙ ተአምራትን አድርገዋልና፡፡ ተአምራትን ማድረግ ግን ብቸኛ የቅድስና መገለጫ አይደለም፡፡ ቅዱሳን ተአምራትንም ያደረጉት በእግዚአብሔር ኃይል ነው፡፡ እዚህ ላይ ማስተዋል የሚያስፈልገው ነገር አንድ ሰው ተአምር ማድረጉ ብቻ እውነተኛ አያስብለውም፡፡ በማን ኃይል ነው ተአምር የሚያደርገው የሚለው ነው መሰረታዊው ነጥብ፡፡ የተዓምር ዓላማ ሰውን ለትምህርት ተገዢ ማድረግ ነው፡፡ የእውነተኞችን ተዓምር የሚያይ ለእውነት ትምህርት፣ የሐሰተኞቹን ተዓምር የሚያይ ደግሞ ለሐሰት ትምህርት ተገዢ የመሆን እድላቸው ሰፈ ነው፡፡ ዛሬ እውነተኛ ተዓምር አይቶ፣ ተዓምሩን ብቻ አድንቆ የመጣ ሰው ነገ የሐሰት ተዓምር ሲያይ ከተዓምሩ ጋር የሚዛመደውን ትምህርትና ስርዓት ሳይመረምር ለስህተት ትምህርት ይጋለጣል፡፡ ይህም በየዘመኑ በተደጋጋሚ የታየ እውነታ ነው፡፡ ቤተክርስቲያን የምትቆመው በተዓምር ሳይሆን በትምህርት መሆኑን መረዳት ይኖርብናል፡፡ ጌታችንም ያስተማረው፣ ሐዋርያትም የነገሩን፣ በቤተክርስቲያን ታሪክም የሚታወቀው ይሔው ነው፡፡

እግዚአብሔርን መምሰል አንጻር

የእውቀት እምነት ብቻ ያላቸው አጋንንት አምላክ ነን አምልኩን ብለው ሰውን ያታልላሉ፡፡ በጌታ ስም በቅዱሳንም ስም በደካማ ሰው ላይ አድረው እንዲሁም መልካቸውን እየለዋወጡ ያታልላሉ፡፡ ስለዚህ ነው ሐዋርያው ‹‹እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎች የክርስቶስን ሐዋርያት እንዲመስሉ ራሳቸውን እየለወጡ፥ ውሸተኞች ሐዋርያትና ተንኮለኞች ሠራተኞች ናቸውና። ይህም ድንቅ አይደለም፤ ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣልና። እንግዲህ አገልጋዮቹ ደግሞ የጽድቅን አገልጋዮች እንዲመስሉ ራሳቸውን ቢለውጡ ታላቅ ነገር አይደለም፤ ፍጻሜአቸውም እንደ ሥራቸው ይሆናል። 2ኛ ቆሮ 11፡13-15›› ያለው፡፡

እውነተኛ እምነት ያለው ሰው ግን ክርስቶስን ይመስላል፡፡ ሐዋርያው ‹‹እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እናንተ ደግሞ እኔን ምሰሉ (1ኛ ቆር 11፡1)›› እንዳለው ክርስቶስን ይመስላል፡፡ እውነተኛ ክርስቲያን ራሱን አይለዋውጥም፡፡ ሌላውንም አያታልልም፡፡ እውነተኛ ማንነቱን ብቻ ይገልጣል እንጂ፡፡ ይህች እውነተኛ ማንነቱም በቀናች ሃይማኖት፣ በበጎ ምግባር ያጌጠች ክርስቲያናዊ ሕይወት ናት፡፡

ዘላለም ሕይወት አንጻር

የእውቀት እምነት ብቻ ያላቸው አጋንንት ምንም አውቀት ቢኖራቸውም በእውቀታቸው መልካም ነገርን ስለማይሠሩበት  መጨረሻቸው የዘላለም እሳት ነው፡፡ በራዕየ ዮሐንስ ‹‹ያሳታቸውም ዲያብሎስ አውሬውና ሐሰተኛው ነቢይ ወዳሉበት ወደ እሳቱና ወደ ዲኑ ባሕር ተጣለ፥ ለዘላለምም እስከ ዘላለም ቀንና ሌሊት ይሣቀያሉ። ራዕ 20፡10›› እንደተባለው መጨረሻቸው ይኸው ነው፡፡

በእውነተኛ እምነት ያለ ሰው ግን መጨረሻው የዘላለም ሕይወት ነው፡፡ እውነተኛ ክርስቲያን በዚህ ምድር ላይ በተጋድሎ ኖሮ ሩጫውን ሲጨርስ የጽድቅ አክሊልን ከአምላኩ ዘንድ ይቀበላል፡፡

ስለዚህ በውሸት “እምነት” ከተባለ የመጽሐፍ ቅዱስን ትምህርት ለሥጋዊ ዓላማና ግብ ከሚያጣምም፣ እውነተኛ የመጽሐፍ ቅዱስን ዓላማ ከማይከተል፣ በተግባር ከማይገለጥ፣ በሐሰት ተዓምራት ላይ ከተመሰረተ የአጋንንት ዓይነት “እምነት” ተለይተን ከቅዱሳን ሐዋርያት በእምነት የተቀበልነውን የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ያለመበረዝና ያለመቀላቀል ተቀብለን፣ እምነታችንን በምግባራት አስጊጠን፣ በእውነተኛ ተዓምራት እንዲሁም በቅዱሳን ሁሉ ሕይወት የተገለጠችውን የእውነት እምነት ያለማመንታት ጠብቀን የመንግስቱ ወራሾች የክብሩ ቀዳሾች እንሆን ዘንድ የእግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃድ ይሁንልን፡፡ የእውነት እምነትን የጠበቁት፣ ለእኛም በዘመናት መካከል በሕይወት የተገለጠች ሃይማኖታቸውን ከሰይጣን መከራ ጠብቀው፣ ድል በማትነሳ ረድኤት፣ ጥርጥር በሌለባት እምነት የጸኑት የቅዱሳን ሁሉ በረከት ከእኛ ጋር ይሁን፡፡ አሜን፡፡

 

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s