መግቢያ
ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ በመጀመሪያይቱ መልእክቱ በዘመኑ በታናሹ ኤስያ ለሚኖሩ ክርስቲያኖች “በእናንተ ስላለ ተስፋ ምክንያትን ለሚጠይቋችሁ ሁሉ መልስ ለመስጠት ዘወትር የተዘጋጃችሁ ሁኑ፤ ነገር ግን በየዋህነትና በፍርሀት ይሁን (1ኛ ጴጥ 3፡15)” በማለት ስለ ክርስቲያናዊ ጥብቅና አስተምሯቸዋል፡፡ በዚህም መልእክቱ ስለ ክርስቲያናዊ ጥብቅና (Christian apologetics) ሁለት መሠረታዊ ነጥቦችን አስተምሯል፡፡ በመጀመሪያ ስለ መሠረተ እምነታችን፣ ስለቤተክርስቲያናችን ሥርዓትና ትውፊት “ለምን?” ብለው ምክንያትን (reason) ለሚጠይቁን መልስ ለመስጠት ሁል ጊዜ የተዘጋጀን መሆን እንደሚያስፈልግ ነግሮናል፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ለሚጠይቁን መልስ ስንሰጥ በየዋህነት/በጥበብ/ (gentleness) (ሰዎችን ሳናሰናክል፣ ተገቢውን ክብር በመስጠት) እና በፍርሀት/በአክብሮት/(respect) (እግዚአብሔርን በመፍራት፣ ህጉን በመጠበቅ) መሆን እንዳለበት መልዕክት አስተላልፏል፡፡
ክርስቲያናዊ ጥብቅና (ለቤተክርስቲያን ጥብቅና መቆም) አስቀድሞ ቅዱሳን ሐዋርያት ከዚያም በእነርሱ እግር የተተኩ ሊቃውንት አባቶች ሲፈጽሙት የነበረ ዋነኛ የአገልግሎታቸው ተግባር ነው፡፡ በእምነት በመጽናታቸው፣ ለእምነታቸው ጠበቃ ሆነው፣ እነርሱ የሕይወት መስዋእትነትን ከፍለው ኦርቶዶክሳዊት እምነትን ስላቆዩልን ዛሬ “አባቶቻችን” ብለን ስንናገር አናፍርባቸውም፡፡ ሃይማኖትን መጠበቅ፣ ለሃይማኖትም ጠበቃ መሆንን ያስተማሩን እነርሱ ናቸውና፡፡ በኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ታላቅ ቦታ ከሚሰጣቸው አዋልድ ቅዱሳት መጻሕፍት መካከል ሃይማኖተ አበው የተባለው ድንቅ መጽሐፍ አንዱ ነው፡፡ ይህ መጽሐፍ በየዘመናቱ የተነሱ ሊቃውንት አባቶቻችን በየዘመናቸው የተነሱ መናፍቃንና አጽራረ ቤተክርስቲያን ላነሷቸው ልዩ ልዩ የክህደት ትምህርቶች በመጽሐፍ ቅዱስ መሰረትነት የተሰጡ መልሶችንና ሃይማኖትን የሚያጸኑ መልእክቶችን የያዘ ነው፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስም ስለ ሃይማኖቱ ጥብቅና መቆሙን ለደቀ መዝሙሩ ለጢሞቴዎስ ሲጽፍለት “መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ፣ ሩጫውን ጨርሻለሁ፣ ሃይማኖትን ጠብቄአለሁ..” (2ኛ ጢሞ 4፡7) በማለት መስክሯል፡፡ ሐዋርያው ሃይማኖትን ጠብቄአለሁ ሲል በአሕዛብ ፊት፣ በአይሁድ ፊት፣ በሮማውያን ፊት ስለ ክርስቶስ ወንጌል በመመስከር የፈጸመውን ክርስቲያናዊ ጥብቅና ሲናገር ነው፡፡
ክርስቲያናዊ ጥብቅና ለቤተክርስቲያን እጅግ አስፈላጊ ከሆኑት የአገልግሎት ዘርፎች አንዱ ነው፡፡ ስለዚህ ነው “ለቤተክርስቲያን ጥብቅና መቆም” በነገረ-መለኮት ትምህርት አንድ ዘርፍ ሆኖ “ጥብቅና ለክርስትና” (Theology of Apologetics) ተብሎ የሚሰጠው፡፡ የቤተክርስቲያን ሊቃውንት ሥራቸው ይህ ነውና፡፡ በምዕመናንና በመንፈሳውያን ማኅበራትም አንዱ ወሳኝ ጉዳይ ሆኖ በመደበኛነት የሚሠራበት አገልግሎት ነው፡፡ ነገር ግን ስለክርስቲያናዊ ጥብቅና በቂ ግንዛቤና የተቀናጀ እንቅስቃሴ ካለመኖሩም ባሻገር አንዳንዶች ለቤተክርስቲያንና ለክርስትና እምነታቸው ጠበቃ የቆሙ እየመሰላቸው ራሳቸውንና ቤተክርስቲያንን እየጎዱ ይገኛሉ፡፡ እኛም በዚህች የአስተምህሮ ጦማር ስለ ክርስቲያናዊ ጥብቅና ምንነት፣ አስፈላጊነት፣ አግባብ ያለው አፈጻጸም እንዲሁም ሊደረጉ ስለሚገባቸው ጥንቃቄዎች እንዳስሳለን፡፡
የክርስቲያናዊ ጥብቅና ምንነት
በኦርቶዶክሳዊት ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ሥር የሚኖር አንድ ክርስቲያን እምነቱን (ሃይማኖቱን) በተመለከተ አምስት ነገሮችን ማወቅ አለበት፡፡ እነዚህም ምን (dogma) እንደሚያምን፣ ለምን (reason) እንደሚያምን፣ ያመነውን እንዴት መፈጸም እንዳለበት (Cannon)፣ ያመነውን እንዴት ለሌሎች ማሳወቅ (sharing) እንዳለበትና እምነቱን የሚፈታተን አስተሳሰብ ሲመጣ እንዴት መከላከል (defense) እንዳለበት ማወቅ ናቸው፡፡ ከዚህ አንጻር ክርስቲያናዊ ጥብቅና ማለት ለቤተክርስቲያን አስተምህሮ፣ ሥርዓትና ትውፊት ጠበቃ (ጠባቂ፣ አስጠባቂ፣ ተከላካይ) መሆን ማለት ነው፡፡ የቤተክርስቲያን ጠባቂ ክርስቶስ ቢሆንም የሰው ድርሻ የሆነውን ማበርከት ክርስቲያናዊ ጥብቅና ይባላል፡፡ በአራተኛውና በአምስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ለተነሱት መናፍቃን እነ ቅዱስ አትናቴዎስ፣ ቅዱስ ቄርሎስና፣ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ የሰጡት ምላሽ በቤተክርስቲያን ታሪክ ተጠቃሽ የክርስቲያናዊ ጥብቅና አገልግሎት ነው፡፡
የክርስቲያናዊ ጥብቅና አስፈላጊነት
የክርስቲያናዊ ጥብቅና ዓላማዎች ብዙ ናቸው፡፡ የክርስቲያናዊ ጥብቅና ዋነኛ ዓላማ ግን የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እምነት፣ ሥርዓትና ትውፊት እንዲጠበቅ ማድረግ ነው፡፡ በዚህም ያመኑትና የተጠመቁት እስከመጨረሻው እንዲጸኑና ለመንግስተ ሰማያት እንዲበቁ ማድረግ ነው፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ያላመኑት የክርስቶስን ወንጌል እንዲያውቁና እንዲያምኑ፣ አምነውና ተጠምቀውም ጸጋን ከሚያሰጡ ምስጢራተ ቤተክርስቲያን እንዲካፈሉ፣ በእምነታቸው ጸንተው ምግባር ትሩፋትን ሠርተው፣ በእምነታቸውና በምግባራቸው ለቤተክርስቲያናቸው ጌጥና መታወቂያ ሆነው ሰማያዊውን መንግስት እንዲወርሱ ማድረግ ነው፡፡ የቤተክርስቲያን አስተምህሮም ሳይበረዝ ለቀጣዩ ትውልድ እንዲተላለፍ ለማድረግ የክርስቲያናዊ ጥብቅና ድርሻው ከፍተኛ ነው፡፡ ስለሆነም ለክርስትና ሃይማኖታቸው ጥብቅና የሚቆሙት ዋጋቸው በሰማያት ታላቅ ነው፡፡ ሐዋርያው ይሁዳ “ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለተሰጠች ሃይማኖት እንድትጋደሉ እለምናችኋለሁ” (ይሁዳ 1፡3) ያለውም ለሃይማኖታችን ጥብቅና እንድንቆም ነው፡፡ ለሃይማኖት መጋደል ማለትም በቃልና በተግባር ለክርስትናና ለቤተክርስቲያን ጥብቅና መቆም ማለት ነው፡፡
የክርስቲያናዊ ጥብቅና መንገዶች
ለኦርቶዶክሳዊት ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ጥብቅና የምንቆመው በአራት መንገዶች ነው፡፡
እውነተኛ እምነቷን፣ ሥርዓቷንና ትውፊቷን በመግለጥ: ሰዎች የቤተክርስቲያንን አስተምህሮ፣ ሥርዓትና ትውፊት በሚገባ እንዲያውቁ፣ አውቀውም እንዲያምኑበት ማድረግ የክርስቲያናዊ ጥብቅና መጀመሪያውና መሠረታዊው ዓላማ ነው፡፡ የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ዶግማና ቀኖና አውቆ ማሳወቅ፣ ጠብቆ ማስጠበቅ ክርስቲያናዊ ጥብቅና ነው፡፡ በቅዱሳት መጻሕፍት የሰፈረውን እውነት፣ የሊቃውንተ ቤተክርስቲያንን ትምህርት አስተባብሮ ለሰዎች ማስተማር ቀዳሚው የክርስቲያናዊ ጥብቅና ሥራ ነው፡፡ ኀልወተ እግዚአብሔርን ለማያምኑ ሰዎች የተለያዩ የኀልወተ እግዚአብሔር መገለጫዎችን አደራጅቶ ማስተማርም ክርስቲያናዊ ጥብቅና ነው፡፡
በቤተክርስቲያን ላይ የሚነሱ መሠረተ ቢስ ወቀሳዎችን ሐሰትነታቸውን በማጋለጥ: ቤተክርስቲያን ያልሆነችውን ሆነች፣ ያላደረገችውን አደረገች፣ የማታደርገውን ታደርጋለች፣ ተግታ የምታደርገውን አታደርግም ለሚሉ ወገኖች ይህ ወቀሳቸው እውነት እንዳልሆነ ማስረዳት ሁለተኛው የክርስቲያናዊ ጥብቅና ዘርፍ ነው፡፡ ለምሳሌ “ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ክርስቶስን አትሰብክም” ለሚሉ ወገኖች ቤተክርስቲያናችን ክርስቶስን ያልሰበከችበትና የማትሰብክበት ጊዜ እንደሌለ ምሳሌን በመጠቀም ማሳየት፣ “ቤተክርስቲያን ቅዱሳንን ታመልካለች” ለሚሉት እንዲሁ ቤተክርስቲያን እግዚአብሔርን ብቻ እንደምታመልክና ቅዱሳንን እንደምታከብር ማስረዳት፣ “ቤተክርስቲያን ስንፍናን ታስተምራለች” ለሚሉትም ቤተክርስቲያን ሥራን ምን ያህል ዋጋ ሰጥታ እንደምታስተምር፣ “የድህነት ምክንያት ናት… ወዘተ” ለሚሉትም ሁሉ በማስረጃ የተደገፈ በቂ ምላሽ መስጠት ክርስቲያናዊ ጥብቅና ነው፡፡ ይህንንም የምናደርገው ክርስቲያኖችን ከመጠበቅ አንጻር ነው፡፡
ቤተክርስቲያንን የሚያስነቅፉ አሰራሮች እንዲስተካከሉ የራስን ድርሻ ማበርከት: በዚህ ዘርፍ በመጀመሪያ ደረጃ እኛ ራሳችን የምንሠራው ቤተክርስቲያንን እንዳያስነቅፋት መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ በቤተክርስቲያን ውስጥ ያለን አገልጋዮችም ሰዎች ነንና እንድንበረታ በጸሎት፣ እንድንጠነክር በሀሳብ (በምክር)፣ በተግባር መደጋገፍ ክርስቲያናዊ መገለጫችን ሊሆን ይገባል፡፡ ቤተክርስቲያንን የሚያስነቅፍ ሥራ የሚሠሩትም እንዲማሩና እንዲያውቁ፣ እንዲመከሩና እንዲታረሙ ለቤተክርስቲያን ሥርዓት ጥብቅና መቆም ያስፈልጋል፡፡ ከዚህ አልፈው ለሌሎች መሰናክል የሚሆኑ ከሆነ ደግሞ ለቤተክርስቲያንና ለእግዚአብሔር መንገር ያስፈልጋል፡፡ ከዚህ አንጻር የክርስቲያናዊ ጥብቅና ውጤት የቤተክርስቲያንን ሥርዓት የሚጠብቁና የሚያስጠብቁ (የቤተክርስቲያን ጠበቃዎችን) ማብዛት ነው፡፡
ምዕመናንን ሊያሳስቱና ሊያስቱ የሚችሉ ሐሰተኛ አስተምህሮዎች በቂ ምላሽ መስጠት: በዘመናችን እንደ አሸን ለፈሉት የሐሰት ትምህርቶች ለሁሉም ባይሆንም በክርስቲያኖች አእምሮ ጥያቄ የሚፈጥሩና ምዕመናንን ሊያስቱ ለሚችሉት በቂ ምላሽ መስጠት ከሊቃውንቱና ከሰባክያነ ወንጌሉ የሚጠበቅ ነው፡፡ ነገር ግን ሁሉም ክርስቲያን የራሱ ድርሻ አለው፡፡ ሐሰተኛ አስተምህሮዎች ለምንና እንዴት ሐሰት እንደሆኑ፣ ብንከተላቸው ለድኅነት (ለጽድቅ) የማያበቁ መሆናቸውን ማጋለጥ ክርስቲያናዊ ጥብቅና ነው፡፡ ከዚህ ጎን ለጎን ደግሞ እውነተኛው ሃይማኖት (አስተምህሮ) ለምንና እንዴት እውነት እንደሆነ፣ ለመዳንም የሚያደርስ መሆኑን ማስረዳትም የዚሁ አካል ነው፡፡ ይህንንም ስናደርግ ዒላማችን ሰዎችን ያሳሳተው የስህተት አስተምህሮ ላይ ሆኖ ለተሳሳቱ ወገኖቻችን ግን ፍቅርን በማሳየት ሊሆን ይገባል፡፡ ሐሰተኛ ትምህርቶችንም ስንሞግት መሠረታዊ የሆኑ መረጃዎችን አደራጅተንና ተንትነን በማያዳግም መልኩ ሊሆን ይገባዋል እንጂ “አለባብሰው ቢያርሱ…” እንዳይሆን መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡
መደረግ ያለባቸው ጥንቃቄዎች
ለቤተክርስቲያን ጥብቅና ስንቆም መጠንቀቅ ያለብን ብዙ ጉዳዮች አሉ፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ጥብቅና የምንቆምለትን የቤተክርስቲያንን አስተምህሮ፣ ሥርዓትና ትውፊት ማወቅ፣ ማመንና መፈጸም ይኖርብናል፡፡ እኛ የማንፈጽመውን ነገር ሌሎችን ፈጽሙ እያልን ጥብቅና መቆም ከአንድ ክርስቲያን የሚጠበቅ አይደለምና፡፡ጠንቅቀን ሳናውቅ ጥብቅና ለመቆም ብንሞክር ተፈትነን ከጽናታችን ልንወድቅ እንችላለንና አስቀድመን ጠይቀን እንወቅ፡፡ ሌላውን ለማዳን አስቀድሞ ራስ መዳን ያስፈልጋልና አስቀድመን ራሳችንን እናድን፡፡ ያን ጊዜ ሌላውን ማሳወቅ፣ ለቤተክርስቲያንም ጠበቃ መሆን እንችላለን፡፡
በሁለተኛ ደረጃ ለቤተክርስቲያን ጥብቅና የምንቆምበት መንገድ ሥርዓትን የተከተለና ለሌሎች አስተማሪ መሆን ይኖርበታል፡፡ ለቤተክርስቲያን ጥብቅና የምንቆምበት መንገድ የራሳችንን ተአማኒነት የሚያሳጣ፣ ሰዎችን የሚጎዳ፣ ቤተክርስቲያንን የሚያሰድብ እንዳይሆን መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ እንዳስተማረን በየዋህነትና በፍርሀት ለቤተክርስቲያን ጥብቅና እንቁም፡፡ ሌሎች ቤተክርስቲያንን ስለጎዱ (ጎድተዋታል ብለን ስላሰብን) እኛ እነርሱን ለመጉዳት አናስብ፡፡ ክርስትናችንንና ቤተክርስቲያንን የምንጠብቅበትን አካሄድ በጥላቻ በመነቃቀፍ ሳይሆን እግዚአብሔርን በመፍራት እናድርገው፡፡ በጥላቻና በክርክር የሚደረግ ከሆነ ክርክሩን ብንረታ እንኳን ሰውን ማትረፍ ላንችል እንችላለን፡፡ ብዙ መመለስ የሚችሉ ሰዎች ከአያያዝ ጉድለት ጠፍተው ቀርተዋልና ክርስቲያናዊ ጥብቅናችን በየዋህነት፣ በብልሀት፣ በመከባበርና በፍቅር ሊሆን ይገባል፡፡
እምነታችንንና ቤተክርስቲያንን ለመጠበቅ በምናደርገው ሂደት ውስጥ መስዋእትነት (የጊዜ፣ የሞራል፣ የገንዘብ፣ የሕይወት) መክፈል ካስፈለገ በጸጋ ለመቀበል መዘጋጀት ያስፈልጋል፡፡ ለቤተክርስቲያን ጠበቃ ለመሆን ስንተጋ ሠርተን ራሳችንን (ምድራዊ ኑሮአችንን) የምንለውጥበትን ጊዜና ጉልበት እንዲሁም አእምሮ ይወስድብናል፡፡ በአጽራረ ቤተክርስቲያንና የክርስትና መንገድ እውነትነት ባልገባቸው የዋሀን የስድብ፣ የስም ማጥፋት ዘመቻ ሊከፈትብን ይችላል፡፡ ከዚህም አልፎ በሐሰት ክስ እየከሰሱ ሊያንገላቱንና ሊያሳስሩን እንዲሁም ጊዜያችንንና ገንዘባችንን ሊያስወጡን ይችላሉ፡፡ አልፎ አልፎም ማስፈራራት፣ የአካል ጉዳት፣ የሕይወት አደጋም ሊደርስብን ይችላል፡፡ ነገር ግን ዋጋችን በሰማይ ነውና በጽናትና በጥብዐት ለቤተክርስቲያን ጥብቅና ቆመን ቤተክርስቲያናችንን ከተኩላዎች ልንከላከል ይገባናል፡፡
ለቤተክርስቲያን ጥብቅና መቆም የሁሉም ክርስቲያን ኃላፊነት ነው፡፡ “እኛ ምን አገባን” ወይም “ሌሎች ይሠሩታል” ብለን የምንተወው ጉዳይ አይደለም፡፡ ክርስትናችንንና ቤተክርስቲያናችንን የምንጠብቀውም በመግደል ሳይሆን በመሞት፣ ጉዳትን በማድረስ ሳይሆን መከራን በመቀበል፣ በጦርነት ሳይሆን ሰላምን በመስበክ መሆኑን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ተምረናል፡፡ ብርሀነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስም “ለእውነት እንጂ በእውነት ላይ ምንም ልናደርግ አንችልምና (2ቆሮ.13፡8)” እንዳለው እውነት በሆነው በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተመሠረተችው ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ላይ የሚነሱ ለጊዜው የሚጎዷት የሚያጠፏት ይመስላቸዋል እንጂ እግዚአብሔር በደሙ የዋጃትና የሚጠብቃት ቤተክርስቲያን በደካሞች እጅ ልትጠፋ አትችልም፡፡ ቤተክርስቲያንን በማቃጠልና ክርስቲያኖችን በመግደል ቤተክርስቲያንን ማጥፋት የሚቻል ቢሆን ኖሮ በዘመነ ሰማዕታት የነበሩ ነገሥታት ባጠፏት ነበር፡፡ ነገር ግን እንደነ ቅዱስ ጊዮርጊስና ቅደስት አርሴማ ያሉ ታላላቅ ሰማዕታትን (የእውነት ምስክሮችን) እንድታፈራ አደረጓት እንጂ አላጠፏትም፡፡ በእውነት ላይ የሚነሱ ራሳቸው ይጠፋሉ እንጂ “የገሃነም ደጆች አይችሏትም” እንደተባለ (ማቴ 16፡18) እውነትን ሊያጠፏት አይችሉም፡፡ ለእውነት የሚተጉ፣ እውነት የሆነችውን ደገኛይቱን የሃይማኖት መንገድ የሚያቀኑ፣ ስለእውነተኛይቱ እምነት ጥብቅና የሚቆሙና ስለእውነትም መከራን የሚቀበሉ ግን በመጨረሻው ቀን ከእውነተኛው አምላክ የጽድቅ አክሊልን ይቀበላሉ፡፡ እኛም ለእውነት ጥብቅና ቆመን በቀኙ ለመቆም ያበቃን ዘንድ የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት የቅዱሳን ተራዳኢነት አይለየን፡፡
ወስብሃት ለእግዚአብሔር