የልጆች መንፈሳዊ ትምህርት መሠረታዊ ዓላማዎች

Focus areasየልጆች መንፈሳዊ ትምህርትን ስናስብ በቅድሚያ ትኩረታችንን የሚስበው ይዘቱ (‘ምን ይማሩ?’ የሚለው) ነው። ወላጆችም ቢሆኑ ስለልጆቻቸው ትምህርት ሲያስቡ በቅድሚያ ማወቅ የሚፈልጉት ‘ምንድን ነው የሚማሩት?’ የሚለውን ነው። ልጆቻቸውንም ‘ምን ተማራችሁ?’ ብለው ነው የሚጠይቁት። የልጆች መንፈሳዊ ትምህርት የሚመራበት ሥርዓተ ትምህርትም ተቀዳሚ ትኩረቱ ‘ልጆች ምን ይማሩ?’ የሚለው ጉዳይ ነው። ይህም የሥርዓተ ትምህርቱ መሠረት ነው። የመምህራን ምደባም ይሁን የትምህርቱ ስልት በትምህርቱ ይዘት ላይ ተመሥርቶ ነው የሚወሰነው። በዚህም መሠረት የልጆች መንፈሳዊ ትምህርት ዋና ዓላማ ልጆች በመንፈሳዊና በሥጋዊ ሕይወታቸው ብቁ እንዲሆኑ ማስቻል ነው:: የመንፈሳዊ ሕይወታቸው ብቃትም በእምነታቸው ጽናትና በክርስቲያናዊ ሥነ-ምግባራቸው ይገለጣል:: እያንዳንዱ መንፈሳዊ ትምህርትና ሥልጠና ይህን ታሳቢ ማድረግ ይኖርበታል::

ከዚህም አንጻር የልጆች መንፈሳዊ ትምህርት ዋና ዋና ዓላማዎች የልጆችን እድሜና የቋንቋ ችሎታን ባገናዘበ መልኩ መንፈሳዊ ዕውቀትን፣ በጎ አመለካከትን፣ ክርስቲያናዊ እሴትንና የመንፈሳዊ አገልግሎት ክህሎትን እንዲያዳብሩ ማስቻል ነው:: እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ሙሉ ክርስቲያናዊ ስብዕና የሚገነባው በዕውቀት ወይም በምግባር ላይ ብቻ ባተኮረ ትምህርት ሳይሆን በእነዚህ በአራቱም ላይ በሚያጠነጥን ተከታታይና ዘላቂነት ባለው ትምህርትና ተሞክሮ ነው:: በዘመናችን የሚታየው የመንፈሳዊ ሕይወት ዝለት አንዱና ዋናው መነሻ መንፈሳዊ ትምህርቶች ከነዚህ ከተጠቀሱት መሠረታዊ ዓላማዎች በአንዱ (በተለይ በዕውቀት ላይ) ወይም በሁለቱ ላይ ብቻ ስለሚያተኩሩ ነው:: እኛም በዚህች የአስተምህሮ ጦማር የልጆችና መንፈሳዊ ትምህርት ዋና ዋና ዓላማዎች እንዳስሳለን፡፡

እምነት፡ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ እምነትን በሚገባ ማሳወቅ

ልጆች በመንፈሳዊው ትምህርታቸው ስለ እግዚአብሔር አምላክነት፣ ስለፍጥረታት አፈጣጠር፣ በአጠቃላይ ስለ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አስተምህሮ፣ እንዲሁም ስለቤተክርስቲያን ታሪክና ፈተናዎች በቂ ዕውቀትን እንዲጨብጡ ማስቻል ያስፈልጋል::  የልጆች  መንፈሳዊ ትምህርት ማካተት ከሚገባቸው አርዕስት መካከልም የእግዚአብሔር ባሕርይ እና ፈጣሪነት፣ ዓለማትን እንዴት እንደተፈጠሩ፣ የሰው ልጅ አፈጣጠርና የእግዚአብሔር ጥበቃ፣ ቅዱሳን መላእክትና ሰዎች እና ሥራቸው፣ ስለ ከበሩ ንዋየ ቅድሳት (ታቦትና ጽላት የመሳሰሉት)፣ ስለ ጌታችን ሥጋዌ (ሰው መሆን)፣ በነገረ ድህነት የእመቤታችን ድርሻ ክብርና ሕይወት፣ ጌታችን ያስተማረው ወንጌልና ያደረጋቸው ተአምራት፣ የጌታ በራሱ ፈቃድ መሰቀል መሞት እና መነሣት፣ ዕርገቱና ዳግም ምጽአቱን፣ ጽድቅና ኩነኔ፣ የቤተክርስቲያን ታሪክና የዘመን አቆጣጠር፣ በዓላትና አከባበራቸው…ወዘተ ይጠቀሳሉ፡፡

አመለካከት፡ ቀና አመለካከት እንዲኖራቸው ማድረግ

ልጆች ነገረ ሃይማኖትን በእውቀት ተኮር አሰጣጥ ቢማሩም ቀና አመለካከት ግን ከሌላቸው ጥረቱ ሁሉ ዋጋ የለውም:: ቤተክርስቲያንን የሚያሳድዱ ወገኖቻችን ስለቤተ ክርስቲያን አነሰም በዛ ያውቃሉ:: ለአስተምህሮዋም ሆነ አስተምህሮዋን ለመጠበቅ ሊሰራ ስለሚገባው ተቋሟ ያላቸው አመለካከት ግን ደዌ አለበት:: በመሆኑም የልጆች መንፈሳዊ ትምህርት ዕውቀትን ከማስጨበጥ በተጨማሪ ልጆች ስለ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ዶግማ፣ ቀኖና፣ ትውፊት፣ ታሪካዊ ጉዞ ቅን አመለካከት ወይም አስተያየት እንዲኖራቸው ማገዝ አለበት:: በጎ አመለካከት የብዙ ነገሮች መሠረት ስለሆነ በልጅነታቸው መገንባት ይኖርበታል፡፡

እሴት፡ ኦርቶዶክሳዊ እሴቶችን ማስተማር

የልጆች መንፈሳዊ ትምህርት ልጆች ኦርቶዶክሳዊ እሴቶችን ለምሳሌ እምነትን፣ ተስፋን፣ ፍቅርን፣ መረዳዳትን፣ መታገስን፣ ትህትናን፣ ፅናትን፣ መታዘዝን፣ ንጽሕናን ወዘተ ገንዘብ እንዲያደርጉ ማገዝ አለበት::  እነዚህ እሴቶች ለክርስትና ሕይወት መሠረታዊ ነገሮች ስለሆኑ ልጆች ከልጅነታቸው ጀምሮ የሕይወታቸው አካል አድርገው ሊያድጉ ይገባል፡፡ እነዚህንም እሴቶች የሚማሩት በማየትና በመሳተፍ ስለሆነ ወላጆች፣ መምህራንና ሌሎች የቤተክርስቲያን ምዕመናን እነዚህ እሴቶችን በመተግበር ለልጆች አርአያ ሊሆኑ ይገባል፡፡

ሥርዓት፡ ሥርዓተ ቤተክርስቲያንን እንዲፈጽሙ ማስቻል

ልጆች ስለሃይማኖታቸው በቂ ዕውቀትና በጎ አመለካከት ቢኖራቸው በምግባር መተርጎም ካልቻሉ እንዲሁ ዋጋ ቢስ ነው:: ልጆች ሲያድጉ አንድ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኝ ሊኖረው የሚገባውን ሥነ-ምግባር ይኖራቸው ዘንድ ያስፈልጋል:: መንፈሳዊ ትምህርታቸውም ልጆች ክርስቲያናዊ ሕይወትን ለመኖር የሚያስችላቸውን ዘዴዎች ሥራ ላይ እንዲያውሉ ያደርጋል:: መንፈሳዊ ትምህርቱ የተለያዪ የክርስትና ሕይወት ተግባራትን እንዲማሩ ያግዛል:: ለምሳሌ ያህል ጸሎት እንዴት እንደሚጀመርና እንደሚፈጸም፣ ቤተ ክርስቲያን ሲገባ እንዴት መሳለም እንደሚገባ፣ በቅዳሴና በትምህርት ጊዜ ሊደረግ የሚገባ ተሳትፎ፣ ከቅዱስ ቍርባን በፊት፣ ጊዜና በኋላ የሚደረጉ ዝግጅቶችና ጥንቃቄዎች ልጆች መማርና ማወቅ እንዲሁም መፈጸም ያስፈልጋቸዋል፡፡ ይህንንም ከመንፈሳዊ ትምህርቱ ሊያገኙ ይገባል። ስለ ሥርዓተ ቤተክርስቲያን የምናስተምርበት መንገድም ልጆችም ሆኑ ሌሎች ምዕመናን ከምንፈጽመው የሚታይ ሥርዓት ባሻገር ያለውን ታላቅ መንፈሳዊ ምሥጢር በኦርቶዶክሳዊ ለዛ እንዲረዱ በማድረግ ይገባል እንጂ ጌታችን እንደወቀሳቸው ጸሀፍትና ፈሪሳዊያን የሥርዓትን መሰረታዊ ዓላማ በመዘንጋት መሆን የለበትም፡፡

ክህሎት፡ የመንፈሳዊ አገልግሎት ክህሎትን እንዲያዳብሩ ማድረግ

ልጆች በቤተክርስቲያን በሚሰጣቸው መንፈሳዊ ትምህርት መንፈሳዊ አገልግሎትን ለመፈጸም የሚሆኑ ክህሎቶችን እየተማሩ ማደግ አለባቸው፡፡ ለምሳሌ ኦርቶዶክሳዊ (ያሬዳዊ) ዝማሬን ማጥናትና ማቅረብ፣ የቅዳሴ ተሰጥኦ መቀበል መቻል፣ በአገልግሎት ጊዜ የሚደረጉ ዝግጅቶች ማስተናገድ፣ በቋንቋቸው መጻፍና መናገር፣ ለታናናሾቻቸው የተማሩትን ማስተማር፣ መንፈሳዊ መርሐግብሮችን ማስተባበርና የመሳሰሉትን ክህሎቶች እያዳበሩ ሊያድጉ ይገባል፡፡ ማንኛውም ትምህርት በሚገባ ሊተረጎም የሚችለው ተማሪዉ ለትምህርቱ የሚገባ በቂ ልምምድ አድርጎ አስፈላጊውን ክህሎት ሲይዝ ነው፡፡ በቃል ከማስተማርም ሆነ በገቢር ከማሳየት ባሻገር ልጆችና ህጻናት በቤተክርስቲያን አገልግሎት እየተሳተፉ ክህሎታቸውን እንዲያሳድጉ ማድረግ ይገባል፡፡ ቤተክርስቲያን ሽህ ዘመናትን ተሻግራ ለዘመናችን ከነትውፊቷ የደረሰችው ልጆችና ወጣቶችን እንደ መርሐ ግብር ማሟያና በሚያይ አሰራር ሳይሆን በገቢር በሚያሳትፍ አሰራር ነው፡፡ ታላላቅ አባቶቻችን ቅዱሳን በጉባኤ ሲገኙ ከእነርሱ ይልቅ ወጣቶች የሆኑ ረድኦቻቸው (ረዳቶቻቸው) እንዲያስተምሩ፣ መናፍቃንንም እንዲረቱ ያደርጉ የነበሩት (ለምሳሌ ቅዱስ አትናቴዎስ) ከእውቀትና ምግባር ባሻገር የክህሎትን ትምህርት እየሰጧቸው ነበር፡፡

ሥነ-ምግባር፡ በክርስቲያናዊ ሥነ-ምግባር ማጎልበት 

ልጆች በልጅነታቸው ቤተክርስቲያን ሄዶ ማስቀደስን፣ እንደየአቅማቸው መጾምና መጸለይን፣ ምፅዋት መስጠትን፣ ሥራን ጠንክሮ መሥራትን፣ ሰውን ማክበርን፣ ከሌሎች ጋር ለምሳሌ ከጓደኛ ከጎረቤት ጋር በሰላም መኖርን…ወዘተ እየተማሩ ሊያድጉ ይገባል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ መጥፎ ከሆኑ ምግባራት ይርቁ ዘንድ በምክንያት ማስረዳት ያስፈልጋል፡፡ መልካም ነገርን ሲያደርጉ ጠቀሜታውን በሚገባ ተረድተውት እንዲያደርጉ፤ መልካም ያልሆነውን ሲተውት ጉዳቱን በሚገባ ተረድተውት እንዲሆን ማድረግ የልጆች መንፈሳዊ ትምህርት ትኩረት መሆን ይኖርበታል፡፡ በኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ መልካም ምግባራት ለክርስቲያን ህይወት መሰረታዊ የድህነት (የመዳን) መፈጸሚያ መንገዶች ናቸው እንጂ ለአንዳንዶች እንደሚመስላቸው “ስንችል” ብቻ የምንፈጽማቸው ከድህነታችን ጋር ያልተያያዙ የምንግዴ ትእዛዛት አይደሉም፡፡

ጥበብ፡ ጥበብን የሕይወታቸው መርህ እንዲያደርጉ ማስቻል

የልጆች መንፈሳዊ ትምህርት ቀጣይ ሕይወታቸውን በማስተዋልና በጥበብ መምራት እንዲችሉ አስተዋጽኦ ማበርከት ይኖርበታል፡፡ ውጥንቅጥ በበዛበት ዓለም እምነታቸውን ጠብቀው እንዲኖሩ በልጅነታቸው ይህንን ጥበብ ከቤተክርስቲያን መማር ይኖርባቸዋል፡፡ ለምሳሌ በእምነት ከማይመስሏቸው ጋር አብሮ መኖርን፣ ስለሃይማኖታቸው ለሚጠይቋቸው ሁሉ በተገቢው ሁኔታ በጥበብ ማስረዳት መቻልን፣ በክርስትናቸው ምክንያት ፈተና ቢገጥማቸው በማስተዋልና በጥበብ ማለፍ መቻልን፣ በሥራ፣ በትዳር ሕይወትና በማኅበራዊ ኑሮ አርአያ መሆንን …. ወዘተ በቤተክርስቲያን ከሚሰጣቸው መንፈሳዊ ትምህርት ሊያገኙትና በሕይወት ተሞክሮአቸው ሊያዳብሩት ይገባል፡፡

በአጠቃላይ የልጆች መንፈሳዊ ትምህርት እውነተኛ እምነትን፣ በጎ አመለካከትን፣ ክርስቲያናዊ እሴትን፣ የመንፈሳዊ አገልግሎት ክህሎትን፣ ሥርዓተ ቤተክርስቲያንን፣ ክርስቲያናዊ ሥነ-ምግባርንና በጥበብና በማስተዋል መኖርን ተቀዳሚ ዓላማዎች ሊያደርግ ይጠበቅበታል። ልጆች የሚማሩበት ሥርዓተ ትምህርትም በእነዚህ ዓላማዎች ዙሪያ የሚያጠነጥን መሆን ይኖርበታል። የሚያስተምሩት መምህራንም በእነዚህ ዓላማዎች ላይ ሊያተኩሩ ይገባል። የማስተማሪያ ስልቱም እነዚህን ዓላማዎች የሚያሳካ መሆን ይጠበቅበታል። ትምህርት በዓላማ ከተመራ ውጤታማነቱ አጠያያቂ አይሆንም። ዓላማዎቹ በግልጽ ካልታወቁ ግን ወጅብ እንደሚያማታው ውኃ ሲዋልሉ መኖር ይሆናል። †

1 thought on “የልጆች መንፈሳዊ ትምህርት መሠረታዊ ዓላማዎች

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s