ቅድስት፡ እግዚአብሔር ለቅድስና እንጂ ለርኲሰት አልጠራንም

ከቅዱስ ያሬድ በተገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የበዓላት ቀኖና መሰረት የዐቢይ ጾም ሁለተኛ ሰንበት ‹‹ቅድስት›› ትባላለች፡፡ «ቅድስት» ማለት «የተቀደሰች፣ የተለየች» ማለት ነው፡፡ በዚህ ዕለት በቤተክርስቲያን በቅዳሴና በማኅሌት ሰዓት የሚነበቡ፣ የሚዜሙ የቅዱሳት መጻሕፍት ምንባባት ስለ ቅድስናና ስለ ቅድስና ሥራ ይሰብካሉ፡፡ ይህች ሰንበት ‹‹ቅድስት›› የተባለችው በባህርይው ቅዱስ የሆነ አምላካችን እግዚአብሔር ዓለምን (ሰውን) ለመቀደስ ሲል ወደ ምድር መምጣቱን፣ የቅድስና አብነት ይሆነን ዘንድም በሥጋው ወራት እንደሰውነቱ በጎ ምግባራትን መስራቱን፣ የቅድስና ተግባር መገለጫ የሆነ ጾምንም መጾሙን ለማስረዳት ነው፡፡ በዚህች ሰንበት እግዚአብሔር ቅዱስ በመሆኑ የተቀደሰ ነገር ያስፈልገዋልና ሰው ሁሉ በቅድስና መንገድ በመመላለስ የክብሩ ባለቤት የመንግሥቱ ወራሽ እንዲሆን ቤተክርስቲያን ታስተምራለች፡፡  እግዚአብሔር “እኔ ቅዱሳን ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ” በማለት ስለማስተማሩ በሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ትምህርት ይሰጥበታል።

ከዚህ በተጨማሪም ይህች ዕለት “ቅድስት” የተባለችው የተቀደሰች ዕለት የሰንበትን ክብር ለማስገንዘብ ነው፡፡ ከዋዜማው ጀምሮ የሚዘመረው ጾመ ድጓ የአምላካችንን ቅድስና እና ሰንበትን ቀድሶ በፈቃዱ እንደሰጠን የሚያነሳው ክፍል ነው፡፡ ይህም ከጾመ ድጓው ‹‹ዛቲ ዕለት ቅድስት ይዕቲ፤ ሰንበትየ ቅድስትየ እንተ አዕረፍኩ፤  ቅዱሳነ ኩኑ እስመ አነሂ ቅዱስ አነ፤ አብ ቀደሳ ለሰንበት›› የሚል ሲሆን ትርጉሙም ‹‹ይህች ቀን የተቀደሰች ናት፤ ያረፍኩባት ቅድስት ሰንበት ናት፤  እኔ ቅዱስ እንደሆንኩ እናንተም ቅዱሳን ሁኑ፤ አብ ሰንበትን አከበራት ቀደሳት፡፡›› የሚል ነው፡፡ “ቅድስት” የሚለው ስያሜም ሰንበት የዕረፍታችን ቀን እንድትሆን በኦሪትም በሐዲስም እግዚአብሔር የባረካት የቀደሳት ዕለት መሆኑዋን የሚያመለክት ነው፡፡

ሰው ለዚህ ለሥጋዊ ህይወቱ የሚያስፈልገውን ለማግኘት መሥራት እንደሚጠበቅበት ሁሉ መንፈሳዊ ህይወቱን ለማጽናትና ቅድስናን ገንዘብ ለማድረግ ደግሞ ከአምላኩ ጋር ያለዉ ግንኙነት (ኅብረት) ፍጹም የጠበቀ ሊሆን ይገባል። ይህንንም ማድረግ የሚቻለው ከኃጢአት ሥራ በመራቅ ብቻ ሳይሆን መንፈሳዊ ትሩፋትን በመስራት ጭምር ነው። በጌታችን ትምህርት፣ በሐዋርያት ስብከት፣ በሊቃውንት ትርጓሜ፣ በቅዱሳን ሁሉ ህይወት የተገለጡትን የመንፈስ ፍሬዎች፣ ጾም፣ጸሎት፣ስግደት፣ምጽዋት ወዘተ ገንዘብ ማድረግ ናቸው። እነዚህ ተግባራት የሰውን (የክርስቲያንን ሰውነት) ለመንፈሳዊነት የሚያበረቱ ናቸው። በቤተክርስቲያን አስተምህሮ አራቱ ዋና ዋና መንፈሳዊ ትሩፋቶች የሚባሉት ጾም፣ ጸሎት፣ስግደት፣ምጽዋት ሲሆኑ የእነዚህም መሠረታዊ ዓላማ እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡

ጾም ለእግዚአብሔር የመታዘዛችን ማሳያ ነው፡፡ ጾም እግዚአብሔር ራሱ ባርኮ የሰጠን ትዕዛዝ ነው፡፡ ራሱ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጾሞ ጾምን ቀድሶልናል (ማቴ 4፡1)፡፡ እንዴት መጾም እንዳለብንም አብራርቶ አስተምሮናል (ማቴ 6፡16)፡፡ ለአዳምና ለሔዋን በመጀመሪያ የተሰጠው ‹‹ከዚህ ዛፍ አትብሉ›› የሚለውም (ዘፍ 3፡1) ትዕዛዝ የጾም የመጀመሪያው መሰረት ነው፡፡ ስለዚህ ጾም መጾም መታዘዝ ነው፡፡ አለመጾም ደግሞ አለመታዘዝ (ዓመጸኝነት) ነው፡፡ ጌታችንም ‹‹ስትጦሙም፥ እንደ ግብዞች አትጠውልጉ፤ ለሰዎች እንደ ጦመኛ ሊታዩ ፊታቸውን ያጠፋሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል። አንተ ግን ስትጦም፥ በስውር ላለው አባትህ እንጂ እንደ ጦመኛ ለሰዎች እንዳትታይ ራስህን ተቀባ ፊትህንም ታጠብ፤ በስውር የሚያይ አባትህም በግልጥ ይከፍልሃል (ማቴ 6፡16)።›› በማለት የጾምን ትዕዛዝ ሰጥቶናል፡፡ ራሱም በገዳመ ቆሮንቶስ ጾሞ አርአያ ሆኖናል (ማቴ 4፡1-11)፡፡ ክርስቲያን ቤተክርስቲያን በሠራችው ሥርዓት መጾም ይገባዋል፡፡ በህመምና ይህንን በመሳሰለው ምክንያት መጾም ካልቻለ ደግሞ የሚችለውን ያህል ሊጾም ይገባዋል፡፡ ጾም በፈቃድ ስለሚደረግ መታዘዝ ነው፡፡ ያለፈቃድ ከሆነ ግን ረሀብ ነው፡፡ ለህጉ በፈቃዳችን በመታዘዝ የቅድስና ባሕርይ ተካፋዮች እንሆናለን፡፡

ጸሎት ከእግዚአብሔር ጋር መግባቢያ ቋንቋ ነው፡፡ ሰው ከአምላኩ ጋር የሚነጋገረው በጸሎት ነው፡፡ ሰው የሚፈልገውን ነገር ከእግዚአብሔር የሚጠይቀው፣ ለተደረገለትም ነገር ሁሉ ምስጋናን የሚያቀርበው በጸሎት አማካኝነት ነው፡፡ ሰው በሃይማኖት ሲኖር ከአምላኩ ጋር መነጋገር አለበት፡፡ “በስውር ላለው አባትህ ጸልይ (ማቴ 6፡6-9)” የተባለው ለዚህ ነው፡፡ አለመጸለይ ማለት ከእግዚአብሔር ጋር ግንኙነት ማቆም ነው፡፡ ሰው ከአምላኩ ጋር ካልተገናኘ ደግሞ በራሱ ደካማ ፍጡር ነው፡፡ ሰው ቤተክርስቲያን ባስቀመጠችው የጸሎት ሥርዓት ሊመራ ያስፈልገዋል፡፡ በተለያየ ምክንያት ያንን ማድረግ ካልቻለ ግን የሚችለውን ያህል ሊጸልይ ይገባል፡፡ ስለዚህ ጸሎት ሰውና እግዚአብሔርን የምታገናኝ ዋና መግባቢያ ናት፡፡ የማይግባባ ሰው በሕይወት የሌለ ብቻ ነው፡፡ መናገር የማይችልም ቢሆን በምልክት ይግባባል፡፡ ጸሎት (ከእግዚአብሔር ጋር መነጋገር) በሕይወት መኖራችንን ያሳያል፡፡

ስግደት ለእግዚአብሔር የመገዛታችን መገለጫ ነው፡፡ የአምልኮ ስግደት በደሙ ለገዛን እኛም እንደምንገዛለት ማሳያ ነው፡፡ እርሱንም እንደምናመልክ ማስረገጫ ነው፡፡ የማይሰግድ አይገዛምና፡፡ ስግደት አምላካችንን እንደምናከብረው እንደምንወደው የምንገልጽበት መንገድ ነው፡፡ ሠለስቱ ደቂቅ ለጣኦት አንሰግድም ያሉትም ለዚህ ነው (ዳን 3፡8)፡፡ ሰው በፍርሀት ሆኖ ለእግዚአብሔር ሊሰግድ ይገባል፡፡ ለዚህ ነው በቅዳሴ ሰዓት ‹‹በፍርሃት ሆናችሁ ለእግዚአብሔር ስገዱ›› የሚባለው፡፡ ሰማያውያን መላእክት ሳያርፉ እንደሚሰግዱለት እኛም በምድር ስንሰግድ የእርሱና በእርሱ መሆናችንን እንገልጻለን (ራዕ 4፡4-8)፡፡ ስግደት የአምልኮ መግለጫ ነው፡፡ ጌታችን ‹‹ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ማንም የለም፤ ወይም አንዱን ይጠላል ሁለተኛውንም ይወዳል፤ ወይም ወደ አንዱ ይጠጋል ሁለተኛውንም ይንቃል፤ ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም (ማቴ 6፡24)።›› እንዳለው የአምልኮ ስግደት ለእግዚአብሔር የመገዛታችን መገለጫ ስለሆነ ለእርሱ ብቻ የሚቀርብ ነው፡፡ በቅዱሳት መጻሕፍት የተመዘገቡት፣ በቤተክርስቲያንም የምንፈጽማቸው ለቅዱሳን የሚደረጉ ስግደቶች የጸጋ እንጅ የአምልኮ ስግደቶች አይደሉም፡፡

ምጽዋት በሰማያት የሚኖረን መዝገብ ነው፡፡ ምጽዋት ወደ ሰማያዊ ቤታችን ስንሄድ የሚጠቅመን መዝገብ (አካውንት) ነው፡፡ ምጽዋት ብልና ዝገት የማያጠፋው፣ ሌባም የማይሰርቀው ሰማያዊ መዝገብ ነው፡፡ በፍርድ ቀን ዋስትና የሚሆነን መዝገብ ነው (ማቴ 6፡19)፡፡ በምድር መዝገብ (የባንክ አካውንት) እያለን  በሰማይ ግን መዝገብ የሌለን መሆን የለብንም፡፡ ዘወትር ‹‹በሰማያዊው መዝገብ ምን አለኝ?›› እያልን ራሳችንን ልንጠይቅ ይገባል፡፡ በምድር ሌላውን ጠቅሞ በሰማይ ራሱን ይጠቅም ዘንድ ሰው ልቡ የፈቀደውን ያህል ምጽዋት በደስታ ይስጥ፡፡ ያለንን ማካፈል በሰማይ መዝገብ ማጠራቀም ነውና፡፡ ጌታም በወንጌሉ ‹‹ብልና ዝገት በሚያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በሚሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በምድር ላይ መዝገብ አትሰብስቡ፤ ነገር ግን ብልም ዝገትም በማያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በማይሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በሰማይ መዝገብ ሰብስቡ (ማቴ 6፡19-20)፡፡›› እንዳለው ምጽዋት የሰማይ መዝገባችን ናት፡፡

ቅድስት በተባለችው የዕለተ ሰንበት መዝሙር (ከጾመ ድጓ) ‹‹ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ ስሙንም ጥሩ፤ ሥራውንም ለአሕዛብ ንገሯቸው፡፡ ለስሙም ምስጋናን አቅርቡ፡፡ ሰንበትን አክብሩ፡፡ እውነትንም አድርጉ፤ ብል የማያበላሸው ሌባም የማያገኘው በሰማያት ያለ መዝገብን ለእናንተ ሰብስቡ፤ ተዘጋጅታችኹም ተቀመጡ፤ ክርስቶስ ወዳለበት ወደላይ አስቡ፡፡›› የሚል መዝሙር/ትምህርት እናገኛለን፡፡ በዚህ ዕለት በቤተክርስቲያን  ‹‹እግዚአብሔርሰ ሰማያተ ገብረ፤ አሚን ወሠናይት ቅድሜሁ፤ ቅድሳት ወዕበየ ስብሐት ውስተ መቅደሱ/እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ሠራ: ምስጋና ውበት በፊቱ: ቅዱስነትና ግርማ በመቅደሱ ውስጥ ናቸው፡፡/ (መዝ.95÷5) የሚለው ምስባክ ከዳዊት መዝሙር ይሰበካል፡፡ እነዚህ መዝሙራት የእግዚአብሔርን ቅድስና እና የሰንበትን ቅድስና የሚገልጹ ሲሆን የሰው ልጅም ቅድስናን የቅድስና ሥራን ገንዘብ በማድረግ ማግኘት እንዳለበት ያስገነዝባሉ፡፡

በአጠቃላይ ጾም ለእግዚአብሔር የመታዘዛችን ማሳያ፣ ጸሎት ከእግዚአብሔር ጋር የምንግባባበት ቋንቋ፣ ስግደት ለእግዚአብሔር የመገዛታችን መገለጫ፣ ምጽዋትም ሰማያዊ መዝገባችን ናቸው፡፡ ሁሉም በነፍስም በሥጋም ሰውን ይጠቅማሉ፡፡ መንፈሳዊ ትሩፋት የተባሉትም የጽድቅ በር ስለሆኑ ነው፡፡ በወንጌል ያመኑ ምዕመናን ራሳቸውን በምግባርም ካላነጹ እምነታቸው ከአጋንንት አይለይም፡፡ እነዚህ ትሩፋቶች ግን የሥጋን ፈቃድ ለነፍስ በማስገዛት በእምነት የምናገኘውን ጽድቅ በልጅነት ገንዘብ እንድናደርግ፣ የእግዚአብሔርን ፍፃሜ የሌለው ቸርነትም እንድንጠባበቅ ይረዱናል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “እግዚአብሔር ለቅድስና እንጂ ለርኲሰት አልጠራንምና (1ኛ ተሰ 4፡7)፡፡” እንዳለው የተጠራነው ለቅድስና መሆኑን ማስተዋል ያሻል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም “ነገር ግን የጠራችሁ ቅዱስ እንደሆነ እንዲሁ እናንተም በአካሄዳችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ፡፡ ‘እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ’ የሚል ተጽፎአልና፡፡” እንዳለው የቅድስናን ሥራ ዘወትር ገንዘብ ማድረግ ይገባል፡፡ ከኃጢአት በንስሐ ነጽተን፣ መንፈሳዊ ትሩፋትን ሠርተን በእግዚአብሔር ቸርነት የዘላለም ሕይወትን እንድንወርስ የእርሱ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡

2 thoughts on “ቅድስት፡ እግዚአብሔር ለቅድስና እንጂ ለርኲሰት አልጠራንም

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s