መድኅን ተወልዶላችኋል!

lidet photo

“እነሆ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኅን ተወልዶላችኋል፤ ይኽውም ቡሩክ ጌታ ክርስቶስ ነው፡፡” ሉቃ 2፡11

አዳም ከተሳሳተ ከገነትም ከወጣ በኋላ 5,500 ዘመን ሲፈፀም፣ ሕገ ኦሪት ከተሰጠች 1,800 ዘመን በኋላ፣ የእግዚአብሔር ቤተመቅደስ ከተሠራ 1,000 ዓመት በኋላ፤ በልደተ ሥጋዌ (ማቴዎስ) ተቆጥሮ ከአብርሃም 42 ትውልድ በኋላ፣ በልደተ ሕጋዊ (ሉቃስ) ተቆጥሮ ከአዳም 77 ትውልድ በኋላ፣  ከዛሬ 2011 ዓመት በፊት በዓለማችን ላይ አንድ ታላቅ ተአምር ተከናወነ፡፡

አውግስጦስ ቄሳር የሮም ገዥ፣ ሄሮድስ የይሁዳ ንጉስ፣ እንዲሁም ቄሬኔዎስ የሶርያ ገዥ በነበሩበት ወቅት የሰውን ልጅ ሕይወት ወደ ታላቁ የድኅነት ምዕራፍ ያሸጋገረ ታላቅ ክስተት በማዕከለ ምድር፣ በሀገረ እስራኤል ተከሰተ፡፡ ይህም የጌታችን የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ነው (ማቴ 1፡17)፡፡ የእርሱ ልደት ከሌሎች ልደታት ሁሉ ልዩ ነው፡፡ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት በነቢያት ትንቢት ተነግሮለት፣ በመልአኩ በቅዱስ ገብርኤልም ብስራት ተነግሮለት በህቱም ድንግልና ስለተወለደ የእርሱ ልደት እጅግ ልዩ ነው፡፡

በዚያ ወራት  ለግብር አሰባሰብ እንዲያመች በማሰብ ሰው ሁሉ እንዲቆጠር (እንዲፃፍ) ከአውግስጦስ ቄሳር ትዕዛዝ ወጣች፡፡ የእመቤታችን ጠባቂ የነበረው ዘመዷ አረጋዊው ዮሴፍም ከዳዊት ወገን ነበርና ፀነሳ ከነበረችው ከድንግል ማርያም ጋር ሊቆጠር ከገሊላ ናዝሬት ከተማ ተነስቶ ቤተልሔም ወደምትባል ከተማ ወደ ይሁዳ ሄደ፡፡ሁሉም በየወገኑ ይቆጠር ስለነበር ዮሴፍም ከዳዊት ወገን ስለነበር ወደቤተልሔም ሄዱ፡፡ ጌታም ከአሕዛብ ጋር (እነርሱን ሊያድን መጥቷልና) አብሮ ይቆጠር ዘንድ ወደዚያው አመሩ፡፡

በዚያም (በቤተልሔም) እያሉ የድንግል ማርያም የመውለጃዋ ወራት (9 ወር ከ 5ቀን) ደረሰ፡፡ የበኩር ልጅዋንም ወለደችው፡፡ ‹‹እኔም ደግሞ በኩሬ አደርገዋለሁ፤ ከምድር ነገስታትም ከፍ ይላል (መዝ 88፡27) ፡፡›› እንደተባለ የበኩር ልጅዋን ወለደችው፡፡ አውራ ነህ ስትል እንዲሁም እንደዚህ በዮሴፍና በኒቆዲሞስ ትገነዛለህ ስትልአውራ ጣቱን አሠረችው፡፡  በድርብ በፍታ ትገነዛለህ ስትል፤ ካህናት ሥጋህን ይጠቀልሉታል ስትል በጨርቅም ጠቀለለችው፡፡ በግርግምም አስተኛችው፤ በእንግዶች ማረፊያ ቦታ ስላልነበራቸው ህፃኑ በግርግም ተኛ፡፡

በዚህች ዕለት የመወለዱ ትንቢት ተፈፀመ፡፡ የመወለዱ ብስራትም ተፈፀመ፡፡ በነቢይ ‹‹ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች›› የተባለው (ኢሳ 7፡14) ተፈፀመ፡፡ ‹‹በጨለማ የሄደ ሕዝብ ታላቅ ብርሃን አየ በሞት ጥላና በጨለማ ሀገርም ለነበሩ ብርሃን ወጣላቸው (ኢሳ 9፡2)››እንደተባለም ያ ብርሀን ወጣ፡፡ እንዲሁም ‹‹ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፤ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፤ ስሙም ድንቅ መካር፥ ኀያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል።›› ኢሳ 9፡6 ተብሎ እንተተነበየም ሕፃን ተወለደ፡፡ ‹‹ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች ›› (ኢሳ 7፡15) እንደተባለም ስሙን አማኑኤል አለችው፡፡ አማኑኤል ማለት እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ሆነ ማለት ነው፡፡ ‹‹ ከጽዮን ታዳጊ ይመጣል፤ ከያዕቆብም ኃጢአትን ያርቃል፡፡››(ኢሳ 59፡20)ተብሎ እንደተፃፈ መድኃኒት ክርስቶስ፣ አዳኝ ክርስቶስ፣ ወገኖቹን እስራኤል ዘነፍስን የሚታደግ (የታደገ) ክርስቶስ ከአማናዊት ጽዮን ከድንግል ማርያም ወጣ፣ ተወለደ፡፡ ለድንግል ማርያም ‹‹ስሙንም ኢየሱስ ትይዋለሽ›› እንዲሁም ለዮሴፍ ‹‹ስሙን ኢየሱስ ትለዋለህ” (ሉቃ 1፡31 ማቴ 1፡21) ተብሎ በመልአኩ እንደተነገረም ስሙን ኢየሱስ አሉት፡፡

አስቀድሞ በነቢያት ስለመወለዱ ብቻ ሳይሆን ስለሚወለድበትም ቦታም፡-‹‹አንቺም የኤፍራታ ምድር ቤተልሔም ሆይ! አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ፤ ነገር ግን አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘለዓለም የሆነ፥ በእስራኤልም ላይ ገዥ የሚሆን ከአንቺ ይወጣልኛል።››(ሚክ 5፡2) እንደተባለ ታላቁ የሰማይና የምድር ንጉስ በቤተልሔም ተወለደ፡፡ ‹‹ እነሆ በኤፍራታ ሰማነው፤ ዛፍ በበዛበትም ቦታ አገኘነው፡፡››(መዝ 131፡6)ተብሎ እንደተፃፈም የሕይወት እንጀራ የሆነው መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእንጀራ ቤት  በተባለችው በቤተልሔም ተወለደ፡፡

የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ልደት የተለያዩ አካላት በተለያየ መልክ ተቀበለውታል፡፡

  1. እንስሳት

እንስሳት ትንፋሻቸውን ገበሩለት፤ በዚያ የነበሩ እንግዶች ግን ሥፍራ አልሰጡትም፡፡ ‹‹በሬ ገዢውን አህያም የጌታውን ጋጥ አወቀ፤ እስራኤል ግን አላወቁኝም፥ ሕዝቤም አላስተዋሉኝም።››(ኢሳ 1፡3) እንደተባለ እንስሳት (አድግና ላህም) አወቁት፤ ሰዎች ግን አራቁት፡፡ በእንስሳት በግርግም መተኛቱ የትህትናው ጥግ ነው፡፡ ‹‹ወራሹ ሕፃን ሳለ ለሁሉ ጌታ ሲሆን ከአገልጋይ የሚለይ አይደለም ››(ገላ 4፡1) እንደተባለ ንጹሐ ባህርይ የእግዚአብሔር በግ ኢየሱስ ክርስቶስ በጎች በሚያድሩበት በበረት ተኛ፡፡በቀዝቃዛ (ተስፋ በቆረጠ ልብ)፤ በጨለማ (ብርሀን በሌለው ኃጢአተኛ ልብ)፤ ንፁህ ባልሆነ (ኃጢአት ባጎሰቆለው ልብ) ቦታ ተወለደ (አደረ)፡፡

  1. መላእክት

የሰማይ መላእክት ልደቱን ለእረኞች አበሰሩ፤ ነገስታትን (ጥበበኞችን) ወደ ቤተልሔም መሩ፡፡ በጌታ ልደት መላእክት ከሰው ልጅ ጋር አብረው ዘመሩ፡፡ ‹‹በዚያ ሀገር እረኞች ነበሩ፤ ሌሊቱንም ተግተው መንጋቸውን ይጠብቁ ነበር፡፡ እነሆም፥ የእግዚአብሔር መልአክ በአጠገባቸው ቆመ፤ የእግዚአብሔርም ብርሃን በዙሪያቸው አበራ፤ ታላቅ ፍርሃትንም ፈሩ፡፡ መልአኩም እንዲህ አላቸው፣ “እነሆ፣ ለእናንተና ለሕዝቡ ሁሉ ደስታ የሚሆን  ታላቅ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ፡፡ እነሆ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኅን ተወልዶላችኋል፤ ይኽውም ቡሩክ ጌታ ክርስቶስ ነው፡፡ ይህም ምልክት ይሆንላችኋል፤ ሕፃን ተጠቅልሎ በግርግምም ተኝቶ ታገኛላችሁ።›› ሉቃ 2፡8-13 ይህ ለእረኞቹ የተነገረው የልደቱ ብስራት ነው፡፡የተወለደው ለመላእክት ሳይሆን ለሰው ልጆች ነውና መላእክት ተወልዶልናል ሳይሆን ተወልዶላችኋል አሉ፡፡

ይህ ታላቅ የምሥራች የእምነታችን መሠረት ነው፡፡ እምነታችን ከእግዚአብሔር ስለመሆኑ መገለጫው ይህ ነው፡፡‹‹ ወንድሞቻችን ሆይ፥ መንፈስን ሁሉ አትመኑ፤ ነገር ግን መናፍስት ከእግዚአብሔር ሆነው እንደ ሆነ መርምሩ፤ ብዙዎች ሐሰተኞች ነቢያት ወደ ዓለም መጥተዋልና። የእግዚአብሔርን መንፈስና የሐሰትን መንፈስ በዚህ ታውቃላችሁ፤ ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ እንደ መጣ የሚያምን መንፈስ ሁሉ ከእግዚአብሔር ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም በሥጋ እንደ መጣ የማያምን መንፈስ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለም፤ ይህም እንደሚመጣ የሰማችሁት ሐሳዊ መሲህ ነው፤ አሁንም እንኳ በዓለም ውስጥ አለ።›› እንደተባለው የጌታችን ልደት የተዋህዶ መሠረቷ ነው፡፡ 1ኛ ዮሐ 4፡1-3

መልአኩ አስቀድሞ ለተናቁት ለእረኞች ልደቱን አበሰረ፡፡ ‹‹ድንገትም ከዚያ መልአክ ጋር ብዙ የሰማይ ሠራዊት  እግዚአብሔርን እያመሰገኑ መጡ። “ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ ” ይሉ ነበር።›› ሉቃ 2፡14 አምላክ ሰው ሆነ፤ ሰውም አምላክ ሆነ፡፡ በመላእክት ዘንድ ምስጋና ተደረገ፤ በደቂቀ አዳምም ዘንድ አንድነት ሆነ፡፡ የሰው ፍቅር አገብሮት አምላክ ሰው ሆነ፡፡

የእግዚአብሔር መልአክ የሩቅ ነገስታትን ጌታ ወደተወለደበት ቦታ ወደ ቤተልሔም በብርሀን መራቸው፡፡ ነገስታቱ በምስራቅ ያዩት ኮከብ ሕጻኑ ባለበት ቦታ መጥቶ እስኪቆም ድረስ በሰው ቁመት ልክ ዝቅ ብሎ ይመራቸው ነበር፡፡ ይህ ኮከብ የእግዚአብሔር መልአክ ነበር፡፡ እስራኤልን በብርሃን ፋና የመራ ጥበበኞችን በኮከብ አምሳያ መርቶአቸዋል፡፡በቀን የሚያበራ፤ ወደ ምስራቅ የሚሄድ፤ ቆሞ በሰው ቁመት ወደታች የሚጠቁም መልአክ እንጂ ኮከብ አይደለም፡፡

  1. እረኞች

እረኞች የመወለዱን ብስራት ከመልአኩ ሰምተው ከመላእክት ጋር አመሰገኑ (ዘመሩ)፡፡  መልካም እረኛ እርሱ ነውና ልደቱም ቀድሞ ለእረኞች ደረሰ፡፡ ዮሐ 10፡11 እረኞቹ አመስግነውም አልቀሩም፡-‹‹እንግዲህ እስከ ቤተ ልሔም ድረስ እንሂድ እግዚአብሔርም የገለጠልንን ይህን የሆነውን ነገር እንይ ተባባሉ። ፈጥነውም መጡ ማርያምንና ዮሴፍን ሕፃኑንም በግርግም ተኝቶ አገኙ። አይተውም ስለዚህ ሕፃን የተነገረላቸውን ነገር ገለጡ። የሰሙትን ሁሉ እረኞቹ በነገሩአቸው ነገር አደነቁ፡፡›› ሉቃ 2፡15-18 እረኞች ልደቱን ሰሙ፤ አመሰገኑ፤ ፈጥነው ሄዱ (በሌሊት መንጋቸውን ትተው)፤ አዩ፤ ያዩትንም ለሌሎች ገለጡ፡፡ እረኞችም እንደ ተባለላቸው ስለ ሰሙትና ስላዩት ሁሉ እግዚአብሔርን እያመሰገኑና እያከበሩ ተመለሱ። የእውነተኛው እረኛ ልደት ለትጉሀን እረኞች ተበሰረ፡፡ በግርግም ተኝቶ ከካህናቱ ከጸሀፍቱ ሳይሆን ከእረኞች ምስጋናን ተቀበለ፡፡ የበጎች እረኞች የበጉን ልደት ከሊቃውንት ከመምህራን ከነገስታቱም ቀድመው ሰምተው አመሰገኑት፡፡

  1. የጥበብ ሰዎች

የሩቅ (የምስራቅ) ነገስታት – የጥበብ ሰዎች – ሊሰግዱለት ስጦታንም ሊያበረክቱለት መጡ፡፡ በቅርቡ የነበሩት ነገስታት በመጣው ሠራዊት ብዛትና ‹‹የተወለደው ንጉስ›› በመባሉ ደነገጡ፡፡የጥበብ ሰዎች በኮከብ (በመልአክ) ተመርተው፤ ሁለት ዓመት ተጉዘው መጥተው፤ ሰግደውለት (የነገስታት ንጉስ ነውና)፤ ወርቅን ለመንግስቱ፣ እጣንን ለክህነቱ፣ ከርቤንም ለሞቱ ገበሩለት፡፡ በነቢይ ‹‹የተርሴስና የደሴቶች ነገሥታት ስጦታን ያመጣሉ፤ የዓረብ ነገሥታት እጅ መንሻን ያመጣሉ” መዝ 71፡10። እንደተባለ የልደት (የገና) በዓል የስጦታ ቀን የሚባለውም ለዚህ ነው፡፡ የጥበብ ሰዎች ‹‹የተወለደው የአይሁድ ንጉስ ወዴት ነው?›› አሉ፡፡ ንጉስ ሆኖ የተወለደ እርሱ ብቻ ነው፡፡ ሌሎች ተወልደው ይነግሳሉ እንጂ ንጉስ ሆነው ሊወለዱ አይቻላቸውም፡፡ የጥብበ ሰዎች መወለዱንም አውቀው ስለነበር ‹‹የሚወለደው›› ሳይሆን ‹‹የተወለደው›› አሉ፡፡

  1. ሄሮድስና ኢየሩሳሌም

የሩቅ ሀገር ነገስታት በልደቱ ተደስተው አምሐ ሲያቀርቡ የቅርብ ነገስታትና ኢየሩሳሌም ግን ደነገጡ (ተረበሹ)፤ የቅርቡ ንጉስ ሄሮድስ ግን ‹‹የአይሁድ ንጉስ ተወለደ›› ሲባል ደነገጠ፡፡‹‹ የካህናት አለቆችንና የሕዝቡን ጻፎች ሁሉ ሰብስቦ “ክርስቶስ በየት ይወለዳል?” ብሎ ጠየቃቸው። እንዲህም አሉት “በይሁዳ ክፍል ቤተ ልሔም ነው፤ በነቢይ እንዲህ ተብሎ ተጽፏልና…›› አሉት ። ከዚህምበኋላ ሄሮድስ ሰብአ ሰገልን በስውር ጠራቸው፤ ኮከቡ የታየበትንም ዘመን ከእነርሱ ተረዳ፡፡ “ሂዳችሁ የዚያን ሕፃን ነገር ርግጡን መርምሩ፤ ያገኛችሁትም እንደ ሆነ እኔም መጥቼ እሰግድለት ዘንድ በእኔ በኩል ተመልሳችሁ ንገሩኝ” ብሎ ወደ ቤተ ልሔምም ሰደዳቸው። › ማቴ 2፡4-9 ሄሮድስ ይህን ያለው እንደ ቃሉ ሊሰግድለት ሳይሆን ሊገድለው አስቦ ነበር፡፡ የጌታን ልደት የቅርቡ ንጉስ ሄሮድስ ሳይሆን የሩቆቹ ነገስታት ሰብአ ሰገል ሰሙ፤ እርሱ ሲሰማ ተረበሸ፤ እነርሱ ግን ሲያገኙት ተደሰቱ፡፡

ይህንን የጌታን ልደት እኛስ እንዴት እንቀበለዋለን? እንደ ቤተልሔም ሰዎች ወይስ እንደ እረኞቹ? እንደ ጥበብ ሰዎች ወይስ እንደ ሄሮድስ? የቤተልሔም ሰዎች በምድራዊ ተግባር ተጠምደው ሌሎች እንግዶችን በማስተናገድ ሲባክኑ ጌታቸው ሲወለድ ማደሪያ መስጠት አልቻሉም፡፡ ትጉሃን እረኞች ግን ከብቶቻቸውን በትጋት ሲጠብቁ የራሳቸውን ጠባቂ አገኙት፡፡ እኛም በተግባረ ሥጋ ብቻ ተጠምደን ቤተመቅደስ የተባለ ሰውነታችንን ለጌታችን ማደሪያ ከመሆን ከልክለን እንግዳ የተባለ ኃጢአት፣ እንግዳ የተባለ የዲያብሎስ ፍሬ እንዲሰለጥንብን መፍቀድ የለብንም፡፡ የጥበብ ሰዎች አባቶቻቸው የነገሯቸውን ተስፋ አስበው፣ ሩቅ መንገድ ተጉዘው፣ አምሐ ይዘው በመምጣታቸው ከመጡበት ያለማመን መንገድ ይልቅ በሌላ የእምነት መንገድ (የክርስቶስን ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ መሆንን አምነው) ተመለሱ፡፡ (ማቴ. 2፡12)

በኢየሩሳሌም የነገሰ ሄሮድስና እረኝነታቸውን ረስተው፣ በምድራዊ ተንኮል ተጠምደው ሰማያዊ ተግባራቸውን የረሱት የአይሁድ አለቆች ግን በተስፋይቱ ምድር ተቀምጠው የጌታቸውን መወለድ ለመስማት አልታደሉም፡፡ ሲሰሙም ለክፋት እንጅ ለድኅነት አልተጠቀሙበትም፡፡ እኛም እንደ ጥበብ ሰዎች አባቶቻችን ያስተማሩንን የክርስቶስን ከሁለት አካል አንድ አካል፣ ከሁለት ባሕርይ አንድ ባሕርይ ሆኖ በሥጋ ማርያም የመገለጥ ፍቅር እያሰብን እንደ ጥበብ ሰዎች አምሐ ልናቀርብለት ይገባል፡፡ ለእግዚአብሔር የምናቀርበው አምሐም ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን ቤተመቅደስ የተባለ ሰውነታችንን እንዲሁም በዕውቀትና በእምነት የታነጸ አገልግሎታችንን ነው፡፡ (ሮሜ. 12፡1)

እንደ ሄሮድስና የአይሁድ አለቆች በተስፋይቱ ምድር በቅድስት ቤተክርስቲያን ተቀምጠን ከእግዚአብሔር ጸጋ ተለይተን እንዳንጣል ልንተጋ ያስፈልጋል፡፡ ለዚህም አብነታችን የጌታችን፣ የመድኃኒታችን እናት፣ የቅዱሳን ነቢያት ተስፋ ፍፃሜ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ናት፡፡ እርሷ የተደረገውን ሁሉ በልብዋ እያሰበች በአንክሮ ትጠብቀው ነበርና፡፡ (ሉቃ 2፡9)፡፡ የዓለም መድኃኒት መወለዱን፣ የነቢያት ትንቢት መፈፀሙን፣ የመላእክትን ምስጋና፣ የእረኞችን ምስጋና፣ የጥበብ ሰዎችን ምስጋና፣ ስግደትና ስጦታ በልብዋ አኖረችው፡፡ የምስጢር መዝገብ ናትና፡፡ እርስዋ በልብዋ ያኖረችው ነው ለእኛም የደረሰን፡፡

በዚህ ሁሉ እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍቅር እንረዳለን፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ በዚህ የእግዚአብሔር ፍቅር በእኛ ዘንድ ተገለጠ፥ በእርሱ በኩል በሕይወት እንኖር ዘንድ እግዚአብሔር አንድ ልጁን ወደ ዓለም ልኮታልና። 1ኛ ዮሐ 4፡9 እንዳለ፡፡ ይህን የእግዚአብሔርን ፍቅር መርምረን መፈጸም አንችልምና በአንክሮ እናደንቃለን፡፡

ይህን አስመልክቶ የደገኛው የባስልዮስ ወንድም፣ የኑሲስ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ጎርጎርዮስ እንዲህ አለ፡- “ለእኛም በሥጋ መገለጡን እንደሚገባው መርምረን ልናውቀው አይቻለንም፤ ጸጋን ለመስጠት ያደረገውን ተዋሕዶ የሚያምኑት ሰዎች ከእነርሱ ትምህርትን ይቀበሉ ዘንድ ይገባል ብሎ ቃል ስለእነርሱ ከተናገረላቸው ከመምህራን እንማር ዘንድ ያሻናል፡፡” ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ጎርጎርዮስ 35፡10፡፡ ስለዚህ ሁላችንም የተደረገልንን ድንቅ ተዓምር፣ የተሰጠንን ድንቅ ስጦታ እያሰብን ከቅዱስ ኤፍሬም ጋር እናመስግን፡- “በቅዱሳን ላይ የሚያድር እግዚአብሔር እኛን ለማዳን ልዩ ከሆነች ድንግል ሰው ሆኗልና፣ ኑ ይህን ድንቅ እዩ፣ ስለተገለጠልን ምስጢር ምስጋና አቅርቡ፣ ሰው የማይሆን ሰው ሆኗልና፣ ቃል ተዋህዷልና፣ ጥንት የሌለው ሥጋ ጥንታዊ ቀዳማዊ ሆነ፣ ዘመን የማይቆጠርለት መለኮት ዘመን ተቆጠረለት፣ የማይታወቅ ተገለጠ፣ የማይታይ ታየ፣ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ በእርግጥ ሰው ሆነ” የረቡዕ ውዳሴ ማርያም፡፡

የተደረገልንን አስበን የጌታችንን ልደት እንደ ዮሴፍና ሰሎሜ በአንክሮ፣ እንደ ጥበብ ሰዎች በአምሐ፣ እንደ ቤተልሔም እረኞች አገልግሎታችንን በትጋት በመፈጸም፣ እንደ ቅዱሳን መላእክት በሰማያዊ ምስጋና እንድናከብር የቅዱሳን አምላክ፣ የአብ የባህርይ ልጅ፣ የድንግል ማርያም ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ በቸርነቱ ይጎብኘን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

1 thought on “መድኅን ተወልዶላችኋል!

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s