የሐዋርያዊ ጉዞ መርሆች: ሰባኪ በመምጣቱ ምን ለውጥ መጣ?

sebaki

ከዚህ አስቀድሞ ባስነበብነው የአስተምህሮ ጦማር የሐዋርያዊ ጉዞ አስፈላጊነትና ተያይዘው የሚስተዋሉ ችግሮች ተዳስሰዋል፡፡ እነዚህን ችግሮች በዝርዝር የዳሰስነው የችግሩን ስፋት፣ጥልቀትና የሚያመጣውን ጣጣ በአግባቡ በማሳየት የመፍትሔ ሀሳብ ለማመላከት ነው፡፡ የተጠቀሱት ችግሮች ሰባክያኑንም፣ ምዕመናንንም፣ በአጠቃላይ ቤተክርስቲያንን የሚጎዱ ከመሆናቸው አንጻር የመፍትሔ ሀሳቦችም የሚጠቅሙት ለሁሉም ነው፡፡ በቅድሚያ ሰባኪ (መምህር) ከሌላ ቦታ የማስመጣት አስፈላጊነቱን ሁሉም አካል ሊያምንበት ይገባል፡፡ የሚመጣበት ዓላማም ንጹሕ ለሆነ የወንጌል አገልግሎት እንጂ ሌላ ዓላማ መሆን የለበትም፡፡ ሰባኪ ማስመጣቱ አስፈላጊ መሆኑ ከታመነበት ትግበራው መሠረታዊ የሚባሉ የአሠራር መርሆዎችን መከተል ይገባዋል፡፡ ለአንድ ችግር መፍትሄ ከመፈለግ በፊት የችግሩን ምንነት፣ መነሻና ያለበትን ደረጃ መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ሰባክያንን ከማስመጣት ጋር ተያይዞ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት የሚያስችል አሰራርና አስተሳሰብም የችግሩን ምንጮች፣ መገለጫዎችና የሚያስከትለውን ጉዳት በሚገባ ከመረዳት መጀመር አለበት፡፡ ችግሩን መገንዘብም ሆነ የመፍትሄ አቅጣጫው ከምዕመናን ጀምሮ እስከ ከፍተኛ የቤተክርስቲያን አስተዳደር አካላት ድረስ ካልተሳተፉበት ውጤታማ አይሆንም፡፡ ለዚህም እንዲረዳ በየደረጃው ያሉ የቤተክርስቲያን አካላት ቢከተሏቸው ይጠቅማሉ የምንላቸውን የመፍትሔ ሀሳቦች በሰባት የትግበራ መርሆች (principles of implementation) ሥር አካተን አቅርበናል፡፡

የትኛው መምህር በየትኛው መዋቅር ይምጣ?

የቤተክርስቲያናችን መምህራን (ሰባክያነ ወንጌል) የተለያየ የማስተማር ጸጋ አላቸው፡፡ ከእውነተኞቹ መምህራን መካከል ማንም መጥቶ በውጭ ወይም በሀገር ውስጥ ባሉት አብያተ ክርስቲያናት ቢያስተምር ዋጋ ያገኝበታል፣ ምዕመናንም ይጠቀሙበታል፣ ይባረኩበታል፡፡ ነገር ግን የመምህራኑ አመራረጥ ባላቸው የማስተማር ጸጋ፣ የአገልግሎት ጊዜና ወጥነት ባለው የመምህራን ስምሪት መመሪያ መሠረት በሚሰጣቸው ምደባ ሊሆን ይገባል እንላለን፡፡

ሰባክያን የሚመረጡበት መስፈርት ብልሹ መሆን አንዱ የዘመናችን ሐዋርያዊ ጉዞ ችግር ነው። በዘመናችን በተለይም ሥጋዊ ጥቅም ባለባቸው ታላላቅ የኢትዮጵያ ከተሞችና በውጭው ዓለም ባለው አሠራር መምህር የሚመረጠው በትውውቅ፣ በጥቅም፣ በመንደርተኝነት ወይም በዝምድና በተሣሠሩ “የደላላዎች” ሠንሠለት አማካይነት መሆኑ የቤተክርስቲያንን አገልግሎት በእጅጉ እየጎዳው ይገኛል፡፡ ምዕመኑ ምንም ባላወቀበት ሁኔታ ጥቂት ግለሰቦች የፈለጉትን ሰው የሚልኩበት፣ ያልፈለጉትን ደግሞ የሚገፉበት ሁኔታ ተፈጥሮአል፡፡ የመምህራን ስምሪትን መምራት የሚገባው የቤተክርስቲያኒቱ አካል በሀገር ውስጥና ከሀገር ወጭ ለስብከት የሚሰማሩ መምህራን የሚመሩበትን ሥርዓትና መመሪያ በተሟላ መልኩ ሊተገብረው ይገባል፡፡ በውጭ ሀገር አጥቢያ ቤተክርስቲያናት፣ ሀገረ ስብከቶች ወይም ሌሎች የአገልግሎት ማኅበራት መምህራነ ወንጌልን ሲፈልጉ ሥርዓትን ባለው መልኩ በቤተክርስቲያኒቱ ተቋማዊ አስተዳደር በኩል የሚታወቁ መምህራንን ማስመጣት ይገባቸዋል፡፡ ለየትኛው ቦታ የትኛው መምህር በየትኛው ጊዜ አገልግሎት ይስጥ የሚለው ጉዳይ አሁን ካለው በተሻለ ሊታሰብበት ይገባል፡፡

በአስተምህሮ ምልከታ “የትኛው መምህር ይምጣ?” የሚለው ጉዳይ በአብዛኛው “በአስመጭዎችና ላኪዎች” ፍላጎት ላይ የተመሠረተ ይመስላል፡፡ በአንዳንዶች ዘንድም “ታዋቂ (ባለዝና)” እና ብዙ ሰው/ገንዘብ ሊሰበስቡ የሚችሉ መምህራን ላይ የማተኮሩ ሁኔታ ይታያል፡፡ ይህም “ምን ያህል ገቢ ያስገባል?” የሚለውን እንደ መስፈርት እየተጠቀሙበት ያሉ ያስመስላል፡፡ መምህር የሚመጣው ገቢ ለማሰባስብ ከሆነ ከሆነ በጣም አደገኛ ውጤት እንደሚኖረው የታወቀ ነው፡፡ ስለሆነም መምህራን ሲመረጡ በመንፈሳዊ አገልግሎት መመዘኛነት ቢሆንና በተቻለ መጠንም በክህነት አገልግሎት የሚራዱና ምዕመናንን የሚመክሩ ሊሆኑ ይገባል። ከአማርኛ ውጭ ቋንቋ በሚነገርባቸው የሀገራችን ኢትዮጵያና በውጭ ሀገራት ለአገልግሎት የቋንቋ ጉዳይ መሰረታዊ ስለሆነ የአካባቢውን ቋንቋ (በተለይም የቤተክርስቲያን ተረካቢ የሆኑ ወጣቶች የሚግባቡበትን ቋንቋ) ማስተማር የሚችሉ መምህራን አንጻራዊ ተመራጭነት ሊኖራቸው ይገባል፡፡

መጥቶስ ምን ያስተምር?

መምህር የሚጋበዘው እንዲያስተምር፣ ሰባኪም የሚመጣው ሊሰብክ እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡ ነገር ግን አሁን ባለው ሁኔታ መምህር ማስመጣቱ ላይ እንጂ “መጥቶ ምንድን (ስለምን) ነው የሚያስተምረው?” የሚለው ጉዳይ በቂ ትኩረት አልተሰጠውም፡፡ በአብዛኛው መምህሩ ራሱ የፈቀደውን (ልቡ የወደደውን) ወይም ለማስተማር የሚቀለውን  (ብዙ ጊዜ ያስተማረውን ወይም አዲስ ዝግጅት የማያስፈልገውን) አስተምሮ (ሰብኮ) ይሄዳል፡፡ የሚያስተምረው ትምህርት የቤተክርስቲያን ቢሆንም ለምዕመናኑ የበለጠ የሚያስፈልገውን ትምህርት ቢያስተምር ግን መልካም ነው፡፡ አዲስ አበባ እና አሜሪካ ያለው ምዕመን በሕይወት መስተጋብሩ የተለያየ ስለሆነ ከሕይወቱ ጋር የተዛመደ ትምህርት ያስፈልገዋል፡፡ ብዙ ጊዜ የተሰበከውን መልሶ መላልሶ ከማስተማር ይልቅ በጥልቀት ያልተዳሰሱ አርዕስትን ማስተማርም መልካም ይሆናል፡፡ ይህ ማለት ግን በሚገባ የታሰበበትን ትምህርት ማስተማር ይገባል እንጂ በአንዳንዶች ዘንድ ልማድ እንደሆነው መንፈሳዊ ረብ የሌላቸውን ተራ ቀልዶችና መንፈሳዊነት የጎደላቸውን ንግሮች ማድረግ መምህሩንም ቤተክርስቲያንንም ያስንቃል፡፡

ተጋባዥ ሰባክያን የሚሰብኩት ስብከት ምን ያህል ምዕመናንን ያንፃል የሚለው ጉዳይ ጥናት የሚያስፈልገው ቢሆንም የትምህርቱ ተከታታይነት ማጣትና ተደጋጋሚ መሆን ግን በግልፅ የሚታይ ችግር ነው። በአንድ ወቅት አንድ የእነዚህ ከሌላ ቦታ ለተወሰነ ጊዜ የሚመጡ መምህራንን ትምህርት ሲከታተሉ የነበሩ ምዕመን “ሁሉም መምህራን ትምህርታቸውን ከአዳምና ከሔዋን ይጀምራሉ፡፡ አንዱ አብርሃም ላይ ሲደርስ ጊዜው አልቆ ይሄዳል፡፡ ሌላው የሙሴ መሪነት ላይ ሲደርስ ይሄዳል፡፡ የበረታው ደግሞ ዳዊት ላይ ያደርሰናል፡፡ እንደዚህ እያልን ሁል ጊዜ ከአዳምና ከሔዋን እንደገና እየጀመርን አዲስ ኪዳን ላይ የሚያደርሰን አጥተን ብሉይ ኪዳንን እንደ ዳዊት እየደገምን ነው” ብለዋል፡፡ አዲስ መምህር ሲመጣ ቢያንስ ያለፈው ያስተማረውን ባይደግም መልካም ነው፡፡ ቢቻል ካለፈው የሚቀጥል ትምህርት ቢሰጥ ተመራጭ ነው፡፡ የሚመጣው መምህር እዚያው ላሉት መምህራን (ሰባክያን) አጭር ስልጠና የሚሰጥ ቢሆን ይመረጣል፡፡ ለጉባዔና ለሌሎች አገልግሎቶች በአቅራቢያው ባሉ አጥቢያ ቤተክርስቲያናት፣ በማኅበራትና በሌሎችም መድረኮች እንዲያስተምር ነጻነት ሊሰጠውም ይገባል እንጂ በአንዳንዶች ዘንድ ልማድ እንደሆነው “እኛ ያስመጣነው መምህር ከእኛ ደብር ውጪ ማስተማር የለበትም” የሚል ፍጹም መንፈሳዊነትም፣ አስተዋይነትም የጎደለውን አሰራር መከተል አይገባም፡፡

በሌላ መልኩ አንዳንድ መምህራን እውነተኛውን ትምህርት ከማስተማር ይልቅ ብዙም ጥልቀት የሌለው ነገር ላይ በማተኮርና የኮሜዲያን ፍርፋሪ የሆኑ እርባና ቢስ ቀልዶችን በመቀለድ የቤተክርስቲያንን መድረክ ለማይገባ ዓላማ ያውላሉ፡፡ ከሚያስተምሩት ትምህርት ጋር የማይገናኝ መናኛ ቀልድና ተረታ ተረት በማብዛት እንደ አርቲስት የመወደድ ፍላጎት ያሳያሉ፡፡ በዚህም የቤተክርቲያንን ሀብት ለብክነት፣ የምዕመናንንም ጊዜ እንቶ ፈንቶ ለመስማት፣ የራሳቸውንም የአገልግሎት ዕድል አልባሌ ነገር ይዳርጉታል፡፡ አንዳንዶችም ከማስተማር ይልቅ ቀሚስና ካባ እየቀያየሩ መታየትን ገንዘብ ያደረጉ ይመስላል፡፡ ወደ ውጭ ሀገር ሄዶ ማስተማር እንደ ትልቅ “የዕድገት ዕርከን” የሚወስዱትና “ዓለም አቀፍ ሰባኪ” ለመባል የሚተጉ ለዚህም ለደላሎች መማለጃን የሚያቀርቡም “መምህራንም” አይታጡም፡፡ ሀገር ማየት ወይም የተሻለ ገንዘብ ማግኘት መጥፎ ነገር ባይሆንም ይህ ተቀዳሚ ዓላማ ሲሆን ግን ቤተክርስቲያንን ይጎዳታል፡፡

ስለዚህ አንድ መምህር ሲመጣ/ሲላክ “ምንድን ነው የሚያስተምረው?” የሚለው ጥያቄ አስቀድሞ መመለስ አለበት፡፡ ለዚህም የሁሉም ሀሳብ መሰማት ይኖርበታል፡፡ ምዕመኑም “መምህሩ ሲመጣ ምንድን ነው የሚያስተምረን (ምንድን ነው የምንማረው)?” ብሎ ቢጠይቅ መልካም ነው፡፡ አስተባባሪዎችም ይህንን ጥያቄ አስቀድመው መመለስ ይኖርባቸዋል፡፡ መምህሩ ምን እንደሚያስተምር እንኳን ሳይነገረው ወደ ቤተክርስቲያን በእምነት የሚመጣው ምዕመን ምን እንደሚማር አውቆ ቢመጣ ደግሞ ምን ያህል የተሻለ ይሆን ነበር?

መቼና ለምን ያህል ጊዜ ይምጣ?

አንዳንድ ሰባክያን በተለይ ወደ ውጭ ሀገር የሚመጡበት ጊዜ ብዙ ያልታቀደበትና የምዕመናንን የሥራ ሁኔታ ያላገናዘበ መሆን ሌላው የዘመናችን ሐዋርያዊ ጉዞ ችግር ነው። የቆይታ ጊዜ ጉዳይ ከሀገር ቤት ሐዋርያዊ ጉዞዎች ይልቅ በውጭ ሀገራት በሚደረጉ ጉዞዎች ላይ ትኩረትን የሚጠይቅ ነው፡፡ በውጭ ሀገር የሚኖረው ምዕመን ሩጫ  (የሥራ ጫና) የበዛበት ነው፡፡ ከዚህም የተነሳ ብዙ ሰው ያለው ጊዜ በጣም አነስተኛ ከመሆኑ አንጻር አብዛኛው ሰው ወደ ቤተክርስቲያን የሚሄደው በሳምንት አንድ ጊዜ (እሁድ ለቅዳሴ) ነው፡፡ ለሰባክያኑ የሚሰጣቸው የየሀገራቱ የቪዛ ሁኔታ የተለያየ ነው፡፡ ሰባክያኑ ያላቸው ጊዜና ለቆይታቸው የሚያስፈልገው ወጭም ከግምት ውስጥ ገብቶ በተጋበዙበት ሀገር መቆየት የሚችሉት ለተወሰነ ጊዜ (ለጥቂት ሳምንታት) ብቻ ነው፡፡ በእነዚህ ምክንያቶች መምህሩ የሚመጣበት ጊዜ በጣም ታስቦበት እና ተመክሮበት ሊሆን ይገባል፡፡ መምህሩ የሚመጣበት ወቅት እንደየሀገሩ ሁኔታ ምዕመናን የተሻለ ጊዜ የሚያገኙበት (ለምሳሌ የዓመቱ መጨረሻ) ወይም በቤተክርስቲያን ታላላቅ አጽዋማት (ዐቢይ ጾም ወይም ፍልሰታ) ቢሆን የተሻለ ነው፡፡ መምህሩ የሚመቸው ጊዜ ብቻ ተወስዶ ወይም ‘ሌሎች አጥቢያዎች መምህር ስላመጡ እኛም እናስመጣ’ ተብሎ በፉክክር የሚመጣ ከሆነ እንዲሁ የሚፈለገውን ያህል ውጤታማ ላይሆን ይችላል፡፡

ማንንና እንዴት ያስተምር?

የተሰበከውን ምዕመን እየደጋገሙ መስበክ ክፋት ባይኖረውም ስብከት የበለጠ ለሚያስፈልገው መድረስ ግን የበለጠ ዋጋ ያስገኛል። የተለመደው የማስተማር ዘዴ በቤተክርስቲያን መድረክ እና በአዳራሽ መምህሩ አትሮኑስ ጀርባ ቆሞ፣ ምዕመናን ከፊቱ ካህናት ከኋላው/ከፊት ለፊት/ ተቀምጠው፣ መጠየቅ እና የሀሳብ መንሸራሸር የሌለበት፣ ሁሉም የሰማውን ‘አሜን እና እልል’ ብሎ የሚቀበልበት የአንድ አቅጣጫ  (one-directional) የትምህርት ፍሰት ነው፡፡ ነገር ግን በእነዚህ መድረኮች የሚገኘው ምዕመን የዕድሜና የጾታ ስብጥሩ መሠረታዊ ትምህርትን ለማስተማር አያስደፍርም፡፡ የቋንቋም ሆነ የመረዳት ልዩነቶች በአደባባይ ባሉ መድረኮች አይስተናገዱም፡፡ በአጥቢያ ቤተክርስቲያናት በዕድሜ ሕፃናት፣ ታዳጊ ልጆች፣ ወጣቶች፣ ጎልማሶችና አረጋውያን ይገኛሉ፡፡ በጾታም ወንዶች፣ ሴቶችና ካህናት አሉ፡፡ በትምህርት ደረጃም እንዲሁ ጀማሪዎች፣ ማዕከላዊያንና የበሰሉት አሉ፡፡ በሥራ ሁኔታም ቢሆን ተማሪዎች፣ ሠራተኞች፣ ጡረተኞች ይኖራሉ፡፡ በትዳርም እንዲሁ ያገቡና ልጆችን የሚያሳድጉ፣ ትዳር ለመመስረት የሚያስቡ፣ ዕድሜያቸው ለትዳር ያልደረሰ አሉ፡፡ በቋንቋም እንዲሁ አማርኛ፣ ኦሮምኛ፣ ትግርኛ… እንግሊዝኛ የሚናገሩ አሉ፡፡ እነዚህ እንደየደረጃቸው የተለያየ ትምህርት ያስፈልጋቸዋል፡፡ የትምህርቱ አሰጣጥ ዘዴም እንዲሁ ሊለያይ ይገባል፡፡ በግል፣ በቡድን፣ በማኅበር፣ በአደባባይ፣ በቃል፣ በጽሑፍ የሚማር ይኖራል፡፡ እነዚህ ሁሉ የምዕመናን ክፍሎችና የማስተማሪያ ስልቶች እያሉ አንድ አይነት ስልት ለሁሉም (one size fits all) መጠቀም ውጤታማ አያደርግም፡፡ ስለዚህ ዘርፈ ብዙ የማስተማሪያ ዘዴዎችንና ጊዜያትን መጠቀም ያስፈልጋል፡፡ ከሌላ ሀገር/ቦታ የሚመጣውም መምህር እነዚህን ሊጠቀም ይገባዋል፡፡

ለቆይታው የሚያስፈልገው የት ይዘጋጅለት?

በውጭው ዓለም ለማስተማር ለአጭር ጊዜ የሚመጡ መምህራን በምዕመናን ቤት እንዲያርፉ ማድረግ የተለመደ አሠራር ነው፡፡ አልፎ አልፎም ሁሉ የተሟላለት ቤት (ሆቴል) የመከራየት ነገር ይታያል፡፡ ምዕመናንን እውነተኞቹን የቤተክርስቲያን መምህራንን ተቀብለው በቤታቸው በማስተናገዳቸው በረከትን ያገኛሉ፡፡ መምህሩም ቤተሰቡን ለማስተማር ዕድል ያገኛል፡፡ ነገር ግን ረዘም ላለ ጊዜ ለሚቆዩ መምህራን በአንድ ምዕመን (ቤተሰብ) ቤት ብቻ መቆየት ምዕመኑ ላይ ጫና እንዳያሳድር፣ ለመምህሩም መሳቀቅን እንዳያመጣ አስቀድሞ ማቀድ ያስፈልጋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ምዕመናኑ መምህራኑን በቤታቸው ተቀብለው የሚያስተናግዱት የሚያገኙትን ዋጋ አውቀውት፣ ተረድተውት፣ አምነውበትና በራሳቸው ነፃ ፍላጎት ወስነውና ጠይቀው ሊሆን ይገባል እንጂ በጫና ባይሆን ይመረጣል፡፡

ለመምህሩ የሚሆን ማረፊያ በቤተክርስቲያኑ ውስጥ ማዘጋጀት ግን ከሁሉም የተሻለ አማራጭ ነው፡፡ ይህም በብዙ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት የተለመደ አሠራርና የቤተክርስቲያን ሥርዓትም ነው፡፡ ለዚህም አብያተ ክርስቲያናቱ የእንግዳ ማረፊያ ያዘጋጃሉ፡፡ ለአገልግሎት የመመጡ መምህራንም በዚያው ያርፋሉ፡፡ የመምህራኑ በቤተክርስቲያን ግቢ ውስጥ መቆየት ምዕመናንም ባላቸው ጊዜ ሄደው እንዲጎበኟቸው፣ ትምህርት እንዲማሩና ምክር እንዲቀበሉ ያግዛል፡፡ መምህሩም ለማስተማርም ሆነ ለመምከር እንዲሁም ለጸሎት ከዚህ የተሻለ አማራጭ የለም፡፡ የቤተክርስቲያን አገልጋይ ለሆነ መምህር በቤተክርስቲያን ቅጥር ውስጥ ባለ ማረፊያ ውስጥ ማረፍ እውነተኛ እረፍትን ይሰጠዋል፡፡

ላበረከተው አገልግሎት ስንት ይከፈለው?

ይህ ጥያቄ ለብዙዎች “አዲስ ነገር” ሊሆን ይችላል ነገር ግን ለተጋባዥ መምህራን ገንዘብ መክፈል የተለመደ አሠራር ነው። ከዚህም ጋር በተያያዘ በዘመናችን ሰባኪ ማስመጣት በቤተክርስቲያን ላይ የሚፈጥረውን ጫና በባለፈው ጦማር አቅርበናል። ፍጹም የሚባለው የሐዋርያነት አገልግሎት እንደ ቅዱሳን ሐዋርያትና እነርሱን መስለው በየዘመናቱ ቤተክርስቲያንን ያለምድራዊ ዋጋ ያገለገሉ፣ በዚህም አብነታቸው “ዋኖቻችን” የሆኑት ታላላቅ ቅዱሳንን መምሰል ነው፡፡ ስለሆነም ይህን መሰሉ መንፈሳዊ አገልግሎት ቢቻል ለራስ እየተጎዱ ለሌሎች ብርሃን መሆን፣ ባይቻል ግን ቢያንስ አላግባብ መበልጸግን (unjust enrichment) የሚያመጣ መሆን የለበትም፡፡ ለዚያ ነው ጌታችን ደቀመዛሙርቱን ለአገልግሎት ሲልካቸው “ያለዋጋ የተቀበላችሁትን ያለ ዋጋ ስጡ፡፡ በመቀነታችሁም ወርቅ ወይም ብር ወይም መሐለቅ አትያዙ፡፡ ለመንገድም ስልቻ ወይም ሁለት ልብስ ወይም ሁለት ጫማ ወይም በትር አትያዙ፤ ለሠራተኛ ዋጋው ይገባዋልና፡፡” (ማቴ. 10፡8-10) በማለት ደቀመዛሙርቱን ያስጠነቀቀቃቸው፡፡ ስለሆነም ለወንጌል አገልግሎት የሚጣደፉ አገልጋዮች ቢችሉ ከመጓጓዣ፣ ምግብና መኝታ ውጭ ያለምንም ምድራዊ ክፍያ ቢያገለግሉ ዋጋቸው ታላቅ ነው፡፡ ይሁንና ገንዘብን ማዕከል ያደረገ የኑሮ ዘይቤ በገነነበት ዓለም አገልጋዮችም የእግዚአብሔርን ቃል ለገንዘብ ማግኛነትና ሰዎችን ለማስደሰት እስካልሸቀጡ ድረስ በግልጽ የሚታወቅ፣ ማጭበርበርና ማስመሰል የሌለበት፣ ምክንያታዊ የድካም ዋጋ ቢከፈላቸው የሚያስነቅፍ አይደለም፡፡

ቅዱስ ወንጌል “ለሠራተኛ ዋጋው ይገባዋል” የሚለው ይህን መሰሉን ወጭን የመሸፈን (cost replacement) አሠራር ብቻ ነው፡፡ ፍጹማን የሆኑ ቅዱሳን ሐዋርያትና እነርሱን መስለው በየዘመናቱ ቤተክርስቲያንን በማገልገል የከበሩ ቅዱሳን ግን ለአገልግሎት የሚሆናቸውን ወጭም በራሳቸው እየሸፈኑ የማንም ሸክም ሳይሆኑ ያገለግሉ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ምዕመናን በላከው መልዕክቱ “እናንተ ከፍ ከፍ ትሉ ዘንድ የእግዚአብሔርን ወንጌል ያለ ዋጋ አስተምሬአችኋለሁና፡፡ እናንተን አገለግል ዘንድ ከሌሎች አብያተ ክርስቲያናት  ተቀብዬ ለምግቤ ያህል ወሰድሁ፤ ከእናንተ ዘንድ በነበርሁበት ጊዜም ስቸገር ገንዘባችሁን አልተመኘሁም፡፡ ባልበቃኝም ጊዜ ወንድሞቻችን ከመቄዶንያ መጥተው አሟሉልኝ፤ በእናንተም ላይ እንዳልከብድባችሁ በሁሉ ተጠነቀቅሁ፤ ወደፊትም እጠነቀቃለሁ፡፡” (2ኛ ቆሮ. 11፡7-9) በማለት የተናገረው ቃል በየዘመኑ ለሚነሱ የወንጌል መመህራን ሁሉ መርህ ሊሆን የሚገባው ነው፡፡

የመንፈሳዊ አገልግሎት ዋጋው በሰማይ የሚገኝ ነው፡፡ ነገር ግን “የሚያበራየውን በሬ አፉን አትሠረው” እንደተባለ ለጊዜውም ሆነ በዘላቂነት ለሚያስተምሩ መምህራን ተገቢውን የአገልግሎት ክፍያ መክፈል ተገቢ ነው፡፡ ይህም የየአጥቢያ ቤተክርስቲያኑን የገንዘብ አቅምና የተሰጠውን አገልግሎት ከግምት ውስጥ ያስገባ መሆን ቢጠበቅበትም ለምዕመናኑ ግልጽ የሆነ ተቋማዊ አሠራር ሊኖረው ይገባል፡፡ “አጥቢያዎች እንደቻሉ ይክፈሉ” ከተባለ እንደየሁኔታው የተለያየ መጠን እየከፈሉ መምህራኑ የተሻለ ለሚከፍላቸው ቅድሚያ ሊሰጡ ይችላሉ፡፡ በዚህም ብዙ የመክፈል አቅም የሌላቸው አጥቢያዎች የሚፈልጉትን መምህር በሚፈልጉት ጊዜ ላያገኙ ይችላሉ፡፡ በጥቂቶቹ ዘንድ እንደሚደረገውም የመምህሩ ክፍያ ባስገባው ገቢ (ፐርሰንት) ከሆነ መምህራኑ በነጻነት ከማስተማር ይልቅ “ምን ያህል ገቢ አስገባ ይሆን?” በሚል የሂሳብ ሥራ እንዲፈተኑ ይጋብዛል፡፡ ስለዚህ ቤተክርስቲያናችን በተለይ ወደ ውጭ ሀገር ለሚሰማሩ መምህራን ተገማችነት ያለው የክፍያ አሰራር መመሪያ ሊኖራት ይገባል፡፡

ይሁንና ይህ የክፍያ አሠራር ቤተክርስቲያንን እንደቀጣሪ ተቋም ተጠግተው ብዙ የሥራ እድል ባለባቸው ቦታዎች ሁሉ በስንፍና የቤተክርስቲያንን ገንዘብ መውሰድን የሚያበረታታ መሆን የለበትም፡፡ አከፋፈሉም ከምዕመናን በተለየ ሁኔታ ካህናት ለአገልግሎት የሚያውሉትን ጊዜ ታሳቢ ያደረገ መሆን አለበት እንጂ በሣምንት አንድ ቀን በዕለተ ሰንበት እንደማንኛውም ምዕመን ወደ ቤተክርስቲያን መጥተው የሚቀድሱትን ወይም የሚያስተምሩትን ካህናት ሊያጠቃልል አይገባውም፡፡ አንዱ በአበል የሚቀድስ፣ የሚያስቀድስ ሌላው ያለ አበል የሚቀድስ፣ የሚያስቀድስበት አሠራር ምንደኞችን እንጂ እውነተኛ አገልጋዮችን አይጠቅምም፡፡ ስለሆነም አፈጻጸሙ እንደየሀገሩና ከተማው ሁኔታ፣ እንደ አጥቢያ ቤተክርስቲያኑ አሠራር፣ እንደ አገልጋዩ የአገልግሎት ትጋትና የገቢ ሁኔታ እየታየ ግልጽ በሆነ አሠራር ሊተገበር ይገባል እንጂ የቤተክርስቲያን አገልግሎት የግለሰቦች መሸላለሚያና ሥጋዊ ጥቅም ማካበቻ መሆን የለበትም፡፡

ሰባኪ በመምጣቱ ምን ለውጥ መጣ?

በአንዳንድ አጥቢያ ቤተክርስቲያናት ብዙ ሰባክያን መጥተው ሰብከዋል፡፡ የቤተክርስቲያን ሀብትም የምዕመናኑ ዕንቁ ጊዜም ለዚህ አገልግሎት ውሏል፡፡ ነገር ግን (የሕይወት ለውጥ ጊዜ የሚወስድና ለመለካት የሚያስቸግር ቢሆንም) “ይህ በመደረጉ ምን ለውጥ መጣ?” የሚለው ጥያቄ መመለስ አለበት፡፡ ምን ያህል አዳዲስ ምዕመናን ወደ ቤተክርስቲያን መጡ? ይመጡ ከነበሩት ውስጥ ምን ያህሉ ለንስሐና ለቅዱስ ቁርባን በቁ? ከተማሩት/ከሰለጠኑት ውስጥ ምን ያህሉ ወደ አገልግሎት ተሰማሩ? የምዕመናን ሱታፌ በምን ያህል ተሻሻለ? የተገኘው ለውጥ ከተፈጸመው አገልግሎትና ከፈሰሰው ገንዘብ አንጻር እንዴት ይታያል? የሚሉትን ጥያቄዎች መመለስ ያስፈልጋል፡፡ መምህራንን ከሩቅ ሀገር ማስመጣትም ያለውን የመምህራን ችግር ለጊዜው ማስታገሻ መድኃኒት እንጂ ዘላቂ መፍትሔ ተደርጎ መወሰድም የለበትም፡፡ በቂ ስልጠና ያላቸው መምህራንን በቋሚነት እንዲያገለግሉ ማድረግ ያስፈልጋል እንጂ በየጊዜው ብዙ ወጭ በማውጣት ለአጭር ጊዜ ብቻ መምህራንን እያፈራረቁ ማስመጣት ዘላቂ ለውጥን አያመጣም፡፡

በአጠቃላይ ሰባኪ ለማስመጣት ሲታሰብ አስቀድሞ ‘ሰባኪ ማምጣት ለምን አስፈለገ? ያሉትን ሰባክያን በሚገባ ተጠቅመናል ወይ? ሰባኪ ለማምጣት ለሚወጣው ወጪ ሚዛን የሚደፋ ምክንያት አለ ወይ? ሰባኪው በቆይታው የሚያስተምረው ትምህርት ትኩረት ምን ላይ ይሆናል? ስብከቱስ በምዕመናን ክርስቲያናዊ ሕይወት ዙሪያስ ምን አስተዋጽኦ ሊኖረው ይችላል?’ የሚሉትን ጥያቄዎች በሚገባ መመለስ ይገባል። የማስመጣቱ ሀሳብም ሲታመንበት ሰባቱን የትግበራ መርሆች መጠቀም ይበጃል። በተጨማሪም ለወንጌል አገልግሎት የተጠራ ሰባኪ ሙሉ ትኩረቱን ስብከት ላይ እንዲያደርግ ሁኔታዎችን ማመቻቸት ያስፈልጋል። የስብከት ቦታውም የቤተክርስቲያን ዐውደ ምህረት እንጂ (የተለየ አስገዳጅ ሁኔታ ካልተፈጠረ በቀር) ተራ አዳራሽ መሆን የለበትም። ሐዋርያዊ አገልግሎቱ የቤተክርስቲያኒቱን አስተምህሮ የጠነቀቀ፣ ሥርዓቷን የጠበቀ፣ ትውፊቷንም የዋጀ እንዲሆን ሁሉም ምዕመን የራሱን ድርሻ እንዲያበረክት ማድረግ ያስፈልጋል። በመጨረሻም ሰባኪ በመምጣቱ የመጣውን ለውጥ በተቋም ደረጃ በየጊዜው መመዘን ያስፈልጋል እንላለን። †

1 thought on “የሐዋርያዊ ጉዞ መርሆች: ሰባኪ በመምጣቱ ምን ለውጥ መጣ?

  1. Astemhero zetwahedo: ቃለ ህይወቱን ያሰማልን ፡

    በዳያስፖራ ያላቸው ቤተክርስቲያን 19 አመት ድፍን ሳውቃት መምህር በማስመጣት የተጎዳች አትመስልም እኔንም ብዙ ነገረ ወሰድጃለሁ ተምራሌሁ however አንድ ነገር አለ ሁሌ ካንሰር በሽታ የሆነብን አስተዳዳሪ ላይ ነው በጣም ከባድ የሆነ ችግር አለ። የአስተዳደሩ ለወጥ ያስፈልጋል ለንደን ሀገር 5 ካህናት ያሉበት ቤተክርስቲያን አንደ አስተዳዳሪው ለዘመናት ቁጭ ያለበት ሁኔታዎች አሉ እዚህም ሀገር ሜልቦርን ብንመለከት በ3 በ4 እየተከፈሉ ቤተክርስቲያኒቱ የግል ቤታቸው ካደረጉ ቆይተዋል። ስለዚህ እነዚህን ግድፈቶች ተመለከቱና ትምህርት እንጠብቃለን።

    Like

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s