ሰባኪ ማስመጣት: የዘመናችን ሐዋርያዊ ጉዞና ዓለማዊ ጓዙ

መግቢያ

ከዘመነ ሐዋርያት ጀምሮ ቅድስት ቤተክርስቲያን ከምትታወቅባቸው ጸጋን የሚያሰጡ አገልግሎቶች አንዱ በቃለ እግዚአብሔር እጦት ለተራቡት ምዕመናን እየተዘዋወሩ የክርስቶስን ወንጌለ መንግስት በማስተማር አዳዲስ ምዕመናንን ማፍራት፣ እንዲሁም ያሉትን ምዕመናን በምግባርና በሃይማኖት እንዲጸኑ የማድረግ አገልግሎት ነው፡፡ በዚህች የአስተምህሮ ጦማር በዘመናችን ሐዋርያትን አብነት ያደረጉ ተዘዋውሮ የማስተማር አገልግሎቶችንና መልካም ማሳ የሆነውን አገልግሎት በሂደት እየወረሩ የመጡትን አረም የሆኑ ክፉ ልማዶች እንዳስሳለን። በቀጣይ በምናወጣው ክፍል ደግሞ የመፍትሔ ሀሳቦችን እንጠቁማለን፡፡

የሐዋርያዊ ጉዞ አስፈላጊነት

ሐዋርያ ማለት “ሖረ” ከሚለው የግዕዝ ግስ የወጣ ሲሆን ትርጓሜውም ዞሮ ማስተማርን የሚገልጽ ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ደቀመዛሙርቱን “ሑሩ ወመሐሩ” (እየዞራችሁ አስተምሩ) ብሎ እንደላካቸው ቅዱስ ወንጌል ይነግረናል፡፡ (ማቴ. 28፡18) ስለሆነም ከቀደሙት ሐዋርያት ዘመን ጀምሮ ከሀገር ሀገር እየተዘዋወሩ ወንጌልን ማስተማር ትልቅ ዋጋ ያለው፣ መንፈሳዊ በረከት የሚታፈስበት መንፈሳዊ አገልግሎት ሆኖ ቆይቷል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትና አርድዕት በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ተዘዋውረው አስተምረዋል፡፡ በእነርሱ እግር የተተኩ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያንም እንዲሁ በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች ተዘዋውረው ወንጌልን አስተምረው፣ የቤተክርስቲያንን አገልግሎት እንዲሰፋ አድርገው፣ ብዙዎችን ወደ ጽድቅ መንገድ መልሰዋል፡፡

ተሰዓቱ ቅዱሳን፣ አባ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን፣ ሐዲስ ሐዋርያ የተባሉት አቡነ ተክለሃይማኖትና የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቸው የሆኑ አያሌ ሊቃውንት፣ መነኮሳትና ባህታውያንም እንዲሁ በሀገራች በኢትዮጵያና በአካባቢዋ በየቦታው ዞረው አስተምረዋል፡፡ ይህም ከአገልግሎቶች ሁሉ የከበረ ዋጋ ያለውና ቅዱሳን እንደ ጧፍ ለሌሎች እያበሩ ያለፉበት የጽድቅ መንገድ ነው፡፡ የተወደደ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ሲያስረዳ “መልካሙን የምስራች የሚያወሩ እግሮቻቸው እንዴት ያማሩ ናቸው?” (ሮሜ 10፡15) ብሏል፡፡ ይህ ዞሮ የማስተማር አገልግሎት በእኛም ዘመን በተወሰነ መልኩም ቢሆን እየተፈጸመ ይገኛል፡፡

ሐዋርያዊ ጉዞ ወደ ጠረፋማ አካባቢዎች

በሀገራችን በኢትዮጵያ ጠረፋማ አካባቢዎች ያሉ በርካታ ክርስቲያኖች ትምህርተ ወንጌልን የሚያስተምራቸው፣ ምሥጢራተ ቤተክርስቲያንን የሚፈጽምላቸው አገልጋይ በማጣት ይቸገራሉ፡፡ በተለይም የአማርኛ ቋንቋን ለመግባቢያነት የማይጠቀሙ ምዕመናን ባሉባቸው አካባቢዎች ችግሩ በጣም ከባድ ነው፡፡ በርካታ ምዕመናንም በቋንቋቸው የሚያስተምራቸው፣ የሚያጸናቸው አገልጋይ በማጣት በነጣቂ ተኩላ በተመሰሉ መናፍቃን ሲወሰዱ ይታያል፡፡ በአንጻሩ በታላላቅ ከተሞችና ሌሎች የአብነት ትምህርት የተስፋፋባቸው የሀገራችን አካባቢዎች በአንድ ደብር እጅግ በርካታ አገልጋዮች “ያለ በቂ አገልግሎት” ሲባክኑ ማስተዋል የተለመደ ነው፡፡ ቅዱስ የሆነ የእግዚአብሔር ቃል ነገረ ምጽዋትን በሚያስረዳበት አንቀጽ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ምጽዓት ለጻድቃንም ለኃጥአንም “ተርቤ አብልታችሁኛልን?” (ማቴ. 25፡35 እና 42) የሚል ጥያቄ እንደሚያቀርብላቸው ይነግረናል፡፡ የቤተክርስቲያን መተርጉማን እንደሚያስተምሩት ጌታችን “ተርቤ አብልታችሁኛልን?” በማለት እያንዳንዳችንን (በተለይም የወንጌልን አገልግሎት የማዳረስ ግዴታ ያለባቸው መምህራንን) የሚጠይቀው ለቁመተ ሥጋ የሚሆን ምጽዋት ብቻ ሳይሆን ለነፍስ ድኅነት የሚሆነውን የእግዚአብሔር ቃል ለሚያስፈልጋቸው ሁሉ ማቅረብን ይመለከታል፡፡ ስለሆነም ትምህርተ ሃይማኖትን የሚያስተምሩ ሁሉ ለጠገበው ለማጉረስ ከመሽቀዳደም ለተራበው ቢደርሱ አገልግሎታቸው የጽድቅ ምጽዋት ይሆንላቸዋል፡፡

ሐዋርያዊ ጉዞ ወደ ዝርወት ዓለም

ከቅርብ ዘመን ወዲህ በቁጥር በርከት ያሉ የቤተክርስቲያናችን ምዕመናን በዝርወት (በውጭው) ዓለም መኖራቸው የአጥቢያ አብያተክርስቲያናት ቁጥር እንዲጨምር ምክንያት ሆኗል፡፡ በውጭ ሀገር ያለ የቤተክርስቲያን አገልግሎት በብዙ መልኩ ከሀገር ቤቱ የተለየ ገጽታ አለው፡፡ በቁጥር ቀላል የማይባሉት በውጭ ሀገር የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት በቂ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉ አገልጋዮች የሏቸውም፡፡ ከዚያም ባሻገር ከአንዱ ደብር ወደሌላው በመሄድ ለማገልገል የሚመች ከባቢ የለም፡፡ በተለይም አብያተ ክርስቲያናት ቋንቋና ፖለቲካዊ እይታን ወይም የተወሰኑ ግለሰቦችን ማኅበራዊ ትስስር ታሳቢ ባደረጉ መቧደኖች በተመሠረቱባቸው ቦታዎች አልፎ አልፎ በንግስ በዓላት ከሚታይ የአንድነት አገልግሎት በቀር አንዱ የአንዱን ክፍተት የሚሞሉበት አሠራርም ሆነ ልማድ አይስተዋልም፡፡ ሁሉም በሩን ዘግቶ የየራሱን ‘አገልግሎት’ ለመፈጸም መሯሯጥና እርስ በርስ በቅናትና በፉክክር መንፈስ መተያየት የተለመደ “የአገልግሎት” ገጽታ የሆነባቸው ቦታዎች ጥቂት አይደሉም፡፡

ከዚያም ባሻገር በውጭ ሀገራት ያሉ አጥቢያዎች ከቤተክርስቲያንነት ይልቅ (ባሻገር) ማኅበራዊ መገናኛዎችና የባህልና ፖለቲካ አቋም ማንጸባረቂያ መድረኮች ሲሆኑም ይስተዋላል፡፡ የትክክለኛ አገልግሎት መመዘኛ መስፈርቱም ክርስቲያናዊ መንፈሳዊነትን ከመከተል ይልቅ “የእኛ ወገን ነው ወይስ የእነርሱ ወገን?” የሚል ስሁት መመዘኛ የሆነባቸው ቦታዎች ቀላል የማይባል ቁጥር አላቸው፡፡ ይህ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ ምልከታን ለአገልግሎት መመዘኛነት የሚያይ መለካዊ አስተሳሰብ በኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ስም በሚጠሩ አጥቢያዎች በብዙ አላዋቂዎች ድጋፍና አርቆ ማስተዋል አለመቻል መስፈኑ የቤተክርስቲያንን መንፈሳዊ አንድነት በመሸርሸር የአገልግሎቷን ተደራሽነት በእጅጉ ሲገድበው ይታያል፡፡

በአጭሩ ከአገልጋይ እጥረትም ሆነ በየአጥቢያው ያሉትን አገልጋዮች መዋዋስን የማያበረታታ (የሚያደናቅፍ) አሰራር ከመስፈኑ የተነሳ በብዙ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ያሉ ምዕመናን የሚገባውን ቃለ እግዚአብሔር በተገቢው መልኩ ሲያገኙ አይስተዋልም፡፡ ስለሆነም በውጭ ሀገር የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ያሉባቸውን የአገልግሎት ክፍተቶች ለመሙላትም ሆነ በሌሎች ምክንያቶች መምህራንና ዘማርያንን ከኢትዮጵያ (ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ከልዩ ልዩ የውጭ ሀገራት) ማስመጣት የተለመደ አማራጭ ሆኗል፡፡ ከሀገራቸው ርቀው፣ የቤተክርስቲያንን ጣዕም ናፍቀው ለሚጠባበቁ ሁሉ የእውነተኛ መምህራን በቅርብ መገኘት ለጽድቅ የሚገባውን ፍሬ እንዲያፈሩ ያስችላቸዋልና በአግባቡ የሚፈጸም ተዘዋውሮ የማስተማር አገልግሎት ለሰጭውም ለተቀባዩም ድርብርብ ጸጋን የሚያሰጥ ነው፡፡

ከሐዋርያዊ ጉዞ ጋር ተያይዞ የሚነሱ ችግሮች

ከሚያገለግሉት አገልጋዮች አንጻር ስንመለከተው ተዘዋውሮ የማስተማር አገልግሎት እጅግ ታላቅ የሆነውን የቅዱሳን ሐዋርያትን በረከት የሚያሰጥ፣ የምጽዋትን ግዴታ የሚወጡበት አገልግሎት ነው፡፡ ምጽዋትን የሚሰጥ መንፈሳዊ ዋጋ ለማግኘት እንጂ ከምጽዋቱ የተነሳ ምድራዊ ክብርና ጥቅምን ለማግኘት ሊያደርገው አይገባም፡፡ አገልግሎቱን ከሚፈልጉት አጥቢያ አብያተክርስቲያናት አኳያ ስንመለከተው ደግሞ አዳዲስ ምዕመናንን የሚያፈሩበት፣ የተበተኑትን የሚሰበስቡበት፣ ያሉትን በእምነትም በምግባርም የሚያጸኑበት የቤተክርስቲያን ቀዳሚ ተልዕኮ የሚፈጸምበት አገልግሎት ነው፡፡ ይሁንና ይህን መሰሉ አገልግሎት ወንጌልን መነገጃ፣ አገልግሎትን ኪስ መሙያ ባደረጉ ምንደኛ “አገልጋዮች” እና የጥቅም አጋሮቻቸው የተነሳ መስመሩን እየሳተ ለጽድቅ መዋል የነበረበት አገልግሎት ግልጽ በሆነ መልኩ የንግድና የጥቅም ትስስር መገለጫ እየሆነ ይታያል፡፡ ምንም እንኳ ይህ ችግር በአሁኑ ወቅት ለሚያስተውል ሁሉ የተገለጠ ቢሆንም ብዙዎች የችግሩን መነሻና ማሳያዎች ስለማይረዱ ባለማወቅም ሆነ በምንግዴ ተባባሪነት ምንደኞችንና የጥቅም ተጋሪዎቻቸውን በሚያስደስት፣ የቤተክርስቲያንን አገልግሎት ግን እንደ ሸቀጥ እንዲቆጠር በሚያደርግ አሳፋሪ አሰራር ተሳታፊ ሲሆኑ ይስተዋላል፡፡ ዋጋ የሚገኝበትን አገልግሎት ፍርድ በሚያመጣ፣ ጌታችንን በሚያስቆጣ ድፍረት እንዲለወጥ ከሚያደርጉት ስሁት አሰራሮች መካከል የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡፡

የቅርቡን እያራቁ የሩቁን መናፈቅ

የቤተክርስቲያንን ገንዘብ አውጥቶ መምህራንን ማስመጣት በራሱ መንፈሳዊ ግብ አይደለም፡፡ በየሀገረ ስብከቱ ያሉ አብያተክርስቲያናትም ራቅ ካለ ስፍራ መምህር ለማስመጣት ከመወሰናቸው በፊት በሀገረ ስብከታቸው ውስጥ ያሉትን ሊቃውንትና ሌሎች ተተኪ መምህራን በአግባቡ መጠቀማቸውን መመዘን ይኖርባቸዋል፡፡ በቅርብ ያለውን እያራቁ በሩቅ ያለውን መናፈቅ ጤናማ ያልሆነ አገልግሎት ማሳያ ነው፡፡ በተለይም የሊቃውንት መፍለቂያ በሆኑ የሀገራችን ከተሞች እውነተኛውን ትምህርት የሚያስተምሩትን በአጠገባቸው ያሉ ሊቃውንት ትተው “ከአዲስ አበባ የሚመጡ” የሚባሉ ወንጌልን እንደ ንግድ የያዙ “መምህራንን” በብዙ ወጭ ማምጣት ቤተክርስቲያንን ሁለት ጊዜ መውጋት ነው፡፡

ይህን በምሳሌ ለማስረዳት የሚከተለውን እውነተኛ ታሪክ እናቅርብ፡- በአንዲት የሰሜን ኢትዮጵያ ከተማ በቅዱሳት መጻሕፍት እውቀታቸው የሚታወቁ በርካታ ሊቃውንት ያሉባቸው ጉባኤ ቤቶች አሉ፡፡ ይሁንና ከቤተክርስቲያን ገቢ ማነስና ከአስተዳደሩ ብልሹነት የተነሳ 2,000 ብር በወር የሚከፈላቸው ሊቃውንት በጣት የሚቆጠሩ ናቸው፡፡ ይሁንና በከተማዋ የተሰባሰቡ ወጣቶች ጉባኤ አዘጋጅተው እንደ ዘመኑ ነፋስ ፌስቡክና ዩቲዩብ የሚያውቃቸውን “ከአዲስ አበባ የሚመጣ” መምህር ማምጣት አለብን አሉ፡፡ ያን መምህር ለሁለት ቀናት ጉባኤ ለማስመጣት (በአውሮፕላን ካልሆነ አይመጣም) በወቅቱ ዋጋ ከ3,000 ብር በላይ የአውሮፕላን ቲኬት፣ ከ500 ብር በላይ ለአልጋና ምግብ ወጪ እንዲሁም ለምንደኛው መምህር 15,000 ብር የኪስ ገንዘብ ይከፍሉታል፡፡ ይሄ ሁሉ ወጭ የወጣበት መምህር መጥቶ የረባ ትምህርት ሳያስተምር ከብዙ ቀልድና ጨዋታ ጋር የተሰበሰበውን ወጣት በስሜት አስጨብጭቦ፣ ለራሱ ለማስታወቂያ የሚሆነውን ቪዲዮ ይዞ ይመለሳል፡፡ የሚያሳዝነው እነዚሁ ወጣቶች ጉባኤውን ለማዘጋጀት መግፍኤ ከሆኗቸው ምክንያች አንዱ “የቤተክርስቲያን ሊቃውንት መጥፋትና መሰደድ አሳስቧቸው” ነው፡፡ ነገር ግን ለሚያስተውል ሰው እነርሱ ካደረጉት ተግባር በላይ ቤተክርስቲያንን የሚጎዳ፣ ሊቃውንቷን የሚያሳንስ ተግባር የለም፡፡

በተመሳሳይ መልኩ በብዙ የውጭ ሀገራት በሚገኙ ሀገረ ስብከቶችና አብያተ ክርስቲያናት ያለ ምንም ወጪ የቤተክርስቲያንን ትምህርት የሚያስተምሩ መምህራን እያሉ በእውቀት ከእነርሱ በእጅጉ ያነሱ መምህራንን ብዙ ወጭ በማውጣት ከሌላ ቦታ ያስመጣሉ፡፡ በአንዳንድ ቦታዎች እንደታየውም ቀደም ባሉ ዓመታት ተጋባዥ መምህራን እየሆኑ በሚሄዱባቸው ሀገራት በልዩ ልዩ መልኩ የመኖሪያ ፈቃድ አግኝተው መኖር ሲጀምሩ “ለንግድ ስለማይመቹ” አብያተ ክርስቲያናቱ እነርሱን በመተው ሌሎችን ማስመጣት ይቀጥላሉ፡፡ ይህ የቅርቡን እየናቁ የሩቁን የመናፈቅ አባዜ የሚያሳየን ነገር ቢኖር በእነዚህ ዘንድ “መምህራንና ዘማርያን ማስመጣት” የሚባለው ለምዕመናን መንፈሳዊ ሕይወት በመጨነቅ የሚደረግ ሳይሆን መንፈሳዊ ላልሆነ ዓላማ ወይም መንፈሳዊ ነው ተብሎ የሚታሰብን ዓላማ በገንዘብ ለመደገፍ የሚደረግ የገቢ ማስገኛ ስልት (fund raising strategy) ነው፡፡

አገልግሎትን ከገንዘብ ጋር መቀላቀል

መንፈሳዊ አገልግሎት ንግድ መሆን የለበትም፡፡ መምህራንን የሚያስመጡ አጥቢያዎችም አገልግሎቱን ገንዘብ ከመሰብሰብ ጋር ሊያገናኙት አይገባም፡፡ ምንም እንኳ የቤተክርስቲያን አገልግሎት ገንዘብ እንደሚያስፈልገው ቢታወቅም ገንዘብን መሰብሰብ በግልጽ በሚደረግ ጥረት እንጂ በማስመሰል በሚደረግ፣ መንፈሳዊ ዋጋን በሚያሳጣ መልኩ መፈጸም የለበትም፡፡ በብዙ ቦታዎች መምህራንን የማስመጣት ነገር “ከገቢ ማስገኛ” መንገዶች አንዱ (ቀዳሚው) ተደርጎ ይታሰባል፤ በተግባርም ይታያል፡፡ ለማስተማር የሚመጡ ሰዎች የሚመረጡትም ያላቸውን ታዋቂነት በመጠቀም ወይም በደላላ አሰራር ገንዘብ መሰብሰብ የሚችሉ መሆናቸውን ታሳቢ በማድረግ ነው፡፡ በተለያየ ቦታ እየተዘዋወሩ ከሚያስተምሩ መምህራንም ቀላል የማይባል ቁጥር ያላቸው ምንደኞች አሉ፡፡ ለእነዚህ ሰዎች “አገልግሎቱ” ኑሯቸውን የሚገፉበት የስምሪት መድረክ እንጂ ለመንፈሳዊ ዋጋ የሚደረግ ሱታፌ አይደለም፡፡

ስለሆነም የየራሳቸውን ደላሎች በየቦታው በማሰማራት፣ “ለአገልግሎት” በሚሄዱባቸው ቦታዎችም በድለላቸውና በማጭበርበራቸው ከምዕመናን ከሚሰበስቡት ገንዘብ በፐርሰንት እየተደራደሩ፣ ካልሆነም ኢ-መደበኛ በሆነ መልኩ ተጽዕኖ እየፈጠሩ የግል ጥቅማቸውን ለማካበት ይሰራሉ፡፡ ገንዘብ ማግኘትን ቀጥተኛ ዓላማ ያደረጉ መንፈሳዊ ስራዎች ፈር ለመሳት ጊዜ አይወስድባቸውም፡፡ ይህ አገልግሎትን ከገንዘብ ጋር የመቀላቀል አሠራርም ከቀጥተኛ መንፈሳዊ ኪሳራነቱ ባሻገር ሐዋርያዊ ሊሆን የሚገባውን ዞሮ የማስተማር አገልግሎት በብዙ መልኩ ያጎድፈዋል፡፡ አገልግሎት ከገንዘብ ጋር ሲቀላቀል የሚያገለግሉት ሰዎችም አገልግሎታቸው የገቢ ምንጫቸው እንጂ የእምነታቸው ፍሬ አይሆንም፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ነገር ግን ያላመኑበትን እንዴት ይጠሩታል?” (ሮሜ. 10፡14) በማለት የጠየቀው የእግዚአብሔርን ስምና ቅዱስ ቃሉን እንደ አማኝ ሳይሆን እንደቅጥረኛ ባለሙያ የሚናገሩትን ይመለከታል፡፡

ከአብያተክርስቲያናት አስተዳደር ጋር በመደበኛም ሆነ ኢ-መደበኛ መልኩ የሚደረጉ “የገንዘብ ድርድሮች” አገልግሎቱን ቁሳዊ ሲያደርጉት ይታያል፡፡ አንዳንዶቹም በድለላቸውና ምዕመናንን በስሜት በማነሳሳት የሚሰበስቡትን መንፈሳዊ ዋጋ የሌለው የገንዘብ መጠን እየጠቀሱ “ካስገባነው ገቢ አንፃር በኮሚሽን መልኩ ይከፈለን” በማለት እስከመከራከር መድረሳቸው አገልግሎቱ ምን ያክል መስመር እየሳተ እንደመጣ በግልጽ ያሳያል፡፡ ከዚያም ባሻገር ለአገልግሎት ተብለው የሚመጡ መምህራን በልዩ ልዩ መንገድ ሌሎች ንግዶችን ሲያካሂዱ ይታያል፡፡ ለምሳሌ ያክል አንዳንዶቹ በውጭ ሀገራት ለአገልግሎት በሚመጡበት ጊዜ የመዝሙርም ሆነ የስብከት ካሴታቸውን የቅጅ መብት ከሰጡት አሳታሚ በመደበቅ (በመስረቅ) ወደ ሲዲዎች እንዲገለበጥ ካደረጉ በኋላ የኦሪጂናሉን ስቲከር በመለጠፍ በኦሪጅናል ዋጋ ምዕመናንን “ለበረከት ውሰዱ” በማለት ይነግዳሉ፡፡ ሌሎችም ከምዕመናን በልዩ ልዩ መንገድ በግል ገንዘብ በመቀበል አገልግሎታቸውን ዋጋ ያሳጡታል፡፡ በአንድ ወቅት አንድ መምህር በአውደ ምህረት “ኢትዮጵያ ሄጄ የማገለግልበት መኪና ብትገዙልኝ ምን አለበት?…ለአገልግሎት እስከሆነ ድረስ አውሮፕላንም እንግዛ ብንል ልታግዙን ይገባል፡፡” በማለት የተናገረውን እንደማሳያ መውሰድ እንችላለን፡፡ እንደዚህ ዓይነት “መምህራን” ወንጌልን መነገጃ የሚያደርጉ፣ ምዕመናንም የእነርሱን የማይጠግብ ኪስ ለመሙላት የተፈጠሩ የሚመስላቸው ስለሆኑ እንጂ እውነት ስለ አገልግሎት ብለው አይደለም፡፡

እንዲህ ዓይነቱ ምንደኛ ጌታችን በወንጌል “ያለ ዋጋ የተቀበላችሁትን ያለ ዋጋ ስጡ፡፡ በመቀነታችሁም ወርቅ ወይም ብር ወይም መሐለቅ አትያዙ፡፡ ለመንገድም ስልቻ ወይም ሁለት ልብስ ወይም ጫማ፣ ወይም በትር አትያዙ፤ ለሠራተኛ ዋጋው ይገባዋልና፡፡” (ማቴ. 10፡8-10) ያለውን የሚተረጉምበትን፣ የሚያስተምርበትን ያልተበረዘ ቅዱስ መንፈስ ከወዴት ያገኛል? ይህን ጥቅስ አንስተው “ሲያስተምሩ” (ንግዳቸውን በአመክንዮ ሲደግፉ) እንኳን የመጀመሪያዎቹን ንባባት ትተው “ለሠራተኛ ዋጋው ይገባዋል” የሚለውን እየደጋገሙ የጌታን ቃል ለነውራቸው መሸፈኛ ያደርጉታል፡፡ ጌታችን እንዳለ “ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው አገልጋይ የለም፡፡” (ማቴ. 6፡24) የሚያሳዝነው በምንደኞቹ ምክንያት ደገኛው አገልግሎት መናቁና መፈረጁ ነው፡፡ በአንጻሩ በዘመናችን በእውነት ለመንፈሳዊ ዓላማ የግል ጥቅማቸውን እየተው፣ ራሳቸውን እየጎዱ የሐዋርያትን ፈለግ ተከትለው በየጠረፉ፣ የተረሱ ምዕመናን ባሉበት ሁሉ የሚያገለግሉ መምህራን ከአጭበርባሪዎቹ የተነሳ “ከኑግ ጋር እንደተገኘ ሰሊጥ” ለትችትና ነቀፋ መጋለጣቸው ያሳዝናል፡፡ ይሁንና መንፈሳዊ አገልጋይ በስህተትም ሆነ በእውቀት የሚፈጠሩ መሰረት አልባ ትችቶች ለአገልግሎቱ ማትጊያ መንፈሳዊ ዋጋዎች ይሆኑታል እንጂ ማደናቀፊያ አይደሉም፡፡

“መምህራንን ተጠቅመን ‘ገቢ ብናስገኝ’ ምን አለበት?” 

እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በብዙዎች ዘንድ አገልግሎትን ለገንዘብ ማስገኛነት የማመቻቸት ክፉ ልምምድ ቢያንስ በመርህ ደረጃ ተቀባይነት አልነበረውም፡፡ አገልግሎቱን ለንግድ የሚያውሉት ሰዎችም ሌሎች ማስመሰያዎችን እየፈጠሩ ይናገራሉ እንጂ በግልጽ ገንዘብ የማስገኘት ዓላማን የሚያነብር (legitimize የሚያደርግ) አመክንዮ ማቅረብ አልተለመደም ነበር፡፡ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ግን ነውሩ ሥር እየሰደደ መንፈሳዊነት የጎደለውን አመክንዮ ያለማፈር በአውደ ምሕረት የሚያብራሩ ምንደኞች በዝተዋል፡፡

ለመሆኑ መምህራንና ዘማርያንን ተጠቅሞ ገንዘብ የሚገኝበት መንገድ ለምዕመናን መንፈሳዊ ህይወት ያለው አንድምታስ ምንድን ነው? ምዕመናን ለቤተክርስቲያን አስተዋጽኦ ማድረግ ግዴታችን ቢሆንም አሥራታችንን የምናወጣው ሕገ እግዚአብሔርን፣ ሥርዓተ ቤተክርስቲያንን ጠብቀን መሆን አለበት፡፡ ሰው በስጦታው ዋጋ የሚያገኝበት አምኖበት ሲሰጥ እንጂ በስሜት ተገፋፍቶ፣ ሰው ይይልኝ ብሎ፣ ‘ታዋቂ’ በሚባሉ በሰባኪነት ስም ድለላን ሙያ አድርገው በያዙ ሰዎች የሽንገላ ምርቃትን ለመቀበል መሆን የለበትም፡፡ የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ይላል “ለሰዎች ትታዩ ዘንድ ምጽዋታችሁን በሰዎች ፊት እንዳታደርጉ ተጠንቀቁ፤ ያለዚያ በሰማያት ባለው በአባታችሁ ዘንድ ዋጋ የላችሁም፡፡ ምጽዋታችሁንም በምታደርጉበት ጊዜ ግብዞች በሰዎች ዘንድ ሊመሰገኑ በምኩራብና በአውራ ጎዳና እንደሚያደርጉት በፊታችሁ መለከት አታስነፉ፤ እውነት እላችኋለሁ፤ ዋጋቸውን ተቀብለዋል፡፡” (ማቴ. 6፡1-2)

በቁማር የሚገኝ ዕጣ ለማግኘት ሲል ገንዘብ የሚሰጥ፣ ስሙ ስለተጠራና ስለተጨበጨበለት ገንዘብ የሚሰጥ፣ የምንደኛ ደላሎችን የአደባባይ ምርቃት ፈልጎ ገንዘብ የሚሰጥ በእግዚአብሔር ቃል መሠረት በምድር ዋጋውን ስለተቀበለ ሰማያዊ በረከትን አያገኝም፡፡ ይሁንና ምዕመናን ይህን የእግዚአብሔር ቃል በሚገባ እንዳይረዱ ተግተው የሚሠሩ ብዙ ናቸው፡፡ ከእነዚህም የተነሳ ብዙ ሰዎች ለቤተክርስቲያን ገንዘብ መስጠት የሚገባው እልልታና ጭብጨባ ባለበት ሰዓት እንደሆነ የሚያስቡ ይመስላል፡፡ ጌታችን በወንጌል “እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን መንግስተ ሰማያትን በሰው ፊት ስለምትዘጉ ወዮላችሁ! እናንተም አትገቡም፤ የሚገቡትንም ከመግባት ትከለክሉአቸዋላችሁ፡፡” (ማቴ. 23፡14) ያላቸው እነዚህን ነው፡፡ የቤተክርስቲያንን ገቢ ከማሳደግ አኳያ የመምህራነ ወንጌል ድርሻ ድለላና ማጭበርበር ሳይሆን ምዕመናንን በሚገባ ማስተማርና ዋጋ የሚያገኙበትን የጽድቅ ስጦታ እንዲሰጡ መምከር እንጂ የሀሰትን አሰራር ማባዛትና ራሳቸውን እንደ ታዋቂ ሰው (celebrity) ለሽያጭ በማቅረብ የምንደኞችን ካዝና መሙላት፣ የምዕመናንንም ስጦታ መንፈሳዊ ዋጋ ማሳጣት አይደለም፡፡

ሰባክያን የሚመረጡበት መስፈርት ብልሹነት

በዘመናችን ለሐዋርያዊ ጉዞ ሰባክያን የሚመረጡበት መስፈርት ብዙ ችግሮች ያሉበት ነው፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው፣ በእውቀታቸውና በማስተማር ብቃታቸው ከሚመረጡት ይልቅ በፌስቡክና ዩቲዩብ ባላቸው ታዋቂነት፣ ገንዘብ ለመሰብሰብ ባላቸው የድለላ ችሎታ፣ የሚገባቸውንም የማይገባቸውንም ቀሚስና ቆብ ለማሳመር በሚያደርጉት መኩነስነስ፣ በዘርና ፖለቲካዊ ቡድንተኝነት እንዲሁም በመሳሰሉት ሥጋዊ መመዘኛዎች የሚመረጡት ይበዛሉ፡፡ ሌሎችም አገልግሎቱ ከሚሰጥበት ቦታ ካሉ ሰዎች ጋር (በተለይም ከካህናትና ሰበካ ጉባኤ አስተዳደር አካላት ጋር) ባላቸው ግላዊ ግንኙነት ይመረጣሉ፡፡ ለዚህም ብለው በየአጥቢያ አብያተክርስቲያናት “ተጽዕኖ ፈጣሪ” ናቸው ብለው የሚያስቧቸውን ሰዎች በአውደ ምህረት የሚሸነግሉ፣ በልዩ ልዩ መንገድ የተጋነነ ግለሰባዊ የስብዕና ግንባታ (personality cult) ለመፍጠር የሚሽቀዳደሙ አሉ፡፡

አብያተክርስቲያናት ከመንፈሳዊ መስፈርት በወጣ መልኩ ሰባክያንን መምረጣቸው በጎ ምግባር የነበራቸው ሰባክያን ሳይቀሩ “የአገልግሎቱን እድል” ለማግኘት ሲሉ በድለላ፣ በማስመሰል አለባበስ እንዲሁም በመሳሰሉት ዋነኞቹን ምንደኞች ለመምሰል ሲሽቀዳደሙ ማየት ልብን ይሰብራል፡፡ አንዳንድ ሰባክያን ለአገልግሎት ከመጡ ተመልሰው የሚጠሩበትን መንገድ ለማመቻቸት ብዙ መንፈሳዊ ያልሆኑ አሠራሮች ውስጥ ይገባሉ፡፡ ተመልሰው መጠራት የማይችሉ ከሆነም በግልጽም በስውርም የራሳቸውን ጓደኞች ወይም የሥጋ ዘመዶቻቸውን በቀጣይ እንዲጠሩ መደላድል ይፈጥራሉ፡፡ ይህም አገልግሎቱን ፍፁም ቁሳዊና ለብልሹ አሠራር የተመቸ ያደርገዋል፡፡ ይህ ችግር በብዛት የሚስተዋለው ጥቅም በሚበዛበት የታላላቅ ከተሞች ወይም የውጭ ሀገራት አገልግሎት ላይ ነው፡፡ መከራ ባለበት አገልግሎትማ ማን ይሽቀዳደማል!?

ሰባክያን ራሳቸውን በሁሉ ጉዳይ ሊቅ አድርገው የማቅረብ ችግር

ሰባክያን ለሚመረጡበት ስሁት መንገድ ለማገዝ ሰባክያኑን ሁሉን የሚያውቁ አስመስሎ በማጋነን ማስታወቂያ መስራት እየተለመደ ነው፡፡ ትሁት አገልጋይ እንኳ ቢሆን ራሳቸውን እንደ “አስመጭና ላኪ” የሚቆጥሩት አካላት ለንግዳቸው ስለሚፈልጉት አቀራረቡን ለማስተካከል ይከብዳል፡፡ አንዳንዶቹ ሰባክያንም ትዕቢቱ ስለሚጋባባቸው ራሳቸውን በሁሉ ጉዳይ ሊቅ አድርገው በማቅረብ በማያውቁት እየተለኩ ይወድቃሉ፡፡ አንድ መምህር በአውደ ምህረት ስለቆመ ብቻ ራሱን የባህልም፣ የኮሜዲም፣ የፖለቲካም፣ የስነ ልቦናም፣ የጤናም፣ የመሳሰለውም ባለሙያ አስመስሎ ከመንፈሳዊ ትምህርት ጋር በማይገናኙ ጉዳዮች ሳይቀር ትዝብት ላይ የሚጥሉ ረብ የለሽ አስተያየቶችን ሲሰጥ ያሳቅቃል፡፡ ከሚያስተምሩት ምዕመን መካከል እነርሱ ባለማወቅ የሚናገሩበትን ሙያ የሚያውቁ ሰዎች እንዳሉ እንኳ አያስተውሉም፡፡ በዚህም ራሳቸውን ያስገምታሉ፣ ቤተክርስቲያንንም ያሰድባሉ፡፡ ከዓለማዊ ጉዳዮች ባሻገር በመንፈሳዊ ትምህርትም አንድ መምህር ሁሉን ሊያውቅ አይችልም፡፡ የማያውቁትን ሲጠየቁ በጥበብ ከማለፍ ይልቅ በሞኝነትና በድፍረት ያልተረዱትን የሚናገሩ ሲበዙ እናስተውላለን፡፡ የዚህም ምክንያቱ ራስን በሁሉ ጉዳይ ሊቅ አድርጎ የማቅረብ ችግር ነው፡፡

በአገልግሎት ሰበብ ግላዊ ወይም ቡድናዊ ዓላማን ማስፈጸም

የቤተክርስቲያን አገልግሎት በጥቅመኞች፣ እንዲሁም በዘርና በፖለቲካ እይታ ቡድናዊ ስሜትን ፈጥረው ቤተክርስቲያንን በሚያውኩ ሰዎች እጅ በሚወድቅበት ጊዜ ከሚታዩ ችግሮች አንዱ መንፈሳዊውን አገልግሎት የሚወዱትን ለማመስገን፣ የሚጠሉትን ለመርገም ማዋል ነው፡፡ ይህ ችግር በውጭ ሀገራት በሚገኙ አጥቢያዎች ይበልጥ ይስተዋላል፡፡ ለማስተማር የሚመጡትን መምህራን በጥቅም በመደለል ወይም የተሳሳተና የተዛባ መረጃ በመስጠት የተወሰኑ ሰዎችን ሀሳብ ብቻ እንዲይዙ ያደርጓቸዋል፡፡ ለዚህም እንዲረዳቸው መምህራኑ በትርፍ ጊዜያቸው ከማን ጋር መገናኘት እንዳለባቸው ወይም እንደሌለባቸውም ጭምር የሚከታተሏቸው ሰዎች ይመድባሉ፡፡ በውለታና በጥቅማጥቅም በመደለል፣ ወይም የተጣመመ ‘መረጃ’ (deliberately twisted information) በመስጠት የሚፈልጉትን ሀሳብ ይጭኑባቸዋል፡፡ ከዚህም የተነሳ የስብከቱና የትምህርቱ አቅጣጫ ሰዎችን ለመንግስተ ሰማያት ለማብቃት ሳይሆን እንዲወደሱ የሚፈልጓቸውን በውዳሴ ከንቱ በመሸንገል፣ እንዲሰደቡ የሚፈልጓቸውን ደግሞ ያለስማቸው ስም በመስጠት እንዲሁም በግልጽ በመሳደብ እንዲበላሽ ያደርጋሉ፡፡ ቡድናዊ ስሜት ያላቸው ሰዎች መምህራንን በማስመጣትና በመደለል ወይም በማታለል የግለሰቦች ወይም አምባገነናዊ አስተዳደሮች ማኅበራዊ ቅቡልነት መገንቢያ አድርገው ይወስዷቸዋል፡፡ በዝና የሚታወቁ መምህራንን ከሚያስቀድሙባቸው ምክንያቶች አንዱም በተበላሸ አሰራራቸው  የሚተቿቸውን ምዕመናን “አንተ/አንቺ እገሌ ከተባለው ታዋቂ መምህር ትበልጣለህ/ትበልጫለሽ? እነርሱኮ ይደግፉናል፡፡” የሚል ስንኩል አመክንዮ ለመፍጠር ነው፡፡

ምንደኛ የሆኑት መምህራንም “አስመጪና ላኪዎቻቸውን” የሚያስደስት የመሰላቸውን የፖለቲካና የቡድንተኝነት አስተሳሰብ በሥጋዊ ስሜት ተመርተው እየተናገሩ በረከትን ሊያወርሱ ተጠርተው መርገምን ይጭናሉ፡፡ (መዝ. 83፡6) የጥቅም ትስስራቸው ወደሚያደላበት ቡድን በመወገን፣ ሌሎቹም በመረጃ እጥረት ወይም መዛባት ከቤተክርስቲያን መሠረታዊ ተልእኮ ወጥተው የግለሰቦችና ቡድኖች መንፈሳዊ ያልሆነ ተልዕኮ ፈጻሚ ሲሆኑ ይታያሉ፡፡ በንግድ ፉክክር ውስጥ ሳይቀር እየገቡ ለአጉራሾቻቸው የንግድ ተቋማት በአውደ ምህረት ማስታወቂያ ይሰራሉ፡፡ አንድ አስተማሪ ይህን መሰሉን ተራ ነገር ሲናገር በሀሳቡ ሊስማሙ የሚችሉት በግላዊ መሳሳብ ከእርሱና ከመሰሎቹ ጋር የሚግባቡ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡ ለሌሎቹ ግን አውደ ምህረቱ የማንን ሀሳብ ለማንጸባረቅ እንደዋለ ለመረዳት አይከብዳቸውም፡፡ ለእነዚህ ሰዎች “ከትምህርቱ” በኋላ “ያስተማረን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የተመሰገነ ይሁን” ብለው የሚያሳርጉ ሰዎች መንፈስ ቅዱስን ሳይታወቃቸው ይዘልፉታል፡፡ ምዕመናንም ቃለ እግዚአብሔርን በንጹህ ህሊና ከመስማት ይልቅ በሚያውቁትና በሚረዱት ልክ እየመዘኑ ለጽድቅ በተቀመጡበት አደባባይ ለፍርድ ይቆማሉ፡፡ አባቶቻችን በመልክዓ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ለወንጌል አገልግሎት መፋጠናቸውን አስበው ሲያመሰግኑ “ጳውሎስ ወጴጥሮስ ለክርስቶስ ላእካነ ቃሉ/ጳውሎስና ጴጥሮስ ሆይ እናንተ የክርስቶስ የቃሉ መልእክተኞች ናችሁ” ማለታቸው ለሰባክያነ ወንጌል መርህ ሊሆናቸው በተገባ ነበር፡፡ ቅዱስ ቃሉን ለማስተማር የሚቆሙ ሁሉ የክርስቶስ አምሳል፣ የመንፈስ ቅዱስ መልእክተኞች ሆነው ከመንፈስቅዱስ የተገኘውን (የተማሩትን፣ ያመኑትን) ሊያስተምሩ ይገባል እንጂ ነገር አመላላሽ ሆነው ቅዱስ የሆነውን የእግዚአብሔርን ቃል የሚወዷቸውን ለመጥቀም፣ የሚጠሏቸውን ለመጉዳት ሊሸቅጡበት አይገባም፡፡ ልበ አምላክ ዳዊት “ቃለ እግዚአብሔር ቃል ንጹሕ/የእግዚአብሔር ቃል ንጹሕ ቃል ነው” (መዝ. 11፡6) ያለው በመንፈስ ቅዱስ መሪነት የሚነገርን እንጂ በዚህ መልኩ የሚሸቀጠውን አይደለምና፡፡

ውሸት፣ ከንቱ ውዳሴና ሽንገላ

የገንዘብ ጥቅምና የግላዊ ታዋቂነት ፍለጋ ተዘዋውሮ የማስተማርን አገልግሎት መንፈሳዊነት እያጠፉት እንደሆነ ከሚያሳዩ ጉዳዮች አንዱ በዚህ መሰል ትስስር የሚመጡ መምህራን የሚገኙባቸው አውደምህረቶች ላይ የሚታየው የውሸት፣ ከንቱ ውዳሴና ሽንገላ ብዛት ነው፡፡ ምንደኛ አገልጋዮች በደላሎቻቸውና በግል በሚቆጣጠሯቸው በርካታ ተከታዮች ባሏቸው የማኅበራዊ ትስስር ገጾች አማካኝነት የሌላቸውን ክብር ለራሳቸው በመስጠት በውሸት፣ በከንቱ ውዳሴና በሽንገላ መንፈሳዊውን አውደ ምህረት የቲያትር መድረክ ያስመስሉታል፡፡ መምህራኑ ለአገልግሎት የሚመረጡበት መስፈርት “ታዋቂ” ናቸው በሚል ስለሆነ “የታዋቂነትን” ካባ እንደደረቡ ለመቆየት ውሸትና ከንቱ ውዳሴን ያበዛሉ፡፡ ፎቶአቸውን በፎቶሾፕ በማሳመር ከቢራ ማስታወቂያ የማይተናነስ ግነት በበዛበት መልኩ የጉባኤ ፖስተሮችን ማስተዋወቅ፣ ያላደረጉትን እንዳደረጉ አስመስለው በመናገር ለራሳቸው የሀሰት ክብርን መስጠት፣ የአብያተክርስቲያናትን አገልጋዮች ከልክ ባለፈ ውዳሴ ከንቱ በመካብ በአጸፋው ለመከበር የመፈለግ አዝማሚያዎች በየአውደምህረቱ እየተለመዱ መጥተዋል፡፡ ይህም በመልካም እርሻችን ላይ እንደበቀለ ተዛማች አረም ነው፡፡

ከባድ የገንዘብ ጫና

በዘመናችን ብዙ የቤተክርስቲያናችን መደበኛ አገልጋዮች እጅግ በጣም አነስተኛ በሆነ ወርኃዊ ደሞዝ እያገለገሉ ቢሆንም የቤተክርስቲያን አገልግሎት ለጥቂቶች ከታላላቅ ደሞዝ ከፋይ መሥሪያ ቤቶች የተሻሉ የገቢ ማግኛ መንገዶች ሆነዋል፡፡ በሀገራችን በኢትዮጵያ አንድ የመንግስትም ሆነ የግል መስሪያ ቤት ሠራተኛ ለመስክ ሥራ ከቦታ ቦታ መንቀሳቀስ ቢያስፈልገው የሚጠቀምበት መጓጓዣና የሚሰጠው አበል እንደ ስልጣን እርከኑ ቢለያይም በአውሮፕላን የመሳፈሪያ ቲኬትና የተጋነነ አበል የሚያገኙት እጅግ ጥቂቶች ናቸው፡፡ በአንጻሩ በመደበኛ በጀት ለሚያገለግሉ አገልጋዮቿ ከመንግስትና የግል ቀጣሪዎች የማይነጻጸር እጅግ ዝቅተኛ ደመወዝ በምትከፍል ቤተክርስቲያን ውስጥ እየተዘዋወሩ ለሚያስተምሩ መምህራን የሚወጣው የአውሮፕላን ቲኬትና የአበል ወጭ በምዕመናን ላይ ከባድ የገንዘብ ጫና የሚፈጥር ነው፡፡ ምንደኛ የሆኑት መምህራን ለመደበኛ ካህናቷ በወር ከምትከፍለው ሃያ እጥፍ በላይ ለአንድና ለሁለት ቀን ጉባኤ ሲጠይቁ ማየት ያልተለመደ አይደለም፡፡ አርቀው ማስተዋል የማይችሉ ሰዎች የክፍያ ጉዳይ አስተያየት ሲሰጥበት “ቢከፈላቸው ምን አለበት?” ይላሉ፡፡ ችግሩ ያለው የተሻለ ገንዘብ መክፈል አለመክፈሉ ላይ ሳይሆን ያለ ተገማች አሠራር ያልተመጣጠነ ክፍያ መጠየቅ አገልግሎቱን በቀጥታም ሆነ በሂደት መስመር የሚያስት በመሆኑ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ገንዘብን መውደድ የክፋት ሁሉ ስር ነው” (1ኛ ጢሞ. 6፡10) ያለውም ይህን መሰሉ መርህ አልባ የገንዘብ ንጥቂያ ሃይማኖትን በመካድ የመጠናቀቅ እድሉ ሰፊ ስለሆነ ነው፡፡ ይህንንም ለመረዳት ሩቅ ሳንሄድ በቅርቡ ከቤተክርስቲያን በይፋ ተለይተው ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ቤተክርስቲያንን ማሳደድን ሥራዬ ብለው የያዙት ወገኖቻችን የሄዱበትን የቀድሞ መንገድ ማስታወስ ይበቃል፡፡

በውጭ ሀገር ባሉ በርካታ አብያተክርስቲያናት አንድን መምህር ለማምጣት ለትራንስፖርትና ለመቆያ ያሉ ወጪዎችን ሳይጨምር ለአንድ ወር አገልግሎት በአማካይ ከሦስት እስከ ሰባት ሺህ የአሜሪካ ዶላር “የኪስ ገንዘብ” ይሰጣቸዋል፡፡ ይህ ክፍያ በዓለማችን ታላላቅ የሚባሉት ድርጅቶች ከሚከፍሉት የሚበልጥ ከመሆኑም ባሻገር በሀገራችን የገጠር አካባቢዎች አንድ ቤተክርስቲያን ማሠራት የሚችል ነው፡፡ የአውሮፕላን ቲኬት፣ የምግብና የመኝታ አገልግሎት ተሸፍኖለት ለአንድ ወር ይህን የሚያክል ክፍያ የሚገኝበት ሥራ እጅግ በጣም ጥቂት ነው፡፡ ይህ ሁሉ ጫና የሚወድቀው በዓለማችን ባሉ ታላላቅ ከተሞች ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ባለውና በብዛት የጉልበት ሥራ በመሥራት በሚተዳደረው ኢትዮጵያዊ ማኅበረሰብ መሆኑ ደግሞ ምጸቱን ያጎላዋል፡፡ ይሁንና “መምህራን ማስመጣቱን” በዋናነት የሚመሩት አካላት ጫናውን የሚያዩበት መንገድ “ያዋጣል ወይስ አያዋጣም?” በሚል የንግድ ሚዛን እንጂ “በእናንተ በአንዱ ስንኳ እንዳንከብድበት በቀንና በሌሊት እየሠራን የእግዚአብሔርን ወንጌል ሰበክንላችሁ” (1ኛ ተሰ. 2፡9) በሚለው በቃልም በሕይወትም በተገለጠው የቅዱሳን አባቶቻችን  ምክር ስላልሆነ ችግሩ አያሳስባቸውም፡፡

መደምደሚያ

ወንጌልን ተዘዋውሮ የማስተማር አገልግሎት የቤተክርስቲያን መሰረታዊ ተልዕኮ ነው፡፡ ከቅዱሳን ሐዋርያት ጀምሮ በየዘመናቱ የተነሱ የቤተክርስቲያን ሊቃውንት፣ መናኝ ባሕታውያንና እንደየጸጋቸው በአግባቡ የተማሩትን ትምህርተ ወንጌልን ለሌሎች የሚያዳርሱ ምዕመናንና ምዕመናት እልፍ ዋጋ ያገኙበት፣ የሚያገኙበት የጽድቅ አገልግሎት ነው፡፡ ይህ አገልግሎት ጌታችን በዳግም ምጽዓት በክብር ለፍርድ ሲገለጥ እያንዳንዳችንን “ተርቤ አብልታችሁኛልን?ተጠምቼ አጠጥታችሁኛልን?” በማለት የሚጠይቀን ደገኛ ምጽዋት ነው፡፡ ዛሬም በዘመናችን ቃለ ወንጌልን ለተራቡ፣ በየጠረፉ፣ አብያተ ክርስቲያናት ባሉበት ሁሉ ያለ ዋጋ እንደቅዱሳን ሐዋርያት እየደከሙ ቤተክርስቲያንን በምዕመናን ከዋክብትነት የሚያደምቁ፣ ራሳቸውም ከአላውያንና ከመናፍቃን በሚመጣ ማለቂያ በሌለው መከራ እየተፈተኑ የሚያበሩ የጽድቅ ፀሐዮች አሉ፡፡

በአንጻሩ ደግሞ የወንጌል አገልግሎትን እንደ አማኝ፣ እንደ አገልጋይ ሳይሆን እንደ አርቲስት፣ እንደ አነቃቂ ንግግር አቅራቢ ለመነገጃነት በማቅረብ ለራሳቸው የሥጋ ድልብን የሚያከማቹ፣ ምዕመናንንም ለስህተት አሠራራቸው ባርያ በማድረግ የጽድቁን አገልግሎት መሸቀጫ የሚያደርጉ አሉ፡፡ እነዚህ ራሳቸውን ‘ታዋቂ’ አድርገው የሚቆጥሩ ወይም ‘ታዋቂ’ ለመሆን የሚጥሩ ምንደኞች ‘አገልግሎታቸው’ በመታየት ላይ የተመሰረተ ስለሆነ ብዙ ሰው የሚያውቃቸው በሞኞች ዘንድም “የቤተክርስቲያን የቁርጥ ቀን ልጆች” የሚባሉ፣ ራሳቸውም በሐሰት የማኅበራዊ ሚዲያ አካውንቶች በመጠቀም ለራሳቸው ከንቱ ውዳሴን የሚያዘንቡ፣ ወንጌልን በገንዘብ የሚለውጡ፣ ምርቃትና ጸሎትን የሚሸጡ ሲሞናውያን ናቸው፡፡ የቤተክርስቲያንን አገልግሎት በሁሉም የዓለም ዳርቻ የማዳረስ ግዴታ ያለብን የቤተክርስቲያን ልዩ ልዩ የአስተዳደር አካላት፣ ካህናትና ምዕመናን የጽድቁ አገልግሎት ለመንፈሳዊ ዋጋ እንጂ ለሥጋዊ ብዕልና ታዋቂነት እንዳይውል የመጠበቅ ግዴታ አለብን፡፡ ተዘዋውሮ የማስተማር አገልግሎታችን የጽድቅ እንጀራን ለተራቡ ሁሉ የሚሰጥ ምጽዋት አድርገን የምናቀርብበት ጥበብ መንፈሳዊ እንዲሆንልን የሐዋርያት አምላክ፣ የሠራዊተ መላዕክት ጌታ፣ አምላካችን እግዚአብሔር ይርዳን፡፡

1 thought on “ሰባኪ ማስመጣት: የዘመናችን ሐዋርያዊ ጉዞና ዓለማዊ ጓዙ

  1. Pingback: የሐዋርያዊ ጉዞ መርሆች: ሰባኪ በመምጣቱ ምን ለውጥ መጣ? – አስተምህሮ

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s