እውነተኛይቱ ቤተክርስቲያን በደብረ ታቦር ትመሰላለች፡፡

Debretabor

በአዲስ ኪዳን ከተገለጹት የቤተክርስቲያን ምሳሌዎች መካከል አንዱ ደብረ ታቦር (የታቦር ተራራ) ነው፡፡ በዚህ ተራራ ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሀነ መለኮቱን ገልፆበታል፡፡ ይህንን ድንቅ ምስጢር ወንጌላዊ ማቴዎስ ‹‹ከስድስት ቀንም በኋላ ኢየሱስ ጴጥሮስንና ያዕቆብን ወንድሙንም ዮሐንስን ይዞ ወደ ረጅም ተራራ ብቻቸውን አወጣቸው። በፊታቸውም ተለወጠ፥ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ፥ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ሆነ። እነሆም፥ ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ታዩአቸው። ጴጥሮስም መልሶ ኢየሱስን፥ ጌታ ሆይ፥ በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው፤ ብትወድስ፥ በዚህ ሦስት ዳስ አንዱን ለአንተ አንዱንም ለሙሴ አንዱንም ለኤልያስ እንሥራ አለ። እርሱም ገና ሲናገር፥ እነሆ፥ ብሩህ ደመና ጋረዳቸው፥ እነሆም፥ ከደመናው። በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት የሚል ድምፅ መጣ። ደቀ መዛሙርቱም ሰምተው በፊታቸው ወደቁ እጅግም ፈርተው ነበር። ኢየሱስም ቀርቦ ዳሰሳቸውና፥ ተነሡ አትፍሩም አላቸው። ዓይናቸውንም አቅንተው ሲያዩ ከኢየሱስ ብቻ በቀር ማንንም አላዩም(ማቴ 17፡1-8)።›› በማለት አስፍሮታል፡፡

በአባቶች አመስጥሮ የታቦር ተራራ የቤተክርስቲያን ምሳሌ ናት፡፡ ‹‹ከስድስት ቀን በኋላ›› የሚለው ምሳሌው ቤተክርስቲያን በስድስተኛው ሺህ በኢየሱስ ክርስቶስ እንደምትመሠረት የሚያሳይ ነው (ትርጓሜው በስድስተኛው ወር መልአኩ (ሉቃ 1፡26)….እንደሚለው ነው)፡፡ በደብረ ታቦር ሦስቱን ደቀመዛሙርት ብቻ ይዞ መውጣቱ ምሥጢረ ክህነት ለሁሉም ሳይሆን ለካህናት ብቻ የሚፈፀም ምሥጢር መሆኑን ለማሳየት ነው፡፡ ብርሀነ መለኮቱንም የገለፀላቸው ለእነዚህ ብቻ ነበር፡፡

በደብረ ታቦር ክርስቶስ ብርሀነ መለኮቱን ገለጸ፡፡ በቤተክርስቲያንም እንደዚሁ የክርስቶስ ማደሪያው ናት፡፡ በደብረ ታቦር ኤልያስ ከብሔረ ሕያዋን ሙሴ ከብሔረ ሙታን ሐዋርያቱ ደግሞ በአካለ ሥጋ ያሉት በአንድነት ከአምላካቸው ጋር ተገኝተዋል፡፡ ቤተክርስቲያንም በአካለ ነፍስ ያሉ ቅዱሳንና በአካለ ሥጋ ያሉ ክርስቲያኖች ከአምላካቸው ጋር ያላቸው አንድነት ናትና የደብረ ታቦር ምሳሌ ጠንካራ መሠረት ያለው ነው፡፡ በቤተክርስቲያንም በቅዳሴ የሚሳተፉት ልዑካን አምስት ናቸው፡፡ ኤልያስና የሙሴ የሁለቱ ቀሳውስት፣ ሦስቱ ደቀመዛሙርት የሦስቱ ዲያቆናት ምሳሌ፣ ጌታችንም የመስዋዕቱ ምሳሌ ናቸው፡፡ ሊቃውንት አባቶች ይህንን ምሳሌ ከነምስጢሩ እንደዚህ አብራርተው አስተምረዋል፡፡

በዚያ በደብረ ታቦር ተራራ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹ ጴጥሮስም መልሶ ኢየሱስን:- ጌታ ሆይ፥ በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው፤ ብትወድስ፥ በዚህ ሦስት ዳስ አንዱን ለአንተ አንዱንም ለሙሴ አንዱንም ለኤልያስ እንሥራ አለ።›› እንዳለው በቤተክርስቲያንም ከቅዱሳንና ከቅዱሳን አምላክ ከእግዚአብሔር ጋር መኖር ምንኛ መልካም ነው? የክርስትናም ዓለማው ሰው ይህንን ሰላም አግኝቶ ከአምላኩ ጋር እየተነጋገረ በቤተክርስቲያን ይኖር ዘነድ ነው፡፡