በዓለ ጰራቅሊጦስ፡ በሀገሩ ሁሉ ቋንቋ ተናገሩ

  • በዓለ ጰራቅሊጦስ በመንፈስ ቅዱስ ለምትመራው የሐዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን የልደት ቀኗ ነው፡፡
  • ቤተክርስቲያን ለሁሉም በየቋንቋው ሃይማኖትን ማስተማር እንዳለባት ከመንፈስ ቅዱስ በላይ ምስክር አያስፈልግም፡፡
  • በየሀገሩ ቋንቋ ወንጌልን ማስተማር እንጂ የየሀገሩን ቋንቋ ለህዝብ ማስተማር የቤተክርስቲያን ኃላፊነት አይደለም፡፡
  • ለቅዱሳን ሐዋርያት የተገለጡላቸው ልሳናት (ቋንቋዎች) የታወቁ፣ ሰዎችም የሚግባቡባቸው ቋንቋዎች ናቸው፡፡
  • ለቅዱሳን ሐዋርያት የየሀገሩ ቋንቋ መገለጡ ሁሉም የዓለማችን ቋንቋዎች የሐዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን ልሳናት መሆናቸውንና የትኛውም ቋንቋ በተለየ ሁኔታ ብቸኛ የቤተክርስቲያን ልሳን እንዳልሆነ ያረጋግጥልናል፡፡
  • የልሳናት (ቋንቋዎች) መገለጥ ዓላማ ደቀመዛሙርቱ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ወንጌልን ለማስተማር ሲዘዋወሩ ሁሉንም በየቋንቋው ማስተማር እንዲችሉ ነው፡፡

የሐዋርያትን ፈለግ በምትከተል ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ከሚከበሩ ዘጠኝ ዐበይት በዓላት መካከል አንዱ በዓለ ጰራቅሊጦስ ነው፡፡ ይህም በዓል በሐዋርያት ሥራ ምዕራፍ 2 በተገለጸው መልኩ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ለ120ው ቤተሰብ የወረደበትን ዕለት የምናስብበት ነው፡፡ በዚህች የአስተምህሮ ጦማር ስለ መንፈስ ቅዱስ ጸጋ፣ ስለ በዓለ ጰራቅሊጦስ የብሉይ ኪዳን ምሣሌዎች፣ ለሐዋርያት ስለተገለጠው ልሳን (ቋንቋ) እንዲሁም ስለተያያዥ ጉዳዮች እንዳስሳለን፡፡

ጰራቅሊጦስ ማለት ምን ማለት ነው?

ጰራቅሊጦስ ማለት የግሪክ ቃል ሲሆን ከሦስቱ አካላት አንዱን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስን የሚገልጥ ነው፣ ትርጉሙም መንጽኢ (የሚያጸና)፣ መንጽሒ (የሚያነጻ)፣ ናዛዚ (የሚያጽናና፣ የሚያረጋጋ) ማለት ነው፡፡ በተጨማሪም ጰራቅሊጦስ ማለት ከሣቲ (ምስጢር ገላጭ)፣ መስተሥርዪ (ይቅር ባይ) እና መስተፍሥሒ (ደስታን የሚሰጥ) ማለት ነው፡፡ ከቅዱሳን ሐዋርያት የሚበዙት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ሞት በኋላ አይሁድን ፈርተው ይሸሹ ነበር፡፡ ከአይሁድ ፍርሃት ሙሉ በሙሉ መላቀቅ ያልቻሉ ደቀመዛሙርቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእነርሱ ተለይቶ እንደሚያርግ ሲነግራቸው አዘኑ፡፡ ለተልዕኮ የጠራቸው፣ ዓለምን በወንጌል ብርሃን እንዲያበሩ የመረጣቸው ጌታ ግን ለድካማቸው አሳልፎ አልሰጣቸውም፡፡ ከትንሣኤው በኋላ እስከ ዕርገቱ ድረስ ለ40 ቀናት እየተገለጠላቸው እምነታቸውን አጸናላቸው፣ ቅዱስ ቃሉን አስተማራቸው፣ ለሐዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያንም መሰረት የሆነ መንፈሳዊ ሥርዓትን አሳያቸው፡፡  ሰብሳቢ፣ ጠባቂ እንደሌላቸው የሙት ልጆች የሚሆኑ መስሏቸው ነበርና “የሙት ልጆች ትሆኑ ዘንድ አልተዋችሁም” (ዮሐ. 14፡18) አላቸው፡፡ ስለ ስሙ መከራን ለመቀበል እንዲጸኑ መንጽኢ (የሚያጸና) መንፈስ ቅዱስ ያስፈልጋቸው ነበርና “እኔ የአባቴን ተስፋ ለእናንተ እልካለሁ፤ እናንተ ግን ከአርያም ኃይልን እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ተቀመጡ፡፡” (ሉቃስ. 24፡49) በማለት ተስፋ ሰጣቸው፡፡ ይህም ተስፋ አስቀድሞ በነቢያት የተነገረ ነው (ትንቢተ ኢዩ. 2፡15)፡፡

ጰራቅሊጦስ ስለምን ኀምሳው ቀን በተፈጸመ ጊዜ ወረደ?

የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ በግልጥ ለሐዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን የተገለጠው ቅዱሳን ሐዋርያት፣ አርድእትና ቅዱሳት አንስት ከእመቤታችን ጋር በአንድነት ለጸሎት ለምስጋና ተሰብስበው እያለ ነው ፡፡ “ኀምሳው ቀን በተፈጸመ ጊዜ፣ ሁሉም በአንድነት በአንድ ቦታ ተሰብስበው ነበር” (ሐዋ 2፡1-47)ሐዋ 2:1) እንዲል፡፡ በነቢያትና በሐዋርያት መሰረትነት የቆመች ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን (ኤፌ. 2፡20) በዓለ ጰራቅሊጦስን በሐዋርያት ዘመን እንደነበረው ከጌታችን ትንሣኤ በኋላ በኀምሳኛው ቀን ታከብራለች፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በዓለ ጰራቅሊጦስን “የቤተክርስቲያን የልደት ቀን” ሲል ጠርቶታል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ የምትመራው የሐዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ተመልታ ለሰው ልጆች ሁሉ እውነተኛ የክርስቶስን ወንጌል መስበክ የጀመረችበት ቀን ነውና፡፡

በዘመነ ሐዲስ ከሚከበሩ በዓላት ብዙዎቹ በዘመነ ብሉይ የነበሩ ምሣሌዎች አሏቸው፡፡ ከእነዚህ አንዱ በዓለ ጰራቅሊጦስ ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ሙሴ በኦሪት መጻሕፍት እንደገለጠልን እስራኤል ዘሥጋ በዓለ ፋሲካን (እስራኤል ዘሥጋ ከግብጽ ባርነት ነፃ የወጡበት) ካከበሩ በኋላ ሰባት ሣምንታትን ቆጥረው በኀምሳኛው ቀን በዓለ ሰዊት (የእሸት በዓል) ያከብሩ ነበር (ዘሌ 23፡15-22፣ ዘጸ 34፡22፣ ዘኁ 28፡26)፡፡ ይህ የብሉይ ዘመን ታሪክ ሊመጣ ላለው ለክርስቶስ ቤዛነት ምሣሌ ነበር፡፡ መቶ ሃያ ቤተሰብ (12ቱ ሐዋርያት፣ 72ቱ አርድእትና 36ቱ ቅዱሳት አንስት) ከጌታችን ትንሣኤ በኋላ ሞገሳቸውን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በመካከል አድርገው በፍፁም አንድነት በጸሎት እየተጉ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰጣቸው የተስፋ ቃል የሚፈምበትን ዕለት በእምነትና በተስፋ ይጠብቁ ነበር (ሉቃ. 24፡49፣ ዮሐ. 14፡15-18፣ ዮሐ. 16፡7-15፣ ሐዋ. 1፡8)፡፡

አባታችን አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በመጽሐፈ ምስጢር የበዓለ ኀምሳ ምንባብ እንደገለፀልን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀመዛሙርቱ “የመንፈስ ቅዱስን መውረድ ተስፋ በሰጣቸው በኀምሳ ሦስተኛው ቀን፣ ከሙታንም ተለይቶ በተነሣ በኀምሳኛው ቀን፣ በዕለተ እሁድ ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ደቀመዛሙርቱ በጽርሐ ጽዮን ተሰብስበው ሳሉ” የሚያጸና፣ የሚያነፃ፣ የሚያረጋጋ የእግዚአብሔር መንፈስ በእሳትና በነፋስ አምሳል ተገለፀላቸው፡፡ በዕለተ እሁድ በመገለፁም የሰንበተ ክርስቲያንን ክብር አስረዳን፡፡ ነገረ ምጽዓቱ (ደብረ ዘይት)፣ የትንሣኤው ብርሃን፣ የመንፈስ ቅዱስም መውረድ ዘላለማዊት በሆነች (ዓለማት በሚያልፉባት ስለዚህም ጊዜ በሚጠፋባት)፣ የመንግስተ ሰማያት ምሳሌ በሆነች በሰንበተ ክርስቲያን ነውና መንፈስ ቅዱስ በዕለተ እሁድ በእሳትና በነፋስ አምሳል ተገለፀ፡፡

እንግዲህ እናስተውል እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ግን ከቅዱሳን ሁሉ በላይ ናትና ቁጥሯ (ክብሯ) ከ120ው በቤተሰብ ጋር አንድ አይደለም፤ የመንፈስቅዱስን ጸጋ ለመቀበል እንደ ሌሎች ቅዱሳን በዓለ ኀምሳን መጠበቅም አላስፈለጋትም፡፡ ከአበው አብራክ ከፍሎ የጠበቃት፣ በማኅፀነ ሐና ያከበራት፣ በቅዱስ ገብርኤል ብስራት ክብሯን የገለጠ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በተለየ ክብር ቀድሷታልና (ሉቃስ 1፡35)፡፡

የእሳትና የነፋስ ምሳሌነቱ ምንድን ነው?

እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በፍፁም አንድነት በልዩ ሦስትነት የሚመሰገን የራሱ ፍፁም መልክ፣ ፍፁም ገፅ፣ ፍፁም አካል ያለው፣ ከአብና ከወልድ ጋር ህልው ሆኖ የሚኖር፣ ዓለማትን የፈጠረ፣ የፍጥረታት ሁሉ መጋቢ፣ ዓለምንም አሳልፎ ለዘለዓለም የሚኖር አምላክ ነው፡፡ አባታችን አባ ሕርያቆስ መንፈስ ቅዱስ በገለጠለት የቅዳሴ ማርያም ምስጋናው እንዳስተማረን መለኮት (እግዚአብሔር) ግን ይህን ያህላል፣ ይህንንም ይመስላል ሊባል አይቻልም (ቅዳሴ ማርያም ቁጥር 47)፡፡ ይሁንና በዓለም ሁሉ በምልዓት የሚኖር አምላክ በፈቃዱ ለፍጥረታት ይገለጣል፡፡ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስም ዓለምን የፈጠረ፣ የሚጠብቅ፣ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስም ህልው ሆኖ (በህልውና ተገናዝቦ) ደቀመዛሙርቱን ለሐዲስ ኪዳን አገልግሎት የጠራቸው፣ በትምህርትም በተዓምራትም ከአብ ከወልድ ጋር የማይለይ ነው፡፡

ቀደምት ሊቃውንት ይህንን ሲያስረግጡ “ወነአምን በመንፈስ ቅዱስ እግዚእ ማኅየዊ ዘሠረፀ እም አብ ንስግድ ሎቱ ወንሰብሖ ምስለ አብ ወወልድ ዘነበበ በነቢያት/ከአብ በሠረጸ ጌታ ማኅየዊ በሚሆን በመንፈስ ቅዱስ እናምናለን፣ ከአብና ከወልድ ጋር እንስገድለት እናመስግነውም ዘንድ፣ በነቢያት አድሮ የተናገረ እርሱ ነው/” በማለት ደንግገዋል (ጸሎተ ሃይማኖት)። በተጨማሪም ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ኤጲስ ቆጶስ ዘቆጵሮስ “ወነአምን በመንፈስ ቅዱስ ነባቢ በውስተ ሕግ ወሰባኪ በነቢያት ዘወረደ በዮርዳኖስ ወተናገረ በሐዋርት ወኃደረ በቅዱሳን ወነአምን ቦቱ ከመ ውእቱ ህላዌ መንፈስ ቅዱስ ፍጹም ጰራቅሊጦስ ዘኢተፈጥረ ዘሠረፀ እም አብ ወነሥአ እም ወልድ / ሕግን በሠራ፣ በነቢያት አድሮ ባስተማረ፣ በዮርዳኖስ በወረደ፣ በሐዋርያት አድሮ ባስተማረ፣ በሊቃውንትም ባደረ፣ በመንፈስ ቅዱስ እናምናለን ። ባሕርየ መንፈስ ቅዱስ ያልተፈጠረ፣ ከአብ የተገኘ (የሠርፀ)፣ ቃልነትን ከወልድ ገንዘብ ያደረገ፣ ፍጹም አካላዊ እንደሆነ በእርሱ እናምናለን” በማለት መንፈስ ቅዱስን ገልጾታል።

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚታይ ሥጋ፣ በሰው ቋንቋ ደቀመዛሙርቱን ካስተማራቸው በኋላ በሥጋ ሲለያቸው አገልግሎታቸው በሥጋ ፈቃድ የሚመራ አለመሆኑን ይረዱ ዘንድ በልዩ ልዩ ኅብረ አምሳል የሚገለጥ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በመካከላቸው እስከ ዓለም ፍፃሜ እንደሚኖር ሲያሳስባቸው በእሳትና በነፋስ አምሳል ተገለፀ (ማቴ. 28፡20)፡፡ የእሳትና የነፋስ ምሣሌነቱም እንዲህ ነው፡- ነፋስ ረቂቅ ነው፣ አናየውም፡፡ ነገርግን ፍሬውን ከገለባው ይለያል፡፡ መንፈስ ቅዱስም ጻድቃንን ከኃጥአን ይለያል፡፡ ነፋስ በዓይናችን አናየውም፣ በዓለም ሁሉ ግን በምልዓት ይኖራል፡፡ ነገር ግን ባሕር ሲገስጽ፣ ዛፍ ሲያናውጥ ሥራውን እናያለን፡፡ መንፈስ ቅዱስም እንዲሁ ነው፡፡ (ዮሐ. 3፡8) በዓለም ሁሉ በምልዓት ሳለ አናየውም፣ ቋንቋ ሲያናግር፣ የቅዱሳት መጻሕፍትን ምስጢር ሲገልጽ፣ ሰማዕታትን ለገድል ለትሩፋት ሲያስጨክናቸው (ሲያጸናቸው) ይታወቃል እንጂ፡፡ እሳት ያልበሰለውን ያበስላል፤ መዓዛ ያልነበረውን እህል መልካም መዓዛ ይሰጠዋል፡፡ እንደዚሁም በመንፈስቅዱስ መገለጥ ያልበሰሉ (የማያስተውሉ) የነበሩ 120ው ቤተሰብ አስተዋዮች ሆነዋል፡፡ መልካም መዓዛ ያልነበራቸው፣ ስለክርስቶስ ስም፣ ስለቤተክርስቲያን እውነተኛ ትምህርት መከራ መቀበልን ይፈሩ፣ ይሸሹ የነበሩ ደቀመዛሙርቱ በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ለገድል ለትሩፋት የሚፋጠኑ፣ የሰይጣንና የመናፍቃንን ግፍ የማይሰቀቁ ሆኑ፣ እስከ መስቀል ሞት ድረስም ጥቡዓን የጽድቅ ምስክሮች (መከራ መቀበልን የሚደፍሩ) ሆነዋል፡፡

እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የሚያድርባቸው ሰዎች አስቀድመው ራሳቸውን ለመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ያዘጋጁ መሆን አለባቸው፡፡ ይህም በቅዱሳን ሐዋርያት፣ በቅድስት ኤልሳቤጥ ታሪክ የተገለጸ ነው፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ የሚመሩ ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈሳዊ ተግባራቸውን በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ሲፈጽሙ የመንፈስ ቅዱስን ፈቃድ እንደሚፈጽሙ ይታወቃል (ሐዋ. 15፡28)፡፡ እስከ ዘመናችን ድረስም በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን እምነታችን፣ ተስፋችን ይሔው ነው፡፡ ነገር ግን በቅዱሳት መጻሕፍት በተገለጠ፣ በታወቀ  በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ሕይወታቸውን የማይመሩ፣ ይልቁንም በበደልና በኃጢአት የገነኑ ሰዎች የራሳቸውን ፈቃድ በፈጸሙ ጊዜ የዋሀንን በማታለል “የመንፈስ ቅዱስ ሥራ” ነው እያሉ እንደሚያታልሉት አይደለም፡፡ የራሳቸውን ፈቃድ፣ በተጥባበ ሥጋ ብቻ የደረሱበትን ሀሳብ እንዲሁም የዓለማውያን ፖለቲከኞችን ጥላቻ ጭምር “በመንፈስ ቅዱስ ስም ወስነናል” የሚሉ በስንዴው መካከል የበቀሉ እንክርዳዶች ስላሉ በማስተዋል ልንጓዝ ያስፈልጋል፡፡ መንፈስን ሁሉ አትመኑ ተብለናልና፡፡

አስቀድሞ ለሐዋርያት የተሰጣቸው ተስፋ ምን ነበር?

ቅዱሳን ሐዋርያት ጸጋ መንፈስ ቅዱስን በተቀበሉ ጊዜ አላዋቂ የነበሩት አዋቂዎች መሆናቸው ከግልጥ ከታወቀባቸው ማሳያወች አንዱ ጌታችን ያስተማራቸውን የወንጌል ብርሃን አስቀድሞ በማያውቋቸው ልዩ ልዩ ቋንቋዎች ማስተማር መቻላቸው ነው፡፡ ሐዋርያ ማለት ዞሮ የሚያስተምር ማለት ነው፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት ዓለምን ዞረው እንዲያስተምሩ ጌታችን አዟቸዋል፤ የቤተክርስቲያንን አደራ ተቀብለዋል፡፡ በዓለም ዞረው ሲያስተምሩ ብዙ መከራ እንደሚጠብቃቸው ጌታችን አስቀድሞ ነግሯቸዋል (ማቴ. 10፡16-25፣ ዮሐ. 15፡18-25)፡፡ የእውነት የክርስቶስ ምስክሮች በመሆናቸው ለሞት ለመከራ ተላልፈው እንደሚሰጡ ሲነግራቸው “አሳልፈው በሰጧችሁ ጊዜ እንዴት ወይም ምን እንደምትናገሩ አትጨነቁ፤ በዚያች ሰዓት የምትናገሩት ይሰጣችኋልና፡፡ የሰማያዊው አባታችሁ መንፈስ እርሱ በእናንተ ላይ አድሮ ይናገራል እንጂ የምትናገሩ እናንተ አይደላችሁምና” ብሏቸዋል (ማቴ. 10፡19-20)፡፡ በዓለም ዞሮ ለማስተማር በየዓለሙ ያለውን ቋንቋ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ሐዋርያት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር በዋለበት እየዋሉ ባደረበት እያደሩ ለሦስት ዓመት ከሦስት ወር ወንጌልን ተማሩ እንጅ የዓለም ቋንቋ አልተማሩም ነበር፡፡ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ በተከፋፈሉ የእሳት ላንቃዎች አምሳል (ሐዋ. 2፡3) በወረደላቸው ጊዜ ግን ሐዋርያት “መንፈስ ቅዱስ እንደአደላቸው መጠንም እየራሳቸው በሀገሩ ሁሉ ቋንቋ ይናገሩ ጀመር፡፡” (ሐዋ. 2፡4)

ለሐዋርያት የተገለጠላቸው ልሳን ምን ነበር?

ለሐዋርያት የተገለጠላቸው ልሳን (ቋንቋ) ሰው የማይሰማው ቋንቋ አልነበረም፡፡ ይልቁንም በዓላቸውን ሊያከብሩ ከተለያዩ የዓለም ክፍሎች የተሰበሰቡ አይሁድ እስኪደነቁ ድረስ በየሀገራቸው ቋንቋ ይናገሩ ነበር፡፡ ለምሣሌ ከተዘረዘሩት መካከል ከጳርቴ፣ ከሜድ፣ ከኢላሚጤ እንዲሁም ከሌሎች ዓለማት የመጡ አይሁድ ሐዋርያት በየቋንቋቸው ሲናገሩ ሰምተው ተደነቁ፡፡ ሰው ቋንቋን ተምሮ ቢናገር አያስደንቅም፡፡ ሲናገርም ቀስ በቀስ ይለምዳል እንጅ በአንድ ጊዜ በማያውቀው ቋንቋ ሊቅ ሊሆን አይችልም፡፡ ለእግዚአብሔር ግን የሚሳነው የለምና ለሐዋርያት በአንድ ጊዜ እስከ 72 ቋንቋ ተገለጸላቸው፤ ለሁሉም በየቋንቋው የሚያስተምሩበትን የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ተቀበሉ፡፡ ለቅዱሳን ሐዋርያት የየሀገሩ ቋንቋ መገለጡ ሁሉም የዓለማችን ቋንቋዎች የሐዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን ልሳናት መሆናቸውንና የትኛውም ቋንቋ በተለየ ሁኔታ ብቸኛ የቤተክርስቲያን ልሳን እንዳልሆነ ያረጋግጥልናል፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍት በብዛት የተጻፉባቸውና የተተረጎሙባቸው ቀደምት ቋንቋዎች የቤተክርስቲያንን አስተምህሮ ከሌሎች ቋንቋዎች በበለጠ ሊገልጡ እንደሚችሉ ግልጽ ቢሆንም አንዱ ቋንቋ የበላይ፣ ሌላው ግን በእግዚአብሔር ዘንድ ያነሰ ክብር ያለው አስመስሎ ከሚያይ ስሁት እይታ ልንጠበቅ ይገባል፡፡  

የተገለጠላቸውን የቋንቋ ብዛት ቅዱስ ሉቃስ ሲገልጽ “መንፈስቅዱስ እንደአደላቸው መጠን” (ሐዋ. 2፡4) መሆኑን አስረዳን፡፡ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን በታመነ ሐዋርያዊ ትምህርታቸው እንዳቆዩልን ለ12ቱ ሐዋርያት እያንዳንዳቸው አስቀድሞ የሚያውቁትን የዕብራይስጥን ቋንቋ ጨምሮ 72 የዓለም ቋንቋዎች (ልሳናት) ያለተከፍሎ (ምንም ሳይቀርባቸው) እንደተገለጠላቸው ጽፈውልናል፡፡ ሌሎች አርድእት ደግሞ ከ15 ጀምሮ 20፣ 25፣ 30፣ 40፣ 50 ቋንቋዎች የተገለጠላቸው ነበሩ፡፡ በእነዚህ አርድዕት ዘንድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ  “በልሳን የሚናገር ቢኖር ሁለት ወይም ቢበዛ ሦስት ሆነው በተራቸው ይናገሩ አንዱም ይተርጉም” ብሎ እንደገለጸው አንዱ ሲያስተምር ሌላው ሌላ ቋንቋ ለሚናገረው ሕዝብ እየተረጎመ አገልግሎታቸውን ፍጹም ያደርጉት ነበር (1ኛ ቆሮ 14፡27)፡፡ የሐዲስ ኪዳን መተርጉማን ለቅዱሳን ሐዋርያት 72 ቋንቋ የመገለፁን ነገር ሲያስረዱ በዘመነ ብሉይ ከነበረው በበደል ምክንያት ከመጣው  የቋንቋ መደባለቅ ጋር ያመሳክሩታል፡፡

የቋንቋ መደበላለቅ ቁጣ አልነበረምን?

በባቢሎናውያን በደል ምክንያት አንድ ቋንቋ የነበራቸው አህዛብ በመንፈስቅዱስ ቁጣ ቋንቋቸው ተደባለቀ፤ በአንድ ቋንቋ ከመነጋገር (ከመግባባት) ቋንቋቸው 72 ሆነ (ዘፍ 11:1)፡፡ ይህም የእርግማን፣ የመለያየት ምልክት ነበር፡፡ በዘመነ ብሉይ የነበሩ ልዩ ልዩ የእርግማን ምልክቶች በዘመነ ሐዲስ ግን የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ መገለጫዎች ሆነዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል የጥፋትና የቅጣት መሳሪያ የነበረው ውሃ (ማይ) (ዘፍጥረት 7) ከመንፈስ ቅዱስ የምንወለድበት የሐዲስ ኪዳን ልጅነት መገለጫና ማረጋገጫ ሆኗል፡፡ (ዮሐ. 3፡5) የበደለኞችና የኃጢአተኞች መቅጫ የነበረው መስቀል (ዘዳግም 21፡23) የክርስቶስ የክብር ዙፋን፣ የቤተክርስቲያን አርማ ሆኗል፡፡ (ማቴ. 20፡20-23) በተመሳሳይ የእርግማንና የመለያየት ምልክት የነበሩት 72 ልሳናት (ቋንቋዎች) በፍፁም አንድነት፣ በመንፈሳዊ ኅብረት ለተሰበሰቡ ቅዱሳን ሐዋርያት ሲገለጡ የእርግማን ምልክት መሆናቸው ቀርቶ ፍፁም የሆነ የመንፈስቅዱስ ስጦታ መሆናቸው ተገለጠ፡፡

ቤተክርስቲያን ለሁሉም በየቋንቋው ሃይማኖትን ማስተማር እንዳለባት ከመንፈስ ቅዱስ በላይ ምስክር አያስፈልግም፡፡ ስለሆነም በዘረኝነትና በመሳሰለው ምክንያት አንዱ ቋንቋ ከሌላው የሚበልጥ አስመስለው የሚናገሩ አላዋቂዎች ከመንፈስ ቅዱስ ተምረው ለሁሉም በየቋንቋው የእግዚአብሔርን ቃል ማቅረብን ሊደግፉ፣ ሊያበረታቱ ይገባል፡፡ ለቅዱሳን ሐዋርያት የየሀገሩ ሁሉ ቋንቋ በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ መገለጡ የተለያዩ ህዝቦች በሚናገሩበት ቋንቋ በመጠቀም ትምህርተ ወንጌልን፣ ሕገ ቤተክርስቲያንን ማስተማር የቤተክርስቲያን መምህራን መንፈሳዊ ግዴታ (ኃላፊነት) መሆኑን ያሳስበናል፡፡ ቋንቋ የሌለው ሕዝብ የለምና የየሀገሩን ቋንቋ ለህዝብ ማስተማር የማኅበረሰብ እንጂ የቤተክርስቲያን ኃላፊነት አይደለም፡፡ በብዙ የውጭ ሀገራት ያሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አጥቢያዎች የኢትዮጵያን ቋንቋዎች ለህጻናት ለማስተማር ይደክማሉ፡፡ ይህ የሚበረታታ ማኅበረሰባዊ ኃላፊነት ነው፡፡  ይሁንና የቤተክርስቲያን ግዴታ ግን አይደለም፡፡ የቤተክርስቲያን ግዴታ ህጻናቱን ጨምሮ ሁሉም ምዕመናን (ከተቻለም ሌሎች አህዛብ) በሚገባቸው፣ በሚረዱት ማንኛውም ቋንቋ ትምህርተ ወንጌልን፣ ሕገ ቤተክርስቲያንን ማስተማርና ሰዎችን ለሰማያዊ መንግስት ዜግነት ማብቃት ነው፡፡

ልሳን ማለት ምን ማለት ነው?

ልሳን ማለት የቃሉ ትርጉም ቋንቋ ማለት ነው፡፡ ብዙዎቹ መናፍቃን ይህን ስለማይረዱ የልሳን ስጦታን ከመግባቢያ፣ ከመማማሪያ፣ ጸሎት ከማድረሻ ቋንቋ የተለየ አድርገው ስለሚገምቱት ለሰይጣን አሠራር በቀላሉ ይጋለጣሉ፡፡ ሰይጣንም ለማይረባ አምልኮ፣ በማያውቁት፣ በማይገባቸው ቋንቋ ክፉ ይሁን በጎ የማይረዱትን መልእክት በደመነፍስ እንዲናገሩ ያደርጋቸዋል፡፡ አንዳንዶችም በልምምድና በሽምደዳ ተራ ጩኸት በመጮኽ በልሳን ተናገርን እያሉ ራሳቸውን ያታልላሉ፣ ማገናዘብ የማይችሉ የዋሀንንም ያስታሉ፡፡

ለቅዱሳን ሐዋርያት የተገለጡላቸው ልሳናት (ቋንቋዎች) የታወቁ፣ ሰዎች የሚግባቡባቸው ቋንቋዎች ናቸው፡፡ ይሁንና የመንፈስ ቅዱስን ስጦታ ማቃለል የሚወድ ሰይጣን በየዘመናቱ በመናፍቃን እያደረ አጋንንታዊ ጩኸትን ከመንፈስቅዱስ ስጦታ ጋር በማምታታት ብዙ አላዋቂዎችን፣ ማገናዘብ የማይችሉ ሰነፎችን አታሏል፤ ወደፊትም ያታልላል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ግን ለሰው የሚጠቅም፣ ለአገልግሎት የሚውል ቋንቋን እንጅ አረፋ የሚያስደፍቅ አጋንንታዊ ጩኸትን አይገልጽም፡፡ መናፍቃኑ በየአዳራሹ የሚዘባርቁት ትርጉም አልባ ጩኸት በብልሃት የተፈጠረ ተረት እንጅ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ አለመሆኑን ለመረዳት መጽሐፍ ቅዱስ በልዩ ልዩ ልሳናት (ቋንቋዎች) መናገርን በተመለከተ ከሚያስተምረን እውነትና ከቤተክርስቲያን ትውፊት አንጻር በሚከተለው መልኩ መገምገም ይገባል፡፡

ለሐዋርያት ቋንቋዎች ለምን ተገለጡላቸው?

ቅዱሳን ሐዋርያት ቋንቋዎች የተገለፁላቸው ስለሁለት ዋና ዋና ምክንያቶች እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስና የቤተክርስቲያን ትውፊት ያስረዳናል፡፡ በዋነኛነት የልሳናት (ቋንቋዎች) መገለጥ ዓላማ ደቀመዛሙርቱ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ወንጌልን ለማስተማር ሲዘዋወሩ ሁሉንም በየቋንቋው ማስተማር እንዲችሉ ነው፡፡ ለዚያም ነው ሐዋርያት በየሀገሩ ቋንቋ በመንፈ ስቅዱስ ስጦታ በተናገሩ ጊዜ ከየሀገሩ የተሰበሰቡ አይሁድ “እንግዲህ በየሀገራችን ቋንቋ ሲናገሩ እንዴት እንሰማቸዋለን?” (ሐዋ. 2፡8) ያሉት፡፡ በተቃራኒው መናፍቃኑ ተገለጠልን እያሉ የሚዘባርቁት ጩኸት ግን ተዘዋውሮ ለማስተማር የሚሆን አይደለም፡፡ አማርኛ ብቻ የሚናገር ሰው ሌላ ልሳን (ቋንቋ) ተገልጾለት በኦሮምኛ፣ በትግርኛ፣ በሲዳምኛ፣ በጉራጊኛና በመሳሰሉት ቢያስተምር ነው የሐዋርያት ዓይነት ልሳን ተገለፀ ማለት የሚቻለው፡፡ ይህም ቋንቋ በመለማመድና ትንሽ ቃላትን በመናገር ሳይሆን የመጻሕፍትን ምስጢር ሳያዛቡ በሙሉ መረዳት በሌሎች ቋንቋዎች ማስተማርን ይጠይቃል፡፡ ስለሆነም የመናፍቃኑ ማምታቻ የሰይጣን አሠራር መሆኑ በዚህ ይታወቃል፡፡

በሁለተኛ ደረጃ ለሐዋርያት ቋንቋ የተገለጸው መገለፁ ተዓምር ነውና ሰዎች ተዓምሩን አይተው ወደጽድቅ መንገድ እንዲመጡ ለመርዳት ነበር፡፡ “ሁሉም ተገረሙ፤ የሚሉትንም አጡ” (ሐዋ. 2፡12) እንዲል፡፡ “አሁንም ቋንቋ መናገር ለማያምኑ ሰዎች ለምልክት ነው” (1ኛ ቆሮ. 14፡22) እንደተባለ ምልክት (ተዓምር) የሆነው፣ የሚሆነው የሚሰማ የሚታወቅ ቋንቋ መናገር እንጂ መናፍቃኑ እንደሚያደርጉት ያለ ትርጉም አልባ የጩኸት ጋጋታ አይደለም፡፡ ረጋ ብለው መናገር የማይችሉትን፣ ትርጉሙን የማያውቁትን፣ ሰዎችም የማይረዱትን የአጋንንት ጩኸት መጮህ በምንም መልኩ ተዓምር ሊባል አይችልም፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት ልሳናት ሲገለጡላቸው በእሳት አምሳል የተከፋፈሉ ልሳናት ለሁሉም ተገልጠውላቸዋል፡፡ እንግዲህ አእምሮ እንደሌላቸው ሆነው የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ በአጋንንታዊ ጩኸት የሚያቃልሉ መናፍቃን የእሳት ልሳናትንም በማስመሰል እንዲሰጣቸው አለቃቸውን (ዲያብሎስን) ይጠይቁት ይሆን!?

በአጠቃላይ በዓለ ጰራቅሊጦስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በተነሳ በኀምሳኛው ቀን፣ በክብር በምስጋና ወደሰማይ ባረገ በአስረኛው ቀን በፍቅር ጉባኤ፣ በአንድነት መንፈስ ለተሰበሰቡ ለ120ው ቤተሰብ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ መገለጡን፣ ዓለምን ዞረው የሚያስተምሩበት የልሳን (ቋንቋ) ስጦታ መቀበላቸውን የምናዘክርበት ከኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ዘጠኝ ዐበይት በዓላት አንዱ ነው፡፡ለሐዋርያት በእሳትና በነፋስ አምሳል የተገለጠ መንፈስቅዱስን የምንዘክረው እንዳለፈ ታሪክ ብቻ ሳይሆን ዛሬን ጨምሮ ለዘለዓለም የቤተክርስቲያን መሪ፣ ምስጢራትን አክባሪ፣ የቅዱሳት መጻሕፍት ምስጢርና ትርጓሜ ገላጭ፣ በአጠቃላይ የቤተክርስቲያን ጠባቂ መሆኑን በመረዳት ነው፡፡

እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ዛሬም ዕለት ዕለት በቤተክርስቲያን የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም ሊያከብር፣ ሊለውጥ፤ በጥምቀት ወደ ቤተክርስቲያን ማኅበር የሚቀላቀሉትን ህጻናትና ምዕመናን ሊያነፃና ሊያከብር፤ ለእውነተኛ መምህራን  የቅዱሳት መጻሕፍትን ምስጢርን ሊገልጽ፣ የመሳሰለውንም አገልግሎት ሊያከብር ይወርዳል፤ በእምነትም እናየዋለን፡፡ ከመንፈስ ቅዱስ ጸጋ  የተነሳ ቅዱሳን ሐዋርያት የተለያዩ ሀገራት ቋንቋዎች ስለተገለጡላቸው የወንጌልን ብርሃን በዓለም ለማስፋፋት ቻሉ፡፡ የተገለጡላቸው ቋንቋዎችም ሰው የሚሰማቸው፣ ለመግባባት፣ ለትምህርትና ለጸሎት የሚሆኑ የታወቁ ቋንቋዎች ናቸው፡፡ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ የሚያቃልሉ መናፍቃን ግን ይህን ለሐዋርያት የተገለጸ እውነተኛ ቋንቋ ትርጉም ከሌለው አጋንንታዊ ጩኸት ጋር በማምታታት ብዙዎችን ያታልላሉ፡፡ አዕምሮ እንደሌላቸው ሆነውም በማይገባቸው ጩኸት የማይረዱትን ይናገራሉ፡፡ እንግዲህ ምን እንላለን? የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ያለ ዓላማ የሚገለጥ አይደለም፡፡ ለሐዋርያት ጸጋን የሰጠ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ማስተዋሉን ያድለን፡፡

ስብሃት ለእግዚአብሔር፣ ወለወላዲቱ ድንግል፣ ወለመስቀሉ ክቡር፡፡